« …ጾታዊ ጥቃት የሚያስከትለውን የጤና መታወክ ለማስወገድ…..»

                                      ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
                                                Teferdgne @yahoo.com

በኢትዮጵያ በጾታ ጥቃት ምክንያት በሚደርስ የጤና ችግር ተጎጂዎቹ ብዙዎች ናቸው፡፡ በእርግጥ የጾታ ጥቃት ወንዶችንም አልፍ አልፎ የሚመለከት ቢሆንም በአብዛኛው ግን በሴቶች ላይ እንደሚፈጸም  እሙን ነው፡፡ ይህንን ችግር ለመከላከልም የሚያስችል ፕሮጀክት መነደፉና ወደስራ ለመግባትም ዝግጅቱ መጠናቀቁን የሚገልጽ መድረክ መስከረም ስምንት ሁለት ሺህ ዓ/ም (1/8/2002) በአዲስ አበባ ደሳለኝ ሆቴል ተካሂዶ ነበር፡፡ ፕሮጀክቱ በምን መልክ እንደሚፈጸም የሚያብራሩልን ዶክተር ደሴ እንግዳየሁ ሲሆኑ ዶ/ር ደሴ የማህጸንና ጽንስ ሐኪም፣የኢትዮጵያ የማህጽንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር አባል እና በጾታ ጥቃት ምክንያት የሚደርሱ የጤና ችግሮችን የመከላከል ፕሮጀክት አስተባባሪ ናቸው፡፡

ኢሶግ/ የፕሮጀክቱን አጠቃላይ ገጽታ ቢገልጹልን?
ዶ/ር  ፕሮጀክቱ በኢትዮጺያ የማህጸንና ጽንስ ሀከሞች ማህበርና በ UNFPA ዩ-ኤን-ኤፍፒኤ ትብብር በአንድነት የሚሰራ የመከላከልና ጥቃት የደረሰባቸውን ሴቶች አስፈላጊውን ህክምና እንዲያገኙ ማድረግ የሚቻልበትን መንገድ የሚያመቻች ነው፡፡ በእርግጥ የሴቶች ጥቃት በተለያየ አቅጣጫ መገለጫው ብዙ ነው፡፡ ይህ ፕሮጀክት ግን የሚያተኩረው በህጻናት ላይ በአስገድዶ መድፈር ምክንያት በሚደርሰው ጾታዊ ጥቃት ምክንያት የሚከሰተውን የስነተዋልዶ አካላትና ሌሎችም የጤና መታወኮችን የተመለከተ ነው ፡፡ ፕሮጀክቱ ትኩረት የሚያደርገው በሆስፒታሎች እና ከዛ ጋር ተያይዞም በዩኒቨርሲቲዎች ላይ ነው፡፡
ለዚሁም የተመረጡት ….

ባህር ዳር --ፈለገ ህይወት ሆስፒታል፣ጎንደር ዩኒቨርስቲ ሆስፒታል ፣ መቀሌ  ዩኒቨርስቲ ሆስፒታል፣ አዳማ ሆስፒታል ፣ድሬዳዋ ድል ጮራ ሆስፒታል ፣አዋሳ ዩኒቨርስቲ ሆስፒታል፣ ጅማ ዩኒቨርስቲ ሆስፒታል ናቸው፡፡
ኢሶግ/ ጾታዊ ጥቃት የደረሰባቸውን ሕጻናት ጤና በመንከባከቡ ረገድ ከአሁን ቀደም ያለው ልምድ ምን ይመስላል?
ዶ/ር  የኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሀኪሞች ማህበር ከአሁን ቀደም ከአለም አቀፉ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር ጋር በመተባበር በጋንዲ ሆስፒታል አንድ ሞዴል ክሊኒክ አቋቁሞ ነበር፡፡ የዚያ ክሊኒክ ትኩረቱ ጥቃት የደረሰባቸው ሴቶች ላይ ነበር፡፡ በእርግጥ ጥቃት በወንዶች ላይም እንደሚደርስ ይታወቃል፡፡ እኛ ሀገር በብዛት የሚታየው ግን ሴቶች ላይ የሚደርሰው ነው ፡፡  ያ ፕሮጀክት በተለይ ጥቃት ደርሶባቸው የሚመጡ ሴቶች ትክክለኛውና የተሙዋላ ህክምና ተደርጎላቸው አስፈላጊው መረጃ ደግሞ ለፖሊስና ለፍርድ ቤቶች ተጽፎ ወንጀል ያደረሰው ሰው አስፈላጊውን የህግ እርምጃ እንዲወሰድበት በማድረግ ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጎ ነበር፡፡ በጋንዲ ሆስፒታል የተቋቋመው ይህ ክሊኒክ ለሁለት አመት ያህል አገልግሎት ከሰጠ በሁዋላ ፕሮጀክቱ በማብቃቱ ለጊዜው ተቋርጦአል፡፡ የዚህ ፕሮጀክት የስራ ውጤት የኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበርን በ UNFPA ዩኤንኤፍፒኤ ለተመሳሳይ ፕሮጀክት እንዲመረጥም አስችሎታል፡፡
አሁን ከዩኤንኤፍፒኤ ጋር የጀመርነው ፕሮጀክት ከጋንዲው ፕሮጀክት ተሞክሮ በመነሳት በተወሰኑት ክልል መስተዳድሮች በሚገኙ ሆስፒታሎችና ዩኒቨርሲቲዎች ስራውን ለማስፋፋት ነው፡፡ ይህ ፕሮጀክት በትክክል ስራውን ሲጀምር ሕመምተኞች በአንድ ጣሪያ ስር ሁሉንም አይነት አገልግሎት እንዲያገኙ ይደረጋል፡፡ መረጃዎቻቸው በጥሩ ሁኔታ በምስጢር ይጠበቅላቸዋል፡፡ ለፍርድ ቤትና ለፖሊስ የሚጻፈው ወረቀትም በፍጥነት ይደርስላቸዋል ፣ከዚያም በተጨማሪ በሴቶች ጥቃት ዙሪያ ስላለው ችግር ለፖሊስ ፣ ለመገናኛ ብዙሀን እንዲሁም ለጤና ባለሞያዎች ስልጠናና የአድቮኬሲ ስራን ይጨምራል፡፡  
ኢሶግ/ ይህንን ፕሮጀክት ለመጀመር የተደረገ ጥናት አለ ?
ዶ/ር/  ለስራው በታጩት ሆስፒታሎችና ዩኒቨርሲቲዎች አንዳንድ ሁኔታዎች ላይ ጥናት ተደርጎአል፡፡እነዚህ የጤና ተቁዋሞች ያላቸው ብቃት ምን ይመስላል ? ጥቃት  ደርሶባቸው የሚመጡ ሰዎችን እንዴት ነው የሚያስተናግዱት?  የጤና ተቁዋሞቹ  የህክምና መስጫ ቦታ ፣የህክምና መሳሪያ ፣ መድሐኒት ፣ የመረጃ ዶክመንት አላቸው ወይ? የሚለው ተዳስሶአል ፡፡
በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ የባለሞያዎቹ እውቱ ፣ስልጠናው፣ ብቃቱ አላቸው ወይ ? በጾታዊ ጥቃት ላይ ያላቸው አመለካከት ምን ይመስላል? መሰልጠን ያስፈልጋቸዋል ወይስ አያስፈልግም ? የሚያነቡት አስፈላጊ ማቴሪያል አላቸው ወይ ? የሚለውም እንደዚሁ በጥናቱ ተዳስሶአል፡፡

በዳሰሳ ጥናቱ እንደታየው ከሆነ በአብዛኛው የጤና ባለሙያው ከሌሎች አካሎች..ማለትም  ከፖሊስ ፣ ከፍርድ  ቤቶች ፣ከህብረተሰቡ ጋር ጭምር እንደዚሁም  ጥቃት ለደረሰባቸው ሴቶች እርዳታ ከሚሰጡ አካላት ጋር ምን ያክል በትብብር እንደሚሰራም ለማየት ተሞክሮአል፡፡ እናም በዚህ ጥናት ያሉትን ደካማና ጠንካራ ጎኖች በመለየት ክፍተት ያለበትን ቦታ ለመሙላት ነው ጥረት የሚደረገው፡፡
ኢሶግ/ ፕሮጀክቱ ከሆስፒታሎችና ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር በጥምረት እንዲሰራ መታቀዱ
ለምንድነው?

ዶ/ር  በዩኒቨርሲቲዎች የሚሰጡት የጤና ትምህርቶች በጾታ ጥቃት ዙሪያ የሚደርሱትን የጤና ችግሮች በሚመለከት ዝርዝር እይታ የላቸውም፡፡ የዚህ ፕሮጀክት አንዱ እይታ የጤና ባለሙያው ተምሮ በሚወጣበት ጊዜ በዚህ ዙሪያ በቂ እውቀት እንዲኖረው ማድረግ ስለሆነ በትምህርቱ እንዲካተት ማድረግ ነው፡፡ ምክንያቱም አንድ ፕሮጀክት የሚነደፈው የተወሰነ ጊዜን በእቅድ ይዞ ነው፡፡ ፕሮጀክቱ ሲያበቃ ለህብረተሰቡ የሚሰጠው አገልግሎት ግን መቋረጥ የለበትም፡፡ ስለዚህ የጤና ባለሙያዎቹ በበቂ ሁኔታ ትምህርቱን ካገኙ አገልግሎቱ ይቀጥላል፡፡ ለጊዜው ግን ለመመረቅ በዝግጅት ላይ ላሉት የህክምና ባለሙያዎች እውቀቱ በስልጠና እንዲሰጥ የኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር ESOG አቅዶአል፡፡

ኢሶግ/ ከዚህ ፕሮጀክት ምን እንጠብቅ?

ዶ/ር  ዋናው ቁልፍ ነገር ስልጠና ነው፡፡ በዚህ ዙሪያ የሚሰሩ ባለሙያዎችን
አመለካከታቸውን እንዲቀይሩና በችግሩ ዙሪያ በቂ እውቀት እንዲኖራቸው ማድረግ ወሳኝ ነው፡፡ሌላው ነገር ለፕሮጀክቱ ማስፈጸሚያነት ከተመረጡት ሆስፒታሎችና ዩኒቨርሲቲዎች ቅድሚያ ተሰጥቶ ስራው የሚጀመረው ለጊዜው ባልተለዩት ግን በሁለቱ ላይ ብቻ ሲሆን በዚያም  ቀደም ሲል በጋንዲ የተቋቋመውን ክሊኒክ የሚመስል ሞዴል ክሊኒኮች ይቋቋማሉ፡፡ ለክሊኒኮቹም የነርስ ባለሙያ ከመቅጠር ጀምሮ አስፈላጊው ነገር ሁሉ እንዲሟላ ይደረጋል፡፡
ሆስፒታሎቹ በእጃቸው ያለውን መድሐኒት የላቦራቶሪ እቃ እና ባለሙያዎችን በተገቢው መንገድ እንዲጠቀሙ ማድረግም ሌላው ትኩረት የሚደረግበት ነው፡፡
ከሌሎች መስሪያ ቤቶች ጋር በመተባበርም ከፖሊስ ከህግ ባለሞያው ከሌሎች አጋር ድርጅቶች እና ከህብረተሰቡጋር አብሮ መስራት የሚቻልበትን መንገድ ይህ ፕሮጀክት በእነዚህ ሶስት አመት ቆይታው እንዲመቻች ያስችላል ተብሎ ይታመናል፡፡
   
         UNFPA በኢትዮጵያ ከሀያ በላይ ከሚሆኑ ሌሎች ድርጅቶችም ጋር የተለያዩ ስራዎችን ይሰራል፡፡ እነዚያ ድርጅቶች በህብረተሰቡ ውስጥ ግንዛቤ የማስጨበጥን ስራ ጨምረው ሌሎችንም ማህበራዊ ጉዳዮች ያከናውናሉ፡፡ ከዚህ ውስጥ የኢሶግ ድርሻ ከእነዚያ ድርጅቶች ጋር በመቀናጀት በጾታዊ ጥቃት ዙሪያ ለሚደርሱ የጤና ችግሮች መፍትሔ የሚሰጥበትን ስራ መስራት ነው፡፡

የእናቶን ሞት መቀነስ የሚያስችሉ የህክምና አገልግሎቶችን መስጠት ማለት በሜሊኒየም ዴቨሎፕመንት ጎልስ የተጠቀሰውን ፣ኢትዮጵያም ቃል የገባችበትን ማሳካት ስለሆነ የኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር ESOG አስፈላጊውን ጥረት ሁሉ በማድረግ የበኩሉን ይወጣል ፡፡

 

ጡት ማጥባት እርግዝናን የሚከላከለው በከፊል ነው፡፡

ፀረደኝ (ከኢሶግ)
                                                Teferdgne@Yahoo.com

    

ሓይ ተፈለዛሬው እትማችን መነሻ የሆነው በማጥባት ጊዜ የሚወሰደው የወሊድ መከላከያ ጉዳይ ነው፡፡ ለመሆኑ ማጥባት በእራሱ እንደወሊድ መከላከያ አይቆጠርምን? የሚለውን መነሻ ጥያቄ በመያዝ ነበር ወደ ዲኬቲ ኢትዮጵያ ያመራነው፡፡አቶ ዳኛቸው አለማየሁ በዲኬቲ ኢትዮጵያ የብሔራዊ ሽያጭ አስተባባሪ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ በዲኪቲ በኩል ስለሚሰጠው የወሊድ መከላከያ አገልግሎት አነጋግረናቸዋል፡፡

*  *      *  *
ኢሶግ/ ዲኬቲ ኢትዮጵያ ማህበራዊ ግብይቱን የጀመረው መቼ ነው?
ዲኬቲ/ ዲኬቲ ኢትዮጵያ ፕሮግራሙን  የጀመረው እንደ እ.አ በ1990 ዓ/ም ነው ፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ በማህበራዊ ግብይት ፕሮግራሙን ሲጀምር   ኮንዶሞችን በማሰራጨት ነው ፡፡ ከተወሰነ ጊዜ በሁዋላ ደግሞ ወደ ወሊድ መቆጣጠሪያዎች በማለፍ በአፍ የሚወሰደውን የወሊድ መቆጣጠሪያ ለመጀመሪያ ጊዜ ገበያ ላይ አውሎአል ፡፡ ከዚያ በመቀጠል ደግሞ የህብረተሰቡን ፍላጎት በተከተለ መንገድ በመርፌ የሚወሰደውን የወሊድ መቆጣጠሪያ በገበያ ላይ አውሎአል ፡፡ እንደሚታወቀው  ባሁኑ ጊዜ በመርፌ የሚሰጠውን መከላከያ ተጠቃሚው ቁጥሩ በጣም ከፍ ያለ ሲሆን በዚያ ምክንያትም ዲኬቲ የተወሰነ ጥናት ካጠና በሁዋላ የወሊድ መቆጣጠሪያው ያስፈልጋል በሚል በማህበራዊ ግብይት ገበያ ላይ አውሎአል፡፡
ቀደም ሲል እንደገለጽኩት የወሊድ መከላከያን በሚመለከት ስርጭቱን መጀመሪያ የጀመርነው በአፍ በሚወሰዱ እንክብሎች  ሲሆን ቀደም ሲል ይሸጡ የነበሩት በወር  ከ(20000-30000) ከሁለት ሺህ እስከ ሶስት ሺህ ይደርስ የነበረ ሲሆን በአሁን  ጊዜ ግን በየወሩ ስርጭታችን  ከ(150000-200000)ከአስራ አምስት ሺህ እስከ ሀያ ሺህ  የወሊድ እንክብሎች በተለያዩ ፋርማሲዎች  እና የጤና ድርጅቶች በመሰራጨት ላይ ይገኛሉ ፡፡  ይህም ማለት የወሊድ መቆጣጠሪያ ተጠቃሚው ቁጥር ከጊዜ ወደጊዜ በጣም ከፍ እንዳለ ነው የሚያሳየን ፡፡
ኢሶግ/ የወሊድ መቆጣጠሪያ አቀማመም ልዩነት አለው ? 

ዲኬቲ/ የወሊድ መቆጣጠሪያ በአብዛኛው ሲዘጋጅ ከሁለት  ቅመሞች ነው ፡፡ እነርሱም ሄትሮ
ጂን  እና ፕሮጀስትሮን የሚባሉ ናቸው፡፡ የእነዚህ የሁለቱ ቅመሞች ውሁድ የሆኑ የወሊድ መቆጣጠሪያዎች አሉ ፡፡ ለብቻ ደግሞ ፕሮጀስትሮን የምንለውን ቅመም የያዘ የወሊድ መቆጣጠሪያ አለ ፡፡ ባብዛኛው የሁለቱ ውህድ የሆኑት የወሊድ መቆጣጠሪያዎች  በአፍ የሚወሰዱ ሲሆን ፕሮጀስትሮን  የተባለውን ቅመም ብቻ የያዙት ደግሞ በአፍ የሚዋጡም  በመርፌ የሚሰጡም አሉ ፡፡ በክንድ የሚሰጡ መከላያዎችም አሉ ፡፡ እናም የወሊድ መቆጣጠሪያዎች አይነት በአብዛኛው በእነዚህ በሄትሮጂን እና ፕሮጀስትሮን ቅመሞች ለይ የተመሰረተ ነው ፡፡ ዲኬቲ ኢትዮጵያ  በመጀመሪያ  ገበያ ላይ ያዋለው የሄትሮጂንና የፕሮጀስትሮን ቅመም ውሁድ የሆነውን የወሊድ መቆጣጠሪያ በአፍ የሚወሰድ ነው ፡፡ በመቀጠል በመርፌ የሚሰጥ ነው እሱም የአንድ ፕሮጀስትሮን ቅመም ብቻ የያዘ የወሊድ መቆጣጠሪያ ነው ፡፡ በመቀጠል ጥናቶችን በምናደርግበት ጊዜ በግሉ የጤና ዘርፍ ላይ አጥቢ እናቶች የሚወስዱት የወሊድ መቆጣጠሪያ በገበያ ላይ ስለአልነበር በተለይም  በአፍ የሚወሰደውን ፕሮጅስትሮን ብቻ ያለውን መከላከያ በገበያ ላይ አውሎአል፡፡
ሌሎቹ የወሊድ መከላከያዎች ማለትም በመርፌ፣  በክንድ የሚወሰዱ አሉ ፡፡ ነገር ግን  ካለው ችግር አንጻር እና ፍላጎቱን በማየት ዲኬቲ ይሄንን ፕሮጀስትሮን ቅመም ብቻ ያለውን  ማለትም የሚያጠቡ እናቶች መውሰድ እንዳለባቸው የሚመከረውን መከላከያ ከጥናት በሁዋላ በገያ ላይ አወሎአል፡፡
የወሊድ መቆጣጠሪያ  ሁለት አይነት ነው ፡፡  ለአጭር ጊዜ የሚወሰድ እና  ለረጅም ጊዜ የሚወሰድ ይባላል ፡፡ ለአጭር ጊዜና ለረጅም ጊዜ ስንል አጭር ጊዜ ማለት አንድ ሳይክል ወስዳ ቢሚቀጥለውም ሌላ ሳይክል ትወስዳለች ማለት ነው ፡፡ለረጅም ጊዜ ሲባል ደግሞ አንድ ጊዜ በክንድ ላይ ከተቀበረ ወይም አንድ ጊዜ ማህጸን ውስጥ ከተቀመጠ ለረጅም ጊዜ ያገለግላል ማለት ነው፡፡አንድ የወሊድ መቆጣጠሪያ የምትወስድ ሴት ሁሉንም የወሊድ መቆጣጠሪያ እንደምርጫዋና እንደሁኔታዋ ብታገኝ ይመረጣል ፡፡
ኢሶግ/ የሚያጠቡ እናቶች የወሊድ መከላከያን ለመውሰድ ምቹ ሁኔታ አለ ? 
ዲኬቲ/ የወሊድ መከላከያውን በመጠቀሙ ረገድ በሁለት አቅጣጫ ማለትም ተጠቃሚም
ጋ ባለሙያውም ጋ ችግር አለ፡፡  ተጠቃሚ ጋ አለ የምንለው ችግር መከላከያውን በሚፈልጉበት ጊሴ በትክክል መረጃን የመስጠት ልምድ ብዙ ጊዜ ይጎላል፡፡ እናቶች አጥቢ መሆናቸውን አይገልጹም፡፡ ባለሞያው ጋ ያለው ችግር  ይሄ የወሊድ መከላከያ ስላልቀረበለት  አንድ የምታጠባ ሴት ብትመጣ የሚሰጣት ፕሮዳክት የለም ፡፡ ሴትየዋ በአፍ የሚዋጥ መከላከያ ብትፈልግም ምን አልባትም  ወደ መርፌ ወይንም በክንድ ወደ ሚሰጥ መከላከያ ይልካታል ፡፡ ይህንን ችግር ለመፍታት (ዲኬቲ) በማህበራዊ ግብይት ፕሮግራም አንዲት ሴት የምትፈልውን ፕሮዳክት እንድታገኝ  ይህንን መከላያ  በግል የጤና ድርጅቶች ላይ እንዲኖር በማድረግ እንዲሁም የተለያዩ ስልጠናዎችን  ለባለሞያዎች በመስጠትና ለድንገተኛ ጊዜ የሚዋጡ እንክብሎችን በገበያ ላይ በማዋል አስተዋጽኦ አድርጎአል፡፡ ሌላው ደግሞ በቅርብ ጊዜ ውስጥ ካሰራጨነው መቆጣጠሪያዎች መካከል  የሄስትሮጅንና የፕሮጀስትሮን ውህድ የሆነ የወሊድ መቆጣጠሪያ አለ ፡፡ ይሄ የወሊድ መቆጣጠሪያ ኢትዮጺያ ውስጥ ለመጀመረያ ጊዜ ነው የገባው ፡፡በመንግስትም ደረጃ  በሌላም የግል ተቋም ውስጥ የገባ አይደለም ፡፡
ኢሶግ/ ጡት ማጥባት በእራሱ የወሊድ መቆጣጠሪያ አይሆንምን ?
ዲኬቲ/ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት አንዲት ሴት በተፈጥሮዋ ጡት  በማጥባትዋ ብቻ
እርግዝናን የምትከላከለው ሙሉ በሙሉ ሳይሆን በከፊል ነው ፡፡
ምን አልባትም ከ(60-65) ፐርሰንት ስድሳ እስከ ስድሳ አምስት በመቶ አካባቢ ነው አንዲት ሴት ጡት በማጥባትዋ ብቻ ወሊድን መከላከል የምትችለው፡፡ ማጥባት ሲባል ደግሞ ብዙ አይነት አጠባብ አለ ፡፡ ሙሉ ጊዜዋን በማጥባት ላይ ያለች ሴት እና አልፎ አልፎ የምታጠባ ሴት እርግዝናውን የመከላከል አቅማቸው የተለያየ ነው ፡፡ ባብዛኛው እቤት ውስጥ ያሉ እናቶች ብዙ ጊዜ ስለሚያጠቡ  የመከላከል አቅሙ ከፍተኛ ሊሆን ይችላል፡፡ ነገር ግን በተለያዩ ምክንያቶች አልፎ አልፎ የሚያጠቡ እናቶች ከሆኑ ማጥባቱ ወሊድን የመከላከሉ አቅም በዚያኑ መጠን ዝቅ ይላል ፡፡ ስለሆነም የምታጠባ እናት በተጨማሪ የወሊድ መቆጣጠሪያዎች  በሆርሞን መልክ ብትወሰድ እርግዝናን የመከላከል አቅሙን ከፍተኛ ያደርገዋል፡፡  
ኢሶግ/ ለሚያጠቡ እናቶች የሚፈቀደው የወሊድ መከላከያ ከሌላው ይለያልን?
ዲኬቲ/ ለሚየጠቡ እናቶች ባብዛኛው የሚፈቀደው ፕሮጀስትሮን የተሰኘውን ቅመም ብቻ
የያዘውን መከላከያ ነው፡፡ ለዚህም ምክንያቱ አንዲት እናት ሄትሮጂንና ፕሮጀስትሮን ውሁድ የሆኑትን መከላከያዎች ልጅ በወለደች ለመጀመሪያ ስድስት ወር ጊዜ ጡት እያጠባች ባለችበት ጊዜ ብትወስድ የሚያመጣው ችግር አለ ፡፡ ይኼውም  የሚመረተው የእናት ጡት ወተት ያንሳል፣ ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የእናት ጡት ውስጥ ያለው ፕሮቲን ጥራት ይቀንሳል ፡፡ ይህ በሚሆንበት ጊዜ  በተዘዋዋሪ ልጁ ይጎዳል፡፡  እናም አንዲት ሴት ከወለደች በሁዋላ ከስድስት ሳምንት ጀምሮ ከፕሮጀስትሮን ቅመም ብቻ  በተለያየ መልክ የተዘጋጁትን የወሊድ መቆጣጠሪያዎችን በማንኛውም የጤና ድርጅቶች ሄዳ መውሰድ ትችላለች ፡፡
ከፕሮጀስትሮንና ሄትሮጂን ውሁድ የሚሰሩ የወሊድ መከላከያዎች ከደም ቡዋንቧ ጋር በተያያዘ ኖርማል የሆነ የደም ዝውውር ችግር ያለባት ወይንም ለአደጋ የተጋለጠች ሴት ካለች ይህንን መከላከያ መውሰድ አይፈቀድላትም፡፡  የጡት ካንሰር ያለባቸው ወይንም ሊኖራቸው ይችላል የተባሉ ሴቶችም ከሁለቱ ቅመሞች ውሁድ የተዘጋጀውን መከላከያ እንዳይወስዱ ይመከራል፡፡


የፕሮጅስትሮን ቅመም ብቻ ያለበትን የወሊድ መቆጣጠሪያ ባብዛኛው በውጭው አለም  ከአርባ (40) አመት በላይ ያሉ ሴቶች የመውለድ እድልን ከፍ ለማድረግ ይጠቀሙበታል፡፡  በዲኬቲ ማህበራዊ ግብይት ይህንን ፕሮግራም የጀመርነው ባለፈው አመት ሀምሌ ወር ላይ ሲሆን ከተጀመረ ጀምሮ ስርጭቱ ወደ መቶ ሺ አካባቢ እንደደረሰ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ይህ ስርጭት ግን ከሌላው የወሊድ ስርጭቶች ጋር ሲተያይ አነስተኛ ነው፡፡ እንደምክንያት የሚቆጠረውም የሚያጠቡ እናቶች ወደፋርማሲም ሆነ አገልግሎቱን ወደሚያገኙበት ጤና ተቋም ሲሄዱ የሚያጠቡ መሆናቸውን ገልጸው ትክክለኛውን መከላከያ አለመውሰዳቸውን ነው፡፡ 

…ስያሜና ዋጋው ቢለያይም ኮንዶም… ኮንዶም ነው፡፡                                                                                         

   ፀሐይ ተፈረደኝ kx!îG                                   

   Teferdgne@yahoo.com

  • በአፍ የሚወሰዱ እና በመርፌ የሚሰጡ የወሊድ መከላከያዎች በኢስትሮጂንና ፕሮጀስትሮን ከሚባሉ ቅመሞች ይዋሃዳሉ፡፡
  • ለምታጠባ ሴት፣ ከደም ቡዋንቡዋ ጋር በተያያዘ በሽታ ያለባት ሴት፣ እንዲሁም የጡት ካንሰር ያለባት ሴትና ከ40 አመት በላይ ለሆኑ ሴቶች ከፕሮጀስትሮን ብቻ የተቀመመ የወሊድ መቆጣጠሪያ መውሰድ የተሻለ ውጤት ያመጣል ተብሎ ይገመታል፡፡

 

      ባለፈው ሳምንት እትም ከወሊድ መከላከያዎች መካከል በእንክብል መልክ በመርፌ እና በክንድ የሚቀበሩትን በሚመለከት የባለሙያ ማብራሪያ አቅርበናል፡፡ በዛሬው እትም ደግሞ ከወሊድ መከላያዎች አንዱ ስለሆነውና ኤችአይቪ ኤይድስን ጨምሮ የአባለዘር በሽታን ለመከላከል ከጥቅም ላይ የሚውለውን ኮንዶምን በሚመለከት በመጠኑ እናስነብባችሁዋለን፡፡ ማብራሪያውን የሰጡን አቶ ዳኛቸው አለማየሁ በዲኬቲ ኢትዮጵያ የብሄራዊ ሽያጭ አስተባባሪ ናቸው ፡፡

                   *    *    *    *    *    *
ኢሶግ/ ዲኬቲ የኮንዶምን ስርጭት መቼ ነው የጀመረው?
ዲኬቲ/ እንደ እ.አ በ/1990ዓ/ም ፕሮግራሙን ሲጀምር ለመጀመሪያ ጊዜ በማህበራዊ ግብይት ፕሮግራሙ ኮንዶሞችን ነው ያሰራጨው፡፡ዲኬት ኢትዮጵያ እስካሁን       ወደ ሰባት መቶ ሚሊየን ኮንዶሞችን አሰራጭቶአል 
ኢሶግ/ የኮንዶም ግብይቱ የሴቶች ኮንዶምን ይጨምራል?
ዲኬቲ/ ዲኬቲ በማህበራዊ ግብይት ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በስነ ተዋልዶ ዙሪያ   የሚያስፈልጉትን የወሊድ መቆጣጠሪያዎችና ከኤች አይ ቪ ጋር በተያያዘ ለመከላከያ የሚረዱትን  የተለያዩ ኮንዶሞች   ለማምጣት ጥረት እያደረገ ነው፡፡      ከእነዚህ ውስጥ የሴቶች ኮንዶምም አንዱ ነው፡፡ በእርግጥ የሴቶች ኮንዶም   ጭርሱንም በአገር የለም ባይባልም በግብይት ደረጃ  ለሕብረተሰቡ በስፋት     አልቀረበም፡፡ ዲኬት ኢትዮጺያ ከመድሐኒት አስተዳደር ቁጥጥር ባለስልጣን ጋር     ይሄንን የሴቶች ኮንዶምን በተመለከተ ወደአገር ውስጥ በስፋት እንዲገባና    እንዲሰራጭ ለማስመዝገብ ጥረት እያደረገ ነው፡፡ ምዝገባው እንደተጠናቀቀ እንደ ማንኛውም የዲኬት ፕሮዳክት በተለያዩ የጤና ድርጅቶች ይቀርባል፡፡
ኢሶግ/ የሴቶች ኮንዶም በአለም ጥቅም ላይ ከዋለ ምን ያህል ጊዜ አስቆጥሮአል?
ዲኬቲ/ የሴቶች ኮንዶም እንግዲህ በአለም ላይ ከመጣ ሀያ አመት ቢሆነው ነው ፡፡   የሚያመርቱት ካምፓኒዎች በጣም ውስን ናቸው ፡፡ ሁኔታውን ስንመለከተው    አንደኛ ካምፓኒዎቹ   ውስን መሆናቸው እና በሁለተኛ ደረጃም ዋጋው ለተጠቃሚዎች ከበድ ስለሚል በቀላሉ ጥቅም ላይ ለማዋል አልተቻለም፡፡ አንድ     የሴት ኮንዶም በኢትዮጺያ ብር ከአምስት ብር በላይ ነው የሚገዛው ፡፡ በሶስተኛ ደረጃ ደግሞ ፕሮግራሙን ባለመጀመራችን ለሴቶቹ ኮንዶሙን በመጠቀሙ ረገድ    ተገቢውን የንቃተ ሕሊና የማዳበር ስራ አልተሰራም፡፡ መድሐኒት አስተዳደር    ቁጥጥር ባለስልጣን ምዝገባውን እንደጨረሰ ከዲኬት ግንዛቤ እንዲኖራቸው ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር ለመስራት ዝግጁ ነው
ኢሶግ/ የወንዶች ኮንዶም ከአምራቾቹ በሚመጣበት ዋጋ ነው ገበያ ላይ የሚውለው?
ዲኬቲ/ ወደ ዋጋው ስንሄድ የወንዶች ኮንዶም አምራቾቹ በሚያከፋፍሉበት ዋጋ ሳይሆን እስከ ሰባት በመቶ እየተደጎመ ነው ለገበያ የሚቀርበው ፡፡ ከገበያ በተገዛበት ዋጋ     ለተጠቃሚ የሚቀርብ ቢሆን ኖሮ አሁን በግል አስመጪዎች ወደ ሀገር      ከሚገቡት ኮንዶሞች ዋጋ ጋር ተመጣጣኝ የሆነ ዋጋ ይጠየቅበት ነበር፡፡ነገር ግን    የተለያዩ የእርዳታ ሰጪ አካላትን ድጋፍ በማስተባበር እስከ ሰባ ከመቶ አካባቢ     የሚደርሰውን ዋጋ በመደጎም ለተጠቃሚ ይቀርባል፡፡  ይሄ የዋጋ ድጎማ           ኮንዶም ላይ ብቻ ሳይሆን ሁሉም የወሊድ መከላያዎችም ላይ እየተደረገ ነው   ባብዛኛው የሚሰራጨው ፡፡ የማህበራዊ ግብይት ዋናው አላማም የሚገለጸው በዚህ መንገድ ነው፡፡ በቁጥርም ጀረጃ ብንመለከት ከአምስት አመት በፊት ዲኬቲ ኢትዮጺያ ውስጥ ያሰራጭ የነበረው     በአመት ከሀያ እስከ ሀያ አምስት    ሚሊየን ኮንዶሞች ነበር ፡፡ አሁን ግን በአመት ስርጭቱ ከሀምሳ አምስት    ሚሊየን በላይ ነው፡፡ እና በቁጥር ደረጃ ስናይ ትልቅ ለውጥ አለ ፡፡ አንዳንድ ጊዜ የቁጥሩ ሁኔታ ፍላጎቱን ግንዛቤውን ሊያሳየን ይችላል ፡፡ ስለሆነም ይሄ ቁጥር      ኮንዶምን በመጠቀም   እረገድ እየተሻሻለ የመጣ ግንዛቤ መኖሩን ይጠቁማል፡፡
ኢሶግ/ በግብይት ላይ ያሉት ኮንዶሞች በስያሜ እና በዋጋ ደረጃ መለያየታቸው ከጥራት      ጋር ይገናኛል?

 ዲኬቲ/ ጥራትን በተመለከተ አንድ ኮንዶም ኢትዮጵያ ውስጥ ሲገባ የመድሐኒት      አስተዳደር ባለስልጣን ጥራቱን ያረጋግጣል፡፡ ኮንዶሞች በተለያየ ስያሜና ዋጋ      ቢሰራጩም ጥራታቸው ግን     የሁሉም እንደተጠበቀ መሆኑን ላረጋግጥ     እችላለሁ፡፡ የኮንዶሞቹ በስያሜ የመለያየት ጉዳይ ምናልባት አንዱ መአዛው ጥሩ     ሆኖ ሌላኛው መአዛ ላይኖረው ይችላል ፡፡ ወይንም ደግሞ ሌላኛው ፍላጎትን     ሊጨምሩ የሚችሉ ክርክር ነገሮች ሊኖሩት ይችላል ፡፡ እንደዚህ አይነት ነገሮችን   ከማካተት ውጪ ጥራታቸውን በሚመለከት ሁሉም አንድ አይነት ጥራት    ያላቸው ኮንዶሞች ናቸው ፡፡    ስያሜና ዋጋው ቢለያይም ኮንዶም ኮንዶም ነው፡፡
ኢሶግ/ ኮንዶሞች በየንግድ ሱቆቹ ከተበተኑ በሁዋላ ስለአገልግሎት ጊዜያቸው       የሚደረግ ቁጥጥር አለ ?
ዲኬቲ/ የጠቀሜታ ጊዜያቸው ያለፈባቸውን ኮንዶሞች የምንቆጣጠርባቸው መንገዶች      አሉን፡፡ ምንጊዜም በስርጭት ላይ ያሉትን ኮንዶሞች በምዝገባቸው ደረጃ መቼ    እንደተመረቱ እና መቼ አገልግሎታቸው እንደሚያበቃ የሚያሳዩን መረጃዎች      አሉን፡፡ ስለዚህ ኮንዶሞቹ የአገልግሎት ጊዜያቸው ከማብቃቱ ከአንድ ወር በፊት     በየሱቆቹ በየፋርማሲዎቹ ያሉትን ኮንዶሞች ጊዜ ከማለፉ በፊት       በመሰብሰብ ለተገልጋዩ እንዳይሸጡ እናደርጋለን፡፡ ሌላው ደግሞ ሻጮቹም      ትርፋቸው እንዳይነካ እና ለሌላም ጊዜ ኮንዶምን የመሸጥ ልማድ እንዲኖራቸው የሚደረግበት አሰራር አለ፡፡ በየችርቻሮው ሱቅም ሆነ በግምጃ ቤቶች የኮንዶምን    አቀማመጥ በተመለከተ ዲኬቲ በሁሉም ክልል መስተዳድሮች የሽያጭ      ሰራተኞች ያሉት በመሆኑ የሽያጭ ሰራተኞቹ በወር እንድ ጊዜ በኢትዮጺያ     ውስጥ ባሉት ወደ ዘጠና በመቶ በሚደርሱት ሱቆች በመሄድ ትምህርት   ይሰጣሉ፡፡  በራሪ ወረቀቶችን በማዘጋጀትም አያያዙ እንዴት መሆን እንዳለበት      ልምዱን እንዲቀስሙ ከማድረግም ባሻገር ጥሩ አቀማመጥ ላደረጉ ደግሞ ዲኬቲ ሽልማት የሚሰጥበትም አጋጣሚም አለ ፡፡ ይህ አሰራር ሌሎችም    ተበረታትተው ያንን ልምድ በመውሰድ የኮንዶም የጠቀሜታ ጊዜው እንዳያልፍ    እና ለተለያዩ     ችግሮች እንዳይጋለጥ ጥረት ያደረጋሉ፡፡
ኢሶግ/ ኮንዶምን በመጠቀም ጊዜ የተለያዩ ችግሮች (መንሸራተት፣መቀደድ…)ይገጥማል   ይባላል፡፡ ይህ ለምንድንነው ?

ዲኬቲ/ ኮንዶም ችግር አለው ሲባል ችግሩ በሁለት በኩል ነው፡፡ አንደኛው የተጠቃሚው      ችግር ሲሆን ሌላው ከኮንዶሙ ከራሱ የሚከሰት ነው፡፡ ኮንዶም ጊዜው      ሲያልፍበት ወይንም ደግሞ ኮንዶሞች የሚቀመጡበትን ደረጃ በትክክል      ካልተጠቀምን ችግሩ ሊከሰት ይችላል፡፡  ለምሳሌ …

  • ኮንዶም ሙቀቱ ከአርባ ዲግሪ ሴንቲግሬድ በላይ በሆነ መብራት ወይንም ሙቀት ባለበት አካባቢ አይቀመጥም ፡፡
  • ኮንዶም የጸሀይ ብርሀን በቀጥታ በሚያገኘው ቦታ እንዳይቀመጥ ይመከራል፡፡   ተጠቃሚውን በተመለከተ ደግሞ ያለው ችግር…
  • ባብዛኛው ለረጅም ጊዜ ኮንዶምን በኪስ ወይም በቦርሳ ይዞ የመሄድ ነገር ካለ ኮንዶሙ ከጥቅም ላይ እንዲውል ሲደረግ በሙቀትና በመፈጋፈግ ላሽቆ ስለሚቆይ የመቀደድ ሁኔታን ያመጣል፡፡
  • በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ በግንኙነት ወቅት ሴትዋ ዝግጁ ካልሆነች በሚፈጠረው መፈጋፈግ ምክንያት ኮንዶሙ የመቀደድ እድሉ የሰፋ ነው ፡፡
  • በሶስተኛ ደረጃ ደግሞ ባብዛኛው ኮንዶሙ ከፓኬት ውስጥ በሚወጣበት ጊዜ ጥንቃቄ በሌለው ሁኔታ በጥርስ ወይንም በመቀስ የመቁረጥ ሁኔታ ካለ ኮንዶሙ የመቀደድ እድሉ ይሰፋል፡፡

  ኮንዶምን በመጠቀም ረገድ ሊደረጉ የሚገባቸውን ጥንቃቄዎች ኮንዶም በሚሸጥባቸው ፓኮዎች ውስጥ በዝርዝር የተቀመጠ ስለሆነ ያሉትን መረጃዎች በትክክል በመከተል ተገልጋዮች እንዲጠቀሙበት ዲኬቲ መልእክት ያስተላልፋል፡፡   አሁን ባሉት መረጃዎች ወደ ዘጠና አምስት በመቶ (95%) ሕብረተሰቡ ስለ ኮንዶም ምንነትና ጠቀሜታ ያውቃል፡፡ ነገር ግን የባህርይ ለውጥ መጥቶአል ለማለት አያስደፍርም፡፡ የኮንዶም አጠቃቀምን በተመለከተ አሁንም ወደፊትም ምንጊዜም በጠነከረ መልኩ ትምህርቱ መሰጠት አለበት፡፡ ምክንያቱም ከትውልድ ትውልድ እየቀጠለ በየጊዜው ለአቅመ አዳም ወይም ለአቅመ ሄዋን የሚደርሱ ዜጎች ስለሚተኩና ለመረጃውም አዲስ ስለሚሆኑ ተገቢውን የጥንቃቄ መረጃ መስጠት ይገባል ፡፡             

የጾታ መብትን ማክበር…የሰብአዊ መብትን ማክበር ነው፡፡
                                                       ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
                                                       Teferdgne@yahoo.com

በጾታ ጥቃት ምክንያት ለሚከሰተው የጤና ችግር ተገቢውን አገልግሎት መስጠትን በሚመለከት በመንግስት ደረጃ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴርን አሰራር እና እቅድ የሚገልጹት አቶ ጸጋዬ በዳኔ በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የአርሶ አደር ጤና ማበልጸግና በሽታ መከላከል ዳይሬክቶሬት ረዳት ዳይሬክተር ናቸው፡፡

ኢሶግ / በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር እይታ የጾታ ጥቃት ከምን ደረጃ ላይ ነው?
ጤ/ጥ /ጾታዊ ጥቃት በአገራችን በጥናት የተደገፈ ብዙም ነገር ባይኖረውም ችግሩ ግን      የጎላ መሆኑ ይታወቃል፡፡ በተከታታይነት በፕሮግራም በተነደፈ መልኩ    የመከላከል ስራ እየተሰራ ባይሆንም ነገር ግን በተለያዩ ጊዜያት ከፕሮግራሞች   ጋራ በቅንጅት እየተሰራ ያለ ጉዳይ ነው፡፡  ትክክለኛውን ቁጥር መግለጽ ባይቻም   ካሉት ከአንዳንድ ድርጅቶች ጥናት ስንነሳ ጾታዊ ጥቃት በአገራችን እንዳለ ነው፡፡    ጾታዊ ጥቃት የሚደርሰውም ባብዛኛው በሴቶች ላይ ነው፡፡ ከአንዳንድ ጥናቶች   በመነሳት የምናየው መረጃ ከአስር በመቶ እስከ ሀምሳ በመቶ ጥቃቱ   የሚደርሰውም አብረዋቸው ከሚኖሩ ከቅርብ ቤተሰቦች መሆኑ ተረጋግጦአል፡፡
ኢሶግ/ ለጾታዊ ጥቃት መንስኤ የሚባሉት ምንድናቸው?
ጤ/ጥ/ ጾታዊ ጥቃት የተለያዩ መንስኤዎች አሉት፡፡ አንዱም የትምህርት ደረጃ አናሳ መሆን ነው፡፡ ሁለተኛው የኢኮኖሚ ዝቅተኛነት ሲሆን ሌላው ደግሞ የባህል      የጎጂ ልማድ ድርጊትም ነው፡፡ እምነትም የተወሰነ አስተዋጽኦ አለው፡፡ ሌላው ደግሞ በተለያዩ ችግሮች ማለትም ከፖለቲካና ከማህበረሰባዊ ከኢኮኖሚያዊ     ችግሮች ጋር   የሚከሰቱ አጋጣሚዎችን በመጠቀም ጥቃቱ ሊፈጸም ይችላል፡፡     ጾታዊ ጥቃቶች ስንል በሴት   ወይንም በወንድ ላይ የሚፈጸሙ የተለያዩ     ችግሮችን የሚመለከት ሲሆን ከእነዚህ ግን በግብረስጋ ግንኙነት የሚፈጸመው   ጥቃት ከፍተኛውን ስፍራ ይይዛል፡፡ ይህም ሴቶችን ከሕጻንነት እድሜ ጀምሮ    በተለያዩ የእድሜ ክልሎች የሚገኙትን ሁሉ የሚያካትት ችግር ነው፡፡
ኢሶግ/ በጾታ ጥቃት ምንያት የሚሰርሰውን የጤና ችግር ለመከላከል የሚያስችል የጤና ፖሊሲ አለ?
ጤ/ጥ/ በጤና ጥበቃ አሰራር የጾታ ጥቃትን ተንተርሶ ለሚመጡ የጤና ችግሮች መፍትሔ የመስጠቱ ነገር በጤና ፖሊሲ ውስጥ  የተካተተ ነው፡፡ ይህም ከሴቶ ጋር በተያያዘ፣እንዲሁም በቤተሰብ ጤና አገልግሎት ጋር በተያያዘ  በሚሰሩ   የጤና አገልግሎቶች የተካተተ ነው፡፤ ከስርአተ ጾታ ጋር በተያያዘም እንደዚሁ     የአገልግሎት ሽፋን የሚሰጥበት ሁኔታ አለ ፡፡ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ     መንገዶች በጾታ ጥቃት ምክንያት የሚከሰቱ የጤና ችግሮችን ለመከላከል የሚያበቁ ስራዎች እየተሰሩ ነው ማለት ቢቻልም ግን በቂ አይደለም፡፡ገና     በእንጭጭነት ላይ ያለ ነው፡፡ በአገር ደረጃ ገና ብዙ ስራ መሰራት የጠበቅብናል ፡፡ ይህ ችግርም በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ብቻ የሚወገድ ሳይሆን ከተለያዩ    መስሪያ ቤቶች ማለትም ከህግ አውጭው፣ከፖሊስ ፣ከሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ   ፣ከትምህርት ሚኒስቴር እና   ከተለያዩ የሚመለከታቸው መስሪያ ቤቶች ጋራ    በቅንጅት ተሰርቶ እልባት ሊገኝለት የሚገባው ጉዳይ ነው፡፡ ነገር ግን በጤና      ጥበቃ ሚኒስቴር ጤናን አስመልክቶ በሚሰሩ ስራዎች ውስጥ አብሮ ተካቶ እየተሰራ ነው ፡፡
ኢሶግ/ ጾታዊ ጥቃት የሚያስከትለው የጤና ችግር ምድነው?
ጤ/ጥ/ጾታዊ ጥቃት የሚደርስባቸው ሰዎች ለኤችአይቪ ሊጋለጡ ይችላሉ፡፡ ከዚህም     በተጨማሪ ሴቶችን ላልተፈለገ እርግዝና ያጋልጣቸዋል፡፡ ያልተፈለገ እርግዝና      ደግሞ ላልተፈለገ ውርጃ የሚያጋልጥ ሲሆን ላልተፈለገ ውርጃ መጋለጥ ደግሞ ብዙ ሴቶችን ዘላቂ ለሆነ የጤና ችግር የሚዳርግና ከዚያም በላይ ለሕልፈት   የሚዳርግ ነው፡፡ በዚህ አደጋ ስር የወደቁትን ሰዎች ለይቶ ይህንን ያህል ናቸው    ብሎ ለመግጽ አይቻልም፡፡ ምክንያቱም የጤና አገልግሎት ፈልገው የሚመጡትን  ብቻ እንጂ ጉዳቱን ይዘው በየቤታቸው የሚማቅቁትን ማወቅ ስለማይቻል ነው፡፡ ስለዚህ በጾታ ጥቃት ምንያት የሚከሰቱትን የጤና ችግሮች ለማስወገድ      የሚመለከታቸው መስሪያ ቤቶች ሁሉ በጋራ የሚሰሩበት ሁኔታ ቢፈጠር      ለህብረተሰቡ ግንዛቤ በመፍጠር የጤና ችግሮችን ወደሚያስከትሉ      ሁኔታዎች ከመገባቱ በፊት ማህበረሰቡ የራሱን ጥንቃቄ እንዲያደርግና እርምጃ      እንዲወስድ እንዲሁም የጤና ችግሩ ከደረሰ በሁዋላ ደግሞ የህክምና አገልግሎት    እሚያገኝበትን መንገድ ማመላከት ይቻላል፡፡ በተጨማሪም ሕብረተሰቡ ይህንን   የጾታ ጥቃት በመከላከሉ ረገድ የራሱን ጥሩ ባህርይና አመለካከት ፈጥሮ      ለወደፊት ጥሩ እይታ እንዲኖረው ለማድረግ የሚያስችሉ ስራዎች መስራት      ያስፈልጋል ፡፡ ህብረተሰቡ የጾታ ጥቃትን በመከላል ረገድ የራሱን ድርሻ በምን     መልኩ ሊወጣ እንደሚችል በማስተማሩ ረገድ የመገናኛ ብዙሀንም ትልቅ ድርሻ አላቸው፡፡
ኢሶግ /በጾታ ጥቃት ምክያት የሚከሰቱትን የጤና መጉዋደሎች የጤና ተቋማቱ   በተገቢው መስራት አለመስራታቸውን መከታተያ መንገዱ ምንድነው?
ጤ/ጥ/ቁጥጥርና ክትትሉን  በሚመለከት ጥናት ባልተደረገበት ሁኔት  በዚህ መልክ    ነው ለማለት እጅግ አስቸጋሪ ነገር ነው፡፡ነገር ግን ካለው አሰራር አኩዋያ     ስንመለከት በህግ በኩል ያሉ ሰዎች ከጤና ጥበቃ አኩዋያ ሊወጡት የሚገባ      ድርሻ ይኖራቸዋል፡፡ የጤና ባለሙያው ደግሞ ያለውን የጤና ችግር ለህግ ክፍሉ     ተገቢውን ማስረጃ መስጠት ይጠበቅበታል፡፡ በዚህ ዙሪያ ባሉ አሰራሮች በእርግጥ የሚታዩ ችግሮች አሉ፡፡ ያ ደግሞ በሂደት ከሚመለከታቸው አካላት ጋራ መድረክ   በመፍጠር ችግሮቹ እንዴት ነው የሚወገዱት በሚል በአገር አቀፍ ደረጃ የሚረዳ      አሰራርን በመዘርጋት ፣በየጊዜው እየተገናኙ ተከታታይ በሆነ መልኩ አቅጣጫ የሚያሳይ የምክክር መድረክ መፍጠር ተገቢ ነው የሚሆነው፡፡ ይህ ከተደረገ     የህብረተሰቡን የጤና ንቃተ ሕሊና በማሳደግ የመከላል ስራው በተጠናከረ     መንገድ እንዲሰራ ማድረግ ይቻላል፡፡ የጾታን መብት ማክበር ማለት በአለም     አቀፍ ደረጃም የሰው ልጅ የሰብአዊ መብትን ማክበር ማለት ነው፡፡ በአንድ ሐገር ያለውን የፖለቲካ፣ኢኮኖሚና ማህበራው ችግሮችን ማስወገድ የሚቻለውም የመላው ሰው የሰብአዊ መብት ሲከበር በመሆኑ ይህንን በማንኛውም መስክ    የተሰማሩ መስሪያ ቤቶች እንዲከበር ማስቻል ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህንን ችግር      የማስወገዱ ሁኔታ ከቤተሰብም ይጀምራል፡፡ በቤተሰብ ደረጃ በውይይት የተነሳ ጉዳይ ወደ አካባቢ ይዘልቃል፡፡ ከአካባቢም ወደሐገር ከሐገርም ወደአህጉር    እንዲሁም ወደአለምአቀፍ ደረጃ ተሸጋግር ስርነቀል መፍትሔ ሊያገኝ ይችላል፡፡    በዚህ መልክ በተቀናጀ መልኩ ካልተሰራ ውጤትን ማምጣት ስማይቻል ጾታዊ     ጥቃትን ለማስወገድ ሁሉም እኔን ይመለከተኛል ብሎ ቅንጅታዊ ስራ መስራት      ይጠበቅበታል፡፡
ኢሶግ/ ችግሩን ለማስወገድ ምን ቢደረግ የተሸለ ይሆናል?
ጤ/ጥ/ ለጤና ባለሙያዎች ስልጠና በመስጠት ፣የማስተማሪያ መርጃ መሳሪያዎችን      በማዘጋጀት እና በማከፋፈል በአገሪቱ ውስጥ ያሉት ድርጅቶች ለሕብረተሰቡ   ተገቢውን አገልግሎት እንዲሰጡ ለማድረግ እና አዋጆቹን እንደገና    በመከለስ መስተካከል የሚገባቸውን ነገሮች በመመልከት ላይ ነን፡፡ የመሰረታዊ አሰራር ሂደት ለውጥን (BPR) እንዲያቀላጥፍ ሕብረተሰቡ ተገቢውንና ጥራቱን የጠበቀ የጤና ሽፋን እንዲያገኝ የሚያስችል አዋጅና መመሪያ እየተዘጋጀም    ስለሆነ እነዚህ በሞላ ቅንጅት ፈጥረው ወደስራ ሲገባ ወደፊት ጥሩ ሁኔታ    ይፈጠራል ብዬ እገምታለሁ፡፡
          በማንኛውም ሁኔታ ከጾታ ግጭት ነጻ የሆነ ማህበረሰብ ማፍራት ይቻላል፡፡ ከጾታ ግጭት ነጻ የሆነ ሕብረተሰብ ተገኘ ማለት ደግሞ በጾታ ጥቃት   ምክንያት የሚከሰትውን የጤና ችግር ማስወገድ ተቻለ ማለት ነው፡፡      እንደሚታወቀው ጤናማ ህብረተሰብ አምራች ነው፡፡ አምራች ከሆነ ደግሞ የአገሪቱን እድገት ሊያፋጥን የሚችል ነው ፡፡ ይህንን ማድረግ ከተቻለ አገሪቱ አሁን ካለችበት እጅግ ደሀ ከሚባለው መስመር ወጥታ ቢያንስ መካከለኛ የእድገት ደረጃ አላቸው ከሚበሉት ተርታ ልትመደብ የምትችልበትን እድል ይፈጥራል፡፡ ስለዚህ ጥሩ ከሰራን የአገራችንን የእድገት ደረጃ እንቀይርበታለን፡፡    ጥሩ ካልተሰራ ደግሞ አሁን ካለንበትም ወደሁዋላ እንዳይጎትተን መጠንቀቅ    ይገባል፡፡ በአሁኑ ወቅት የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ሰላሳ ሺህ የጤና አገልግት    ሰራተኞችን አሰልጥኖአል፡፡ እነሱም የጤና አገልግሎቱን በማዳረስ ረገድ ትልቅ   ኃይል ናቸው፡፡ በተጨማሪም በአሁኑ ሰአት በየከተማው የጤና ኤክስቴንሽን      ሰራተኞች በኤችአይቪ ኤይድስ፣በቤተሰብ ጤና ፣በህጻናት ጤና አገልግሎት እና በተለያዩ ፕሮግራሞች ላይ የህብረተሰቡን ንቃተ ሕሊና ማሳደግና የጤና   አገልግሎቱ ተጠቃሚ እንዲሆን ያደርጋሉ፡፡ በዚህ መልክ ከተሰራ ለወደፊቱ      ተገቢው ለውጥ እንደሚመጣ እሙን ነው፡፡
***************************************************

በሕክምናው ላይ እምነት አንዲኖር……..
                                      ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
የአምድ ተሳታፊያችን ሃና ይትባረክ ትባላለች፡፡ በደረሰባት የጤና ችግር ምክንያት ያየችውን እማኝነት አድርሳናለች፡፡ እኛም ለአንባቢ ብለናል፡፡
              *      *      *
     እድሜዬ  አርባ ከሞላ በሁዋላ ማለትም ዘግይቼ ነበር አንዲት ሴት ልጅ የወለድኩት፡፡ በእርግጥ ቀደም ሲል ሁለት ወንዶች ልጆች አሉኝ፡፡ እናም ከወለድኩ በሁዋላ ልጅትዋን ማጥባት በምጀምርበት ሰአት ወተት ከጡቴ በደንብ አይወርድም ነበር ፡፡ ነገር ግን ቀደም ሲል ከወለድኩዋቸው ሁለቱ ልጆች ጋር ተመሳሳይ ሁኔታ  ስለነበረ ያው የተለመደ ነው በሚል ችላ አልኩት፡፡  ልጅትዋ በመጀመሪያም ወተት ስላልነበረው ቀጥሎም የጡቱ ጫፍ ቆስሎ ስነበር ቁስሉ ይዳን ሲባል ስለቆየና በሁዋላም መድረቅ ስለጀመረ የእናትዋን ጡት ምንም ሳትጠባ ነው የተቋረጠው፡፡በተለይም አንደኛው ጡት ወተቱ መኖሩ ከውስጡ እየታየ መስተዋት የሚመስል ስስ ቆዳ የሚመስል ነበር ጫፉን ሽፍን ያደረገው፡፡
     ወደ አንድ ወር ገደማ ሲሆነኝ አለች ሀና ታሪኩዋን ስትቀጥል ጡት መያዣዬን ሳወልቅ እንደቆዳ ነገር ቅርፍ ብላ ከጡቱ ላይ ተነሳች፡፡ የተነሳችበት  ቦታም የማዠት ሁኔታ ነበረው ፡፡ የጡት መያዣው ጠቦኝ ነው ማለት ነው ብዬም ሰፋ ያለ ጡት መያዣ መጠቀም ጀመርኩ፡፡ ግን አሁንም ከተወሰነ ጊዜ ማለትም ከአንድ ሳምንት በሁዋላ እንደገናም በተመሳሳይ ሁኔታ የጡት መያዣው የጡቱን ጫፍ ላጥ አደረገው፡፡ ከዚያ በሁዋላ ወደ ሐኪም  ሄድኩኝ፡፡ በመጀመሪያ ያገኘሁዋት ሴት ሐኪም ጡት መያዣ ቢጠብሽም እንደዚህ መሆን የለበትም አለችኝ ፡፡  ትንሽ ቀን ቆይቼ ደግሞ ገላዬን ታጥቤ በፎጣ ስጠረግ እንደገና ተላጠና እንደማዠት አለና ወዲያውም ድርቅ አለ፡፡ ቁስል ነው እንዳልል ወዲያው ድርቅ ይላል፡፡  ደህና ነው እንዳልል ደግሞ እየቆየ ይላጣል ፣ያዣል፡፡ ሁኔታው ግራ ስላጋባኝ ወደ ወለድኩበት ክሊኒክ ሌላ ዶክተር ጋ ሄድኩኝ፡፡ እሱ ደግሞ ጡቱን አገላብጦ ከፈተሸ በኋላ ጡቱ ውስጥ የሚጠጥር እጢ መሰል ነገር የለም፡፡  ስለዚህ የቆዳ ችግር ነው በማለት የሚቀባ ቅባት ሰጠኝ፡፡ ቅባቱን ስቀባው ይለሰልሳል ፡፡ ግን ቅባቱን ስተወው ይደርቃል፡፡ ስለዚህ እንደገና ወደሌላ ቦታ የቆዳ ሐኪም ጋ ሄድኩኝ፡፡ እንዲህ እንዲህ እያልኩ በሁዋላ የሄድኩበት ሐኪም ቀደም ሲል ከታዘዘልኝ ቅባት መሰል መድሀኒት ሌላም ተጨማሪ አድርጎ አዘዘልኝ ፡፡ ነገር ግን አሁንም ከወር በሁዋላ እንደገና መድረቅ ጀመረ፡፡ መድሀኒቱም አልቆ ነበር፡፡እኔም ግራ ስለገባኝ በግሌ መረጃ ከኢንተርኔትና ከሌሎች የህክምና ሰነዶች ማፈላለግ ጀመርኩኝ፡፡ እናም በእንደዚህ ያለ ሁኔታ በቆዳ መድረቅ መላጥ በመሳሰሉት ምልክት እያሳየ የሚከሰት የካንሰር ዘር እንዳለ አነበብኩኝ፡፡ ከዚያም በጣም ስለደነገጥኩ ይሄ ነገር እንግዲህ ችግር አለው ማለት ነው አልኩና ሌላ ሐኪም ጋ ደግሞ ሄድኩኝ፡፡ ከቆዳ መቆጣት ጋር በተያያዘ ካልሆነ በስተቀር ሌላ  ምንም ችግር የለውም ብሎ ቀደም ብሎ ሌላው ሐኪም የሰጠኝን ቅባት እና ሌላም መድሀኒት በተጨማሪ ሰጠኝ፡፡ አሁን ደግሞ ቆዳው ቀደም ሲል ይደርቅ የነበረው ቀርቶ በጣም ከመለስለሱ የተነሳ ብጭቅ የሚል ነገር ሆነ፡፡  አንድ ጠንከር ያለ ችግር ከሌለው በስተቀር እንደዚህ ለወራት ያህል የማይድንበት ምክንያት ስላልገባኝ ከጡቱ ላይ አንድ ሳምፕል ወስደህ መርምልኝ ስለው ከዚህማ ምንም ሳምፐል መውሰድ አያስፈልግም ብሎ መለሰለኝ፡፡ እኔ ግን አይሆንም በላቦራቶሪ ይታይልኝ ብዬ እምቢ ስለው እሺ በማለቱ የምርመራው ውጤት ሲገኝ የሐኪሙን ቀደም ሲል የነበረ እምነት የሚፈታተን ስለነበር በጣም ግራ ተጋባ፡፡ እናም ይህ ውጤት ትክክል ያልሆኑ መወገድ ያለባቸው ሴሎች እንዳሉ ያሳያል ስለዚህ በአስቸኳይ ወደ ቀዶ ሕክምና መሔድ አለብሽ ነበር ያለኝ ትላለች ሃና፡፡
     ሀና የጡቴ ነገር አሳሳቢ እየሆነ በመምጣቱ ከዚህ በሁዋላ ግን ወደካንሰር ሕክምና መሔድ እንዳለብኝ እራሴን አሳመንኩና ወደ ካንሰር ስፔሻሊስቶች መሄድ ጀመርኩ ትለናለች፡፡ ወደ ሀያ ቀን ገደማ የፈጀው ቀጠሮ ተሳክቶ ያገኘሁዋቸው ሐኪም በዚህ መስክ ልምዱ ስላላቸው ለየት ያለ እርምጃ ነበር የወሰዱት፡፡ በጣም ጊዜ ፈጅተው በእጃቸው ጡቱን ዳስሰው ፈልገው ትንሽ ምልክት ስላዩ ቀጣይ የህክምና ምርመራ ይደረግ ብለው በአልትራሳውንድ ታየሁ፡፡ በዚህም ጊዜ በወተት ማመንጫው ውስጥ የሆነ የፈሳሽ ምልክት አገኙ፡፡ ይህ ሳይፈስ ወይንም ሳይጠባ የቀረ ወተት ሊሆን ይችላል በማለት አሁንም በተገኝው የምርምራ ውጤት ስላልረኩ እንደገና ለፓቶሎጂስት መሩኝ፡፡  ውጤቱም የካንሰር ነገር በጣም አጠራጣሪ መሆኑን ይገልጻል ፡፡
     ከዚያ በሁዋላ ግን ሕይወትን ለማትረፍ አፋጣኝ የህክምና እርምጃ መውሰድ እንዳለብኝ አመንኩ የምትለው ሀና በቀጣይ የገጠማትን ሁኔታ እንዲህ ትገልጻለች፡፡
ስለካንሰር ሲወራ የሆነ የሚገድል ነገር እንዳለ ማንም ሰው ስለሚያስብ ፍርሀት አለ፡፡ እኔም በጡት ካንሰር የተጎዱ ብዙ ሰዎችን ሁኔታ ስላየሁ ለሕይወቴ በጣም በመፍራቴ የተለያዩ ሐኪሞች ጋ ሄጃለሁ ፡፡ እናም በሕክምናው ጉዳይ ቶሎ መልስ የሚሰጠኝ ሐኪም እየፈለግሁ ግን አለማግኘቴ አስፈራኝ ፡፡ በተለይም በመጨረሻ ደረጃ ለሀያ ቀን ገደማ ቀጠሮ ይዤ ያገኘሁዋቸው ባለሙያ ያለውን እውነታ አውቀውታል፡፡   ነገር ግን ለእኔ ሊነግሩኝ ፈቃደኛ አልነበሩም፡፡ በከፍተኛ ሁኔታ አጠራጣሪ ነው የሚለው ውጤት መቼም በአመዛኙ የሚሄደው ካንሰር ይሆናል ወደሚለው ስለሆነ ብዙ አሳሰበኝ፡፡ በዛ ላይ የቀጠሮዎች ሁኔታ እንደዚህ በስጋት ላይ ላለ በሽተኛ የበለጠ ያሳስባል፡፡ በዛ ላይ
የሐኪሙ መልስ አይ እኔ ምንም ልነግርሽ አልችልም ሂጂና የሚቀጥለውን ምርመራ አድርጊ ብቻ ሆነ ፡፡በጣም ብዙ ሰነዶችን ሳገላብጥ ያገኘሁት መረጃ እንደሚጠቁመው ብዙ የካንሰር ታማሚዎች ከበሽታው መዳን የሚችሉበት መንገድ እያለ ግን አስቀድመው የሚጎዱት በስጋት ምክንያት ነው፡፡
     ከባለቤቴ ጋር ተነጋግረን የተከፈለው መስዋእትነት ተከፍሎ በውጭ አገር ሕክምናው እንዲካሄድ ወሰንን፡፡ የሄድኩት ወደ ታይላንድ ባንኮክ ነበር፡፡ የህመሙን ሁኔታ የሚገልጸውን መረጃ አያይዤ በሆስፒታሉ ለመታከም አንደምፈልግ መረጃውን በላክሁኝ በማግስቱ ነበር መልስ ያገኘሁት፡፡ እነሱም የሚያስፈልገው ሕክምና እንደዚህ ያለ ነው ፣ይህንን ለማድረግ ይህን ያህል ዋጋ ያስከፍላል፣ የሚፈጀው ጊዜ ይህን ያህል ነው የሚለውንና የመሳሰሉትን ጠቃሚ መረጃዎች ለመስጠት ጊዜ አልፈጁም፡፡   የሄድኩበት ሆስፒታል አሉ ከሚባሉ ትላልቅ ሆስፒታሎች አንዱ ጋ ሲሆን አደረጃጀቱ በጣም ዘመናዊ ነው፡፡ ነገር ግን የህክምና ባለሙያዎቹ እውቀት ሲወዳደር እንዲያውም የኛ ሐገር ሐኪሞች ይበልጣሉ የሚያሰኝ አንዳንድ ሁኔታዎችን ታዝቤአለሁ፡፡ ነገር ግን የህክምና መሳሪያዎችና የሕክምናው መስክ ስፋት እኛ ገና ያልደረስንበት ነው ለማለት እችላለሁ፡፡ ብዙዎቹ መሳሪያዎቹ ኢትዮጵያ ውስጥ የሉም፡፡ ያገኘሁት የምርመራ ውጤት ቋንቋው እንኩዋን ሳይለወጥ አንድ አይነት ነገር ነው የነገሩኝ፡፡ ነገር ግን እዚህ አገር ካገኘሁት መረጃ የሚለየው ምንም አይነት ነገር ቢሆን ሊታከም የሚችልና ችግር የሌለው ቀላል መሆኑን ነው፡፡ ይህንን ሀገሬ ላይ ሰምቼው ቢሆን ኖሮ እኔ እዛ ድረስ መሄድ አልፈልግም ነበር፡፡
     በውጭ ካየሁት ሁኔታ እንደተረዳሁት በአገራችን መታረም አለበት ብዬ የማስበው ታካሚውን የማክበርና ታካሚው ተገቢውን አገልግሎት የማግኘት መብት እንዳለው የማመን ጉዳይ ይመስለኛል፡፡ ሌላው የታዘብኩት ነገር ለመረጃ ግልጽ መሆንን ነው፡፡
     ሕክምናውን በተመለከተ ምርመራው ሲደረግ መረጃው እስኪገኝ ድረስ በየጊዜው እኔ እንዳልደክም አስፈላጊውን መረጃ በመስጠት ከቤቴ እንዳልሄድ ወይንም ሲፈልጉኝ ደግሞ እንድሄድ ያደርጉኝ ነበር፡፡ ይሄ በኛም አገር በጣም ሊለመድ የሚገባው አሰራር ይመስለኛል ፡፡ የምርመራው ውጤት ዞሮ ዞሮ የጡት ካንሰር በመሆኑ አስፈላጊው ሕክምና የጡቱን ጫፍ በመቁረጥና እንዲሁም በጨረር በማከም ተካሄዶአል፡፡ እንክብካቤውን መግለጽ በጣም ያስቸግረኛል፡፡
     ሀሳቤን ግን የምደመድመው ትላለች ሃና በውጭ አገር ለመታም አንድ ሰው ቀላል ሕክምና ለማድረግ እንኩዋን ቢያንስ መቶ ሺህ ብር ያህል ያወጣል፡፡ በሆስፒታሉ ውስጥ የሚታየው ታካሚ ኢትዮጵያዊ ቁጥር ለማመን የሚያስቸግር ነው፡፡ ነገር ግን ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ለሕክምና ወደውጭ ሲሄድ የሚያጠፋው ገንዘብ ጊዜና ጉልበት ከግምት ውስጥ ቢገባ ሐገርንና ወገንን በእጅጉ ሊጠቅም እንደሚችል ምንም አያጠራጥርም ፡፡
     በእርግጥ በብዙ ሁኔታዎች በኢትዮጵያ የሕክምናው ስራ እየተሻሻለ መሆኑ አይካድም፡፡ ግን አሁንም የቀሩ ነገሮችን ለማሟላት መንግስትን ብቻ መጠበቅ ሳይሆን ባለሀብቶችም ቢሳተፉ ጥሩ ይመስለኛል፡፡ ባለሐብቶቹ  ፊታቸውን ወደ ሕክምናው መስክ  ዞር ቢያደርጉ በመስኩ ያለውን እድገት ስለሚያፋጥነው ወደውጭ ለሕክምና የሚፈሰው ገንዘብ በሀገር ውስጥ ለልማትና እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ፡፡ከዚህ ውጪ ግን ታካሚውን ወደውጭ ሐገር ከመሄድ የሚያስቀር አይነት እንክብካቤና  ግምት ወይም ክብር ለታካሚው የመስጠት ነገር ከሕክምና ባለሙያዎቹ ይጠበቃል፡፡  ስለዚህ መሰረታዊው ነገር በሕክምና ባለሙያዎቹ እጅ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ በሕክምናው ላይ እምነት አንዲኖር ሊያደርጉ ይችላሉ፡፡ በእርግጥ ይህንን የሚያሙዋሉ ሙያተኞች እንደሚኖሩ አልጠራጠርም፡፡ ነገር ግን ባጠቃላይ የህክምና ባለሙያው ሁሉ የስራ መርህ እንዲሆን ሕዝብ ይጠብቃል፡፡

 

ሀና ይትባረክ

...ቂጥኝ፣ጨብጥ፣ከርክር…የመሳሰሉት በሽታዎች ዛሬም አሉ?
                                      ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
teferdgne@yahoo.com

በአለማችን ከጥንት ጀምሮ የሚታወቁ የተወሰኑ በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት የሚተላለፉ የሚባሉ በሽታዎች የነበሩ ሲሆን ከእነሱም በሀገራችን አሰያየም ቂጥኝ፣ጨብጥ፣ከርክር በሚል የሚታወቁት ከፊሎቹ ናቸው፡፡ እናም እነዚህ ቀደም ባሉት ዘመናት የሚታወቁት በሽታዎች እውን ዛሬም አሉ ይሆን ሲሉ የጠየቁን ከአውቶቡስ ተራ አቶ ብዙአየሁ አንተነህ ናቸው፡፡ ይህንኑ ጥያቄ መነሻ በማድረግ ከዶክተር እያሱ መስፍን ጋር ቆይታ አድርገናል፡፡ ዶ/ር እያሱ መስፍን የማህጽንና ጽንስ እስፔሻሊስትና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ረዳት ፕሮፌሰር ናቸው፡፡

///                 ///          ///
በግብረስጋ ግንኙነት ጊዜ የሚተላለፉ በሽታዎች የሚለው አባባል በአለም አቀፍ ደረጃ ቃሉ እራሱ አወዛጋቢ በመሆኑ የአባላዘር በሽታዎች ወይንም የአባላዘር ኢንፌክሽኖች (STI) በሚል እንዲተካ ተደርጎአል፡፡ የአባላዘር በሽታዎች ቁጥራቸው እስከ ሰላሳ እንደሚደርስ ምንጮች ያስረዳሉ፡፡ የአባላዘር በሽታዎች በተለይም በሴቶች ላይ ከሰባ(70) እስከ ሰማንያ(80) በመቶ ያህል ሕመሙ የማይሰማ እንዲያውም ሕመሙ መኖሩ እንኩዋን እስከማይታወቅ ደረጃ የሚደርስ በመሆኑ ታማሚዎች በሌላ የጤና ችግር ምክንያት ምርመራ ሲያደርጉ የሚታወቅበት አጋጣሚ ብዙ ነው፡፡ በህብረተሰቡ ዘንድ ቀደም ሲል የሚታወቁት ማለትም ከርክር ጨብጥ ቂጥኝ በመባል የሚገለጹት የአባላዘር በሽታዎች አሁንም አሉ፡፡ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር በ2005 እንደውጭው አቆጣጠር ባደረገው ጥናት ጨብጥና ከርክር ስርጭታቸው ምን ያህል ነው የሚለውን ለጊዜው መናገር ቢያስቸግርም ነገር ግን ኤችአይቪና ቂጥኝ ስርጭታቸው ምን ያህል እንደሆነ የሚታወቅ ነው፡፡ለምሳሌ ቂጥኝ (2.7%) ሁለት ነጥብ ሰባት በመቶ ያህል እንደሆነ በጥናቱ ተጠቁሞአል፡፡ ይሄም መረጃው የተገኘው ለክትትል ጤና ተቋማት ለምርመራ ከሄዱት ነብሰ ጡር እናቶች ውስጥ የተገኘ እንጂ ወደ ሕክምናው ያልሄዱ ሌሎች ተጎጂዎች እንደሚኖሩ መገመት ይቻላል፡፡ በእርግጥ እያንዳንዱ የአባላዘር በሽታ የየራሱ ምልክት ያለው ነው፡፡ ሆኖም ግን እነዚህ እስከ ሰባ እና ሰማንያ በመቶ ያህል አይታወቁም የተባሉት በአጋጣሚ በሌላ ምርመራ ካልተገኙ ሊታወቁ የሚችሉት በቆይታቸው ወቅት አንድ የጤና ችግር ሲፈጠር ብቻ ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ በቂጢኝ በሽታ የተያዘ ሰው ምንም ሳይታወቅለት ወይንም ምንም ሕክምና ሳይደረግለት ሀያ አመት ያህል ከቆየ በተለያዩ የከፉ የጤና ችግሮች በሽታው እራሱን ሊገልጽ ይችላል፡፡
የበሽታዎቹን አይነት ስንመለከት አንዳንዶች በባክቴሪያ ምክንያት የሚከሰቱ ሲሆን ሌሎች ደግሞ በቫይረስ ምክንያት የሚከሰቱ ናቸው፡፡ ለምሳሌ ጨብጥ፣ ቂጥኝ የመሳሰሉት በቫክቴሪያ
መንስኤነት የሚከሰቱ ሲሆን በቫይረስ ከሚተላለፉት ደግሞ ኤችአይቪን መጥቀስ ይቻላል፡፡  ሌሎችም (Fungus & Protozoa’s) ፈንገስ እና ፕሮቶዙዋስ የሚባሉ ከማህጸን ፈሳሽ በማምጣት የጤና ችግር የሚያስከትሉ የህመም ምክንያቶች ወይንም ኢንፌክሽኖችም አሉ፡፡
በተለምዶ እንደሚታወቀው የአባላዘር በሽታ የወንድ ወይንም የሴት በሚል የሚከፈል  አይደለም ፡፡ ነገር ግን ለምሳሌ Candida ካንዲዳ የሚባለው የ fungal ፈንጋል ኢንፌክሽን ሙሉ በሙሉ እንደአባላዘር ባይወሰድም ባብዛኛው ግን ሴቶችን የሚያጠቃ ነው፡፡ይህ ኢንፌክሽን በእርግጥ ወንዶች ላይ ብዙ አይታወቅም፡፡ ነገር ግን መጠኑ ይለያይ እንጂ ሁሉም በሁለቱም ጾታዎች የሚታዩ ናቸው፡፡
የአባላዘር በሽታዎችን ምንነት ለመለየት  በህክምናው አደረጃጀት ውስጥ የሚከፋፈሉበት እና እንደ አይነታቸው የሚመደቡበት አሰራር አለው፡፡ እሱም (syndromic approach) ሲንድሮሚክ አፕሮች የሚባል ነው፡፡ የዚህም አሰራር የአባላዘር በሽታዎችን በሲንድሮም ወይንም በሚያሳዩት የምልክት አይነት ከፋፍሎ ተመሳሳይ ሕክምና መስጠት ነው፡፡ ለምሳሌ ዝርዝር የሆነ የላቦራቶሪ ምርመራን የማይፈልግ ወይንም ቢፈልግ እንኩዋን ያንን አገልግሎት በሚመለከት በእኛ አገር አቅም አብዛኛዎቹ ምርመራዎች የሌሉ በመሆኑ ለሶስተኛው አለም አገሮች አሰራር እንዲያመች ተደርጎ በአለም የጤና ድርጅት (WHO) የተዘጋጀ ነው፡፡ ይህንን የኢትዮጵያም መንግስት እንደውጭው አቆጣጠር ከ2000 ዓ/ም/አካባቢ ጀምሮ ተቀብሎት እየሰራበት ነው፡፡ እናም (syndromic approach) በዛ አደረጃጀት መሰረት ሲታይ ለምሳሌ ዋና የሚባሉ አይነቶች ወደ ሰባት አሉ፡፡ በአብዛኛው በህብረተሰቡ ዘንድ የሚታወቁት ጨብጥ፣ከርክር፣ቂጥኝ የሚባሉት እና የመሳሰሉት በእነዚህ ክፍፍሎች ውስጥ የሚካተቱ ናቸው፡፡ ለምሳሌ አንዱ/ urethral discharge syndrome /

 ዩሪትራል ዲስቻርጅ ሲንድሮም ይባላል፡፡ ይህም ማለት በአባላዘር የሚተላለፍ ከሽንት መሽኛ ቱቦ ፈሳሽ የማውጣት ችግር ማለት ነው፡፡ እንደዚህ አይነት ሕመም ከሚያስከትሉት  መካከል ጨብጥ (Gonorrhea ) የሚጠቀስ ነው፡፡ ይህ የአባላዘር በሽታ በሴትም በወንድም የሚከሰት ነው፡፡ ሕክምና በሚሰጥ ጊዜ ከሽንት መሽኛ ቱቦ የሚወጣውን ፈሳሽ (urethral discharge)  እንኩዋንስ ለታማሚው ለጤና ባለሙያውም ለመለየት የሚያስቸግር ነው፡፡
ስለዚህ በሽታዎቹን በተመሳሳይ ከሚያስከትሉት የጤና ችግር በመነሳት በ(syndromic approach) በሚባለው አንድ ላይ አብሮ የማከም ሁኔታ ነው ያለው፡፡ ይኸውም አሰራር የተጀመረው በኢትዮጵያ ከተደረገው ጥናት በመነሳት በሽንት መሽኛ መስመር ፈሳሽ የሚያመጡ ችግሮች የትኞቹ ናቸው በሚል በመለየትና ምን አይነት ሕክምና ተገቢ ይሆናል ከሚል የተጀመረ  ነው፡፡ ጨብጥ ብቻም ሳይሆን ቂጥኝም እንደዚሁ ቂጥኝ ተብሎ ሳይሆን ዩሪትራል ዲስቻርጅ ሲንድሮም በሚለው ዘርፍ ውስጥ ተካትቶ ነው ሕክምናው የሚሰጠው፡፡ በጤና ጣቢያም እንዲሁም በመንግስት ሆስፒታሎች ወይንም በሌሎች ቦታዎች በተሰጠው ስልጠና መሰረት ይህንን በመከተል የህክምና አገልግሎቱ ይሰጣል፡፡
የአባላዘር በሽታዎች እንደበሽታው አይነት የህመሙ ስሜት ይለያያል ፡፡ ለምሳሌ ጎኖሪያ ወይንም የጨብጥ በሽታ እንደመግል ብጫ የሆነ ፈሳሽ፣ ሽንት ሲሸኑ የማቃጠል ስሜት ይኖረዋል ፡፡ይሄ በተለይም የሁለቱ ሕመሞች መለያ ጸባይ ነው፡፡ በእርግጥ እንደአይነታቸው የመግሉ መጠንና የከለሩ አይነት ሊለያይ ይችላል፡፡
ቀደም ባሉ ዘመናት በግልጽ ይታወቅ የነበረና ዛሬም ካሉት የአባለዘር በሽታዎች ከርክር የሚባለው አንዱ ነው፡፡ቀደም ሲል በተጠቀሰው የአባላዘር አይነት አመዳደብ ውስጥ ከርክር የሚገኘው  የብልት መቁሰል ወይንም መላጥ በሚለው ስር ነው፡፡ ከርክር የወንድ በሽታ ነው በሚል በተለምዶ የሚገለጽ ቢሆንም ነገር ግን ይህ የብልት መቁሰል በሁለቱም ጾታዎች ላይ የሚከሰት ነው፡፡  ከርክር የውጭ የመራቢያ ክፍልን በማቁሰል የሚታወቅ በመላው አለምም በእኛ አገርም የሚታይ ችግር ነው፡፡ ከርክር በሁለቱም ጾታዎች የሚከሰት ቢሆንም ነገር ግን በወንዶች ላይ ለየት የሚያደርገው በጊዜው ተገቢው ሕክምና ሳይሰጥ ከቀረና መላጡ የወንዱን ብልት ዙሪያውን ዞሮ ከገጠመ ብልቱን እስከመቆረጥ ሊያደርስ ይችላል፡፡


ባጠቃላይ የአባላዘር ኢንፌክሽኖች ዋነኛ መተላለፊያቸው በግብረስጋ ግንኙነት ነው ይባል እንጂ በሌሎችም መንገዶች ይተላለፋሉ፡፡ ከደም ንክኪ ወይንም ደም ከሌላ ሰው በመውሰድ በመሳሳም በአፍ የሚደረጉ ወሲባዊ ድርጊቶች ወይንም( Homo ) ወንዶች በወንዶች ላይ በሚያደርጉት የፊንጢጣ የወሲብ ግንኙነት ሊሆን ይችላል፡፡ ለምሳሌ ጎኖሪያ ወይንም ጨብጥ በሚያስከትለው ሕመም በፊንጢጣ ወሲብ በሚፈጽሙት ላይ ከፊንጢጣቸው መግል ሊወጣ ይችላል፡፡ ቂጥኝ ደግሞ (oral sex) የወንዱን ብልት በሴትዋ አፍ ውስጥ በማስገባት በአፍ ወሲባው ድርጊትን በሚጠቀሙ ላይ ቁስለቱ በብልት እንደሚታየው ሁሉ በአፍ ውስጥ ሊቆስል ይችላል፡፡ እነዚህ ብቻም ሳይሆኑ ሌሎችም በፊንጢጣ ላይ ሕመምን ሊያስከትሉ የሚችሉ የአባላዘር ሕመሞች አሉ፡፡ ሌላው የቂጥኝ አንዱ የመተላለፊያ ዘዴው በእርግዝና ጊዜ ከእናት ወደልጅ ነው፡፡ ስለዚህ  ቂጥኝ ነብሰጡር እናቶች ለእርግዝና ክትትል ወደጤና ማእከላት ሲሄዱ መደረግ ከሚገባቸው ዋነኛ ክትትሎች አንዱ ነው፡፡ ይሄም ቂጥኝ በእርግዝና ጊዜ ወደ ጽንሱ እንዳይተላለፍ ለመከላከል ይረዳል፡፡

ሴትን ልጅ መግረዝ ቆሻሻ እንደማስወገድ ይቆጠር ነበር፡፡
                                           ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
                                           teferdgne@yahoo.com
 እንደውጭው አቆጣጠር በ1997 ዓ/ም ነበር ሁለት እህትማማቾች አንድ ሀሳብ ይዘው ከነበሩበት አካባቢ ወደትውልድ መንደራቸው ከምባታ እና ጠምባሮ ዞን መለስ ያሉት ፡፡ በዚያም የመሰረቱት አገር በቀል ግብረ ሰናይ ድርጅት ከምባታ ሜንቲ ጌዝሜ ቶጴ ይባላል፡፡ ከሁለቱ እህትማቾች አንዱዋ ማለትም ፍቅርተ ገብሬ በህይወት የሌሉ ሲሆን እስከአሁን ስራውን ይዘው የዘለቁት ቦጋለች ገብሬ የዚህ እትም እንግዳ ናቸው፡፡ከምባታ ሜንቲ ጌዝሜ በትክክል ስራውን ከጀመረ እነሆ አስር አመት ሞሎቶታል፡፡ ይህንኑ በሚመለከት ከጥቅምት (19-21 )ድረስ በከምባታ ዱራሜ የተለያዩ ፕሮግራሞችን ባካተተ መልኩ በአል ተከብሮአል፡፡ መስራቿ ቦጋለች ገብሬ እንደሚሉት ለሀያ አመታት ያህል ከኖሩባት አሜሪካ ወደ ትውልድ መንደራቸው ተመልሰው ይህንን ድርጅት ካቋቋሙበት ምክንያት አንዱ …አንዲት ልጅ እንኩዋን ከግርዛት ባድን …የሚል እንደነበር ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ መልስ ሰጥተዋል፡፡ በከምባታ ጠምባሮ ዞን የተጀመረው ስራ ዛሬ ወደ ወላይታ ፣ጉራጌ ፣አርባ ምንጭ እና ኦሮሚያ ክልል ዘልቆአል፡፡ ቦጋለች ገብሬ ከኢሶግ ዘጋቢ ጋር ቆይታ አድርገዋል፡፡
ኢሶግ/ በስነተዋልዶ አካልነቱ የሚታወቀውን የሴትን ልጅ ብልት ትልተላ የማስቀረት ስራው
     አጀማመር ምን ይመስል ነበር ?
ቦጋለቸ/
የሴትን ልጅ ብልት ትልተላና ሌሎች ተያያዥ የስነተዋልዶ ጤናጉዳዮች ኤችአይቪን ጨምሮ በሚመለከት ከህብረተሰቡ ጋር መወያየት ስንጀምር ችግሩ የተወሳሰበና ግዙፍ ሆኖ ነበር ያገኘነው፡፡ ምንጊዜም አንድን ስራ ሲጀምሩት በጣም የሚያስፈራ ይሆንና ወደውስጡ ሲዘለቅ ግን ስራውን ስራው እራሱ እንደሚመራው ነበር የተረዳሁት፡፡ ስለዚህም የስነተዋልዶ ጤናን ችግር ለመፍታት ህብረተሰቡን ማሳመን አስፈላጊ በመሆኑ በልጅነቴ ወደ እማውቀው ቤተክርስቱያን በመሄድ ለመጀመሪያ ጊዜ ህብረተሰቡን በእነዚህ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች አወጋገድ ላይ እና ስለኤችአይቪ ኤይድስ ሳነጋግር የገጠመኝ አንድ ነገር ነበር፡፡ በጊዜው የምናገረውን ነገር ህብረተሰቡ በደንብ ነበር ያዳመጠኝ፡፡ ብዙ ጠንካራ ጠንካራ የሆኑ ጥያቄዎችም ተነስተውልኝ ነበር፡፡ ከነዚህም ጥያቄዎች መካከል …ቦጌ…አንቺ ልጅ በነበርሽበት ጊዜ ያ ጠባብ ወንዝ የነበረው አሁን እየተሸረሸረ እየሰፋ በመሄዱ ብዙ ጉዳት አድርሶአል፡፡ ብዙ ሰዎችንም እየጎዳብን እየገደለብንም ነው፡፡ ስለዚህ ለእኛ የሚቀድመው  አንቺ ከምትነግሪን ነገር ይልቅ ይህንን ድልድይ ማሰራት ነው… አሉኝ፡፡ እኔም በወቅቱ …እሺ …እናንተ የምትችሉትን አግዙን…እኛ ደግሞ የምንችለውን እናድርግ በማለት በመስማማታችን  በአንድ አመት ገደማ ድልድይ ሰራን፡፡ እንግዲህ ከዚያ ወዲህ ላለው ስራ መቃናት ትልቁን አስተዋጽኦ ያደረገው የዚህ ድልድይ መሰራት ነው፡፡ ይህም አንድን ነገር ተግባራዊ ለማድረግ ህብረተሰብን ማዳመጥ አንዱና ትልቁ ሊለመድ የሚገባው ነገር መሆኑን የተማርንበት  ነው፡፡
ኢሶግ/ ሴቶች የስነተዋልዶ ጤናቸውን እንዲጠብቁ ለማድረግ የተጠቀማችሁበት ዘዴ ምንድነው?
ቦጋለች/
ሴቶች የስነተዋልዶ ጤናቸውን እንዲጠብቁ መማር አለባቸው፡፡ ሴቶች ከተማሩ ስለሚፈልጉት ነገር ተገቢውን ግንዛቤ ለማግኘት ሰፊ እድል ይፈጥርላቸዋል፡፡ በተጨማሪም ዛሬ ያሉትን የህብረተሰብ ክፍሎች ካላስተማርን የወደፊቱን ትውልድ ልናድን አንችልም፡፡ ምክንያቱም ዛሬ ያለችው ሴት የወደፊቱንም ልጅ ስለምትወልድ ያንን የሚተካውን ትውልድ ማስተማር ትችላለችና፡፡ ግርዛት በአካባቢያችን ቆሻሻ ማስወገድ ተብሎ ነው የሚጠራው፡፡ ስለሆነም የሴትን ግርዛት ለማጥፋትና የሴት ልጅ ግርዛት የሚያመጣውን ጠንቅ ለማሳወቅ በዚህ ችግር ምክንያት መውለድ ያቃታቸውን ሴቶች  ሁኔታ ማሳወቅ የመሳሰሉትን ሁሉ መስራት ይጠበቅብን ነበር፡፡ ስለጤና ጉዳይ ትምህርት መስጠት ብቻም በቂ ስለማይሆን  የእናቶች ሆስፒታል መስራትም አስፈላጊ በመሆኑ ይህንንም ተግብረናል፡፡  ሴቶቹ እራሳቸው በሚገጥማቸው የስነተዋልዶ ጤና ሁኔታ ላይ እንደፈለጉ እንዲያዙና እራሳቸውንም እዲጠብቁ ለማስቻል ደግሞ የኢኮኖሚ ጥገኝነታቸውን ማላቀቅ አንዱ ጉዳይ ነው ተብሎ ስለታመነ ሴቶቹ የሙያና አንዳንድ የእደጥበብ ውጤቶችን ሰርተው ለገበያ የሚያበቁበት ማእከል በመስራት እንዲጠቀሙበት አድርገናል፡፡
ኢሶግ/ ምን ያህል ሴቶች ከግርዛት ድነዋል?
ቦጋለች/
ይህንን ያህል ሴቶች ከግርዛት ድነዋል ለማለት ለጊዜው ያስቸግራል፡፡  ነገር ግን በዩኒሴፍ የተደረገው ጥናት እንደሚያመለክተው በዞኑ ያሉ ሴቶች በሙሉ ከግርዛት ድነዋል የሚል እምነትን ያሳድራል ፡፡ ባለፈው አመት የተደረገውና ዘንድሮ ይፋ የሆነው ጥናት እንደሚያሳየው (3%) የሚሆኑ ወንዶች እና ሴቶች ወንድ ልጄ የተገረዘች ልጅ ቢያገባ ወይንም ሴት ልጄ ተገርዛ ብትዳር ነው የምመርጠው ሲሉ (97 %) የሚሆኑት ደግሞ የልጆቻቸውን አለመገረዝ ነው የመረጡት፡፡ ይህ ማለት ግን ግርዛትን መቶ በመቶ አጥፍተናል ማለት አይደለም፡፡ ነገር ግን በአንድ በኩል ህጉን በመጠቀም በሌላ በኩል ደግሞ የህብረተሰቡ አባላት በየፊናው የየበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ ማድረግ ተችሎአል፡፡ እያንዳንዱ ሰው የማን ልጅ ተገረዘች፣የማን ልጅ አልተገረዘችም እስከማለት የሚደርስ መረጃን የመቀባበል ሁኔታ አለ፡፡ በትምህርት ቤትም ውስጥ የቷ ልጅ ተገርዛለች የቷ ልጅ አልተገረዘችም የሚል መረጃ ስላለ አንዱ የአንዱ ዘበኛ ሆኖ እየጠበቀ ነው ማለት በሚያስችል ሁኔታ የሴት ልጅ መገረዝ ጎጂነትን ሕብረተሰቡ ተቀብሎታል፡፡
ከምባታ ሜንቲ ጌዝሜ በአሁኑ ወቅት ያልተገረዙ ሴት ልጆች ክለብን አቋቁሞአል፡፡ መስሪያ ቤቱ ካቋቋመው ክለብ ውጭም ያልተገረዙ ሴት ልጆች እራሳቸውን በማደራጀት ክለብ እያቋቋሙ ይገኛሉ፡፡ እነዚህ ሴት ልጆች እራሳቸውንና ሌሎችንም ከግርዛት ለመከላከል የበኩላቸውን ጥረት ከማድረግ ባሻገር በህብረት በመቆማቸው አንድ የሰሩት ገድል አለ፡፡ …ከመካከላቸው አንዷ ልጅ ከከምባታ ወደሐዲያ ተጠልፋ ትወሰዳለች፡፡ እነዚህ ሴት ልጆች አምስት በመሆን ከቤተሰብም ሆነ ከህግ ጋር ሳይመክሩ በቀጥታ ልጅቷ ወዳረፈችበት በመሄድ እነሱም መልሰው ጠልፈው ወደመንደሩዋ ያመጡዋታል፡፡ ከዚያም ልብሱዋን አልብሰው የትምህርት መርጃ እቃዎችን (እርሳስ፣እስክሪፕቶ፣ደበተር..ወዘተ…አሟልተው ወደ ወላጆቿ በመመለስ ወደ ትምህርት ቤቷም እንድትገባ ያደርጉአታል፡፡ ለአንድ አመት ያህልም ማንም እንዳይነካት ተራ በተራ እየጠበቁ …ከማንም እንደማታንስና በራስዋ እንድትተማመን እዲሁም ትምህርቷን በትክክለኛው መንገድ ምንም ሳትሸማቀቅ  እንድትማር አድርገዋታል፡፡ምክንያቱም በአካባቢው አንዲት ሴት ልጅ አንዴ ከተጠለፈች በሁዋላ ተመልሳ እንድትማር ወይንም ወደቤተሰብ እንድትቀላቀል የሚያደርግ ልምድ ያልነበረ በመሆኑና ያ ትክክል እንዳልሆነ ነው ልጆቹ ለህብረተሰቡ ያሳዩት፡፡ እነዚህ ልጆች ይህንን አጉል ልማድ ተቋቁመው ልጅቱ ሕይወቷን በትክክለኛው መንገድ እንድትቀጥል አስችለዋታል፡፡ ይሄ የሚያሳየው ሴቶቹ ልጆች ምን ያህል እየተደራጁና እራሳቸውንም እየጠበቁ ከመሆኑም በላይ ጉዳዩ የህዝብ ባለቤትነትን እያገኘ መምጣቱን ነው፡፡
ኢሶግ / የወንዶቹ ምርጫ የተገረዘች ወይስ ያልተገረዘች ሴት ነው?
ቦጋለች/


በእርግጥ ወንዶቹ የተገረዘችን ሴት ማግባት አንፈልግም ቢሉ አያስደንቅም፡፡ ምክንያቱም የባህሪይ ለውጥ ባንድ ጊዜ አይመጣም፡፡ ትልቁ ነገር የሴት ልጅ ግርዛት መቅረት አለመቅረቱ የሴቷ ልጅ መብት መሆኑን ሴቶቹ ለወንዶቹ በግልጽ የሚነግሩበትና መፍትሔውን የሚያቀርቡበት ጊዜ ላይ መደረሱ ነው፡፡  ሴቷ …በግርዘት የሚወገደው የእኔ አካል ነው፣ ወላጆቼ ሲፈጽሙት የኖሩት እኔን ለመጠበቅ ሲሉ ነበር፣ ነገር ግን አሁን ጎጂ መሆኑ ስለተረጋገጠ ከአሁን በሁዋላ አልገረዝም የሚሉ ሴት ልጆችን አፍርተናል፡፡ በመሰረቱ የሴትን ልጅ ብልት መተልተል ከወሲብ ፍላጎት ጀምሮ በወሊድ ጊዜ እንዲሁም በግርዛት ወቅት ከሚተላለፉ በሽታዎች ጭምር እጅግ ጎጂ ልማድ መሆኑን መላውን ሕብረተሰብም በማስተማር ላይ ስለሆንን በብዙዎች ዘንድ ተቀባይነትን ያገኘ ነገር ነው፡፡ስለዚህ ያልተገረዘች ሴት አናገባም የሚሉ ወንዶች ቢኖሩ ምናልባትም በውጤቱ የማይረኩበት ኑሮ ለመመስረት እየተዘጋጁ መሆኑን ቢረዱት መልካም ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ግን ሴቶቹ በራሳቸው አካል ላይ ሌላ ሊያዝበት እንደማይገባ ከሚያውቁበት ደረጃ ደርሰዋል፡፡ ሕብረተሰቡም ቢሆን የገዛ ልጁን እያወቀ አይጎዳም፡፡ አይተለትልም፡፡ ግርዛት የሃይማኖት እና የባህል አካል ነው ብለው በማመን ነው የሴት ልጅን ብልት ሲገርዙ የኖሩት፡፡ ያ ግን ትክክል አለመሆኑን በተገቢው እያስተማርን  እና የመረጃ ክፍተትን ለማሟላት ጥረት እያደረግን በመሆኑ በአብዛኛው አሁን ድርጊቱ እየቆመ ነው፡፡ ስለዚህ  የጋብቻ ምርጫው የወንዶች ብቻም ሳይሆን የሴቶችም ነው፡፡ ስለሆነም ወንዶቹ ያልተገረዘችን ሴት ለጋብቻ ቢፈልጉም የሴቷ ፍላጎት ካልታከለበት እንደፈለጉ ከማያገኙበት ደረጃ ተደርሶአል፡፡መፈቃቀዱ የወንዶችም የሴቶችም ነውና፡፡ 

በእርግዝና ወቅት የሰውነት መገጣጠሚያዎች ይላላሉ…
                                           ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
በእርግዝና ወቅት የአካል እንቅስቃሴን አስፈላጊነት በተመለከተ ማብራሪያ የሰጡን ዶ/ር ደሴ እንግዳየሁ የማህጸንና ጽንስ ሕክምና እስፔሻሊሰት ናቸው፡፡ ዶ/ር ደሴ እንግዳየሁ የኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር አባል ናቸው፡፡
                ------------------------///---------------------------
አንዲት ሴት በምትጸንስበት ጊዜ የሚታዩ የተለያዩ አካላዊ ለውጦች ይኖራሉ፡፡ ከሰውነት መጠቁዋቆር ጀምሮ በእግር እጅና ፊት እንዲሁም ሰውነት የማበጥ ሁኔታዎች ይከሰታሉ፡፡ እብጠቱ የሚከሰትበት ምክንያት እርግዝናው እያደገ ሲመጣ የደም መልስ የሚባለውን ከእግር ወደልብ ደምን የሚመልሰውን የደም ቡዋንቡዋ ስለሚጫነውና የደም ዝውውሩን ሰለሚያውከው ነው፡፡ በእርግዝና ጊዜ ፈሳሽ በሰውነታችን ውስጥ ይጨምራል፡፡ ያ ፈሳሽ በሚጨምርበት ጊዜ ከደም ቡዋንቡው እየወጣ በቆዳችን ስር ይከማቻል፡፡ይሄ ነገር በብዛት የሚከሰት ሲሆን ከሌሎች ሕመሞች ጋር በተያያዘ ካልሆነ በስተቀር እንደ ችግር አይቆጠርም፡፡ ነገር ግን ከደም ግፊት ፣ከኩላሊት ከመሳሰሉት ሕመሞች ጋር የሚያያዝ ከሆነ አሳሳቢ ነው የሚሆነው፡፡ በህመም ምክንያት ማለትም የልብ የኩላሊት የጉበት የመሳሰሉት በሽታዎች ያሉበት ሰውም በእግሩ ወይንም በሰውነቱ ላይ እብጠት ሊኖረው ይችላል፡፡ በእርግዝናው ምክንያት የሚከሰተው ግን አሳሳቢ አይደለም፡፡የሰውነት መጠቋቆር የሚከሰተው ደግሞ ኢስትሮጂን እና ፕሮጀስትሮን የተባሉት  ሆርሞኖች (ቅመሞች)  መጠናቸው ስለሚጨምር ነው፡፡
     በእርግዝና ጊዜ የልብ ሕመም፣ የደም ዝውውር ችግር ፣ስኩዋር የመሳሰሉት ሕመሞችም ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡ በእርግዝና ጊዜ የሴቶች የደማቸው መጠን ብዛቱ ማለት ነው ሊጨምር ይችላል፡፡ ይህ በሚሆንበት ወቅት ደግሞ ልብ ስራው ይጨምራል፡፡ በደቂቃ የሚተነፈሰው ትንፋሽም በደቂቃ መጠኑ ከፍ ይላል፡፡
     እርግዝናው ጊዜውን እየጨመረ በሄደ ቁጥር የሆድ አካባቢ ወደፊት ነው የሚሳበው፡፡ በዚህ ወቅትም የጀርባ አከርካሪ አጥንት የመለጠጥ ሁኔታ ይታይበታል፡፡ በዚህም ምክንያት በትክክል ቀጥ ማለት ያለበት ሰውነት ሆድ ወደፊት ሲገፋ ወገብም አብሮ ሰለሚለመጥ አቋምን ማስተካከል ይከብዳል፡፡ ነብሰ ጡር እናቶች ቀደም ሲል ይሰሩት የነበረውን ስራ ወይንም ያደርጉ የነበረውን እንቅስቃሴ ማድረግ ይከብዳቸዋል፡፡ ለምሳሌ ብስክሌት ትነዳ የነበረች ሴት ብትሆን ሚዛኗን መጠበቅ ስለሚያቅታት ልትወድቅ ትችላለች፡፡
በእርግዝና ጊዜ የሰውነት መገጣጠሚያዎቻች እና የወገብ አጥንት በዳሌ አካባቢ ያሉ አጥንቶችና መገጣጠሚያዎች ልጅ በሚወለድበት ጊዜ ሰውነት እንዳይጠብቅ ለማድረግ ቅድመ ዝግጅት ሰለሚያደርጉ ይላላሉ፡፡
እርግዝናው የሰውነት አቋምን አለመስተካከል፣ድካምን እንዲሁም የተለያዩ የጤና ችግሮችን ሊያስከትል የሚችል ሲሆን እነዚህን ለማቃለልም የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ማድረግ በባለሙያዎች ይመከራል፡፡
በእርግጥ በሳይንሱ መንገድ ብዙ ጊዜ የሃሳብ ለውጦች አሉ፡፡ እንደውጭው አቆጣጠር በ1980ዎቹ ዓ/ም እና ከዚያ በፊት በነበረው እምነት አንዲት ሴት ስታረግዝ እረፍት ታድርግ ተብሎ ነበር የሚመከረው ፡፡ አሁን ግን የሚመከረው በእርግዝና ጊዜ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ማድረግ ጥቅም አለው በሚል ነው ፡፡ በተለይም ከእርግዝና በፊት የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ያደርጉ የነበሩ እናቶች ያንን ልምድ እንዲቀጥሉ ይመከራል፡፡ ምክንያቱም ሰውነታቸው ስብ እንዳይጨምርና ውፍረት እንዳይመጣ እንዲሁም የመተንፈስ፣የእንቅልፍ፣የአመጋገብ ችግር እንዳይከሰትባቸው ነው፡፡ የስኩዋር ፣ የልብ ፣የደም ዝውውር ችግር ለመሳሰሉት ሁሉ እንዳይጋለጡም ይረዳል፡፡
በእርግጥ ሁሉም እርጉዞች የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ያድርጉ ወይንም እስፖርት ይስሩ ማለት አይቻልም ፡፡ አንዲት እርጉዝ ወደ እስፖርቱ ከመሄድዋ በፊት ሐኪምዋን
ማማከር ይገባታል፡፡ ምክንያቱም አንዳንድ ጊዜ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ማድረግ የሚከለከልባቸው ሁኔታዎች ይኖራሉና ፡፡
በእርግዝና ጊዜ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ የማድረግ ጠቀሜታ

  • የተፈጠረውን የአካል መላላት፣የወገብን ሕመም እንዲሁም ወልደው ከተነሱ በሁዋላ እናቶች የሚደርስባቸውን የሰውነት አለአግባብ መወፈር (መዘረጋገፍ ) ሁሉ ለመቆጣጠር የሚያስችለው የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ሲደረግ ነው፡፡
  • እርጉዞች እስፖርት ቢሰሩ የእለት ተእለት እንቅስቃሴያቸውን ውጤታማ በሆነ መንገድ ለመስራት ይረዳቸዋል፡፡ በብዛት በእርግዝና ጊዜ የሚከሰተውን ድካም ያስወግድላቸዋል፡፡ እንቅልፍን በትክክል ለመተኛት ያግዛል፡፡ የምግብ ፍላጎታቸውም የተሻሻለ እንዲሆን ይረዳል፡፡ የሆዳቸው ግድግዳም እንዲጠናክር ስለሚያግዝ በስተመጨረሻው የመዘርገፍ ባህሪይ እንዳይኖረው ይሆናል፡፡ እስፖርት የሚሰሩ እርጉዝ ሴቶች አስቀድሞውኑም ጡንቻዎቻቸው ስለሚጠነክሩ ምጡ የማይጠናበት ወይንም በቀላሉ የሚወልዱበት ሁኔታ ይመቻችላቸዋል፡፡  ከወለዱ በሁዋላም ቦርጭ እንዳይኖራቸው የሚረዳ ሲሆን ወልደውም አርባ አምስት ቀን ካረፉ በሁዋላ እስፖርቱን እንዲቀጥሉ ይመከራል፡፡
  • ሰውነት የተስተካከለ እንዲሆን  ፣ማህጽን እንዳይላላ ፣በእስፖርት መታገዝ አለበት፡፡ ልጅ ሲወለድ ጭንቅላቱ እስከ 9.5 ሴንቲ ሜትር ድረስ የሚደርስ ዙሪያ ነው ፡፡ ስለዚህ ልጁ ሲወለድ የሚወጣው ሰውነትን ለጥጦ ማለትም አስፍቶ ሰለሆነ ያንን ልጁ የወጣበትን አካል (ብልት፣ማህጸን) በእስፖርት ማጠንከር በጣም ይመከራል፡፡ በእርግጥ እስፖርት ባይሰራም በእራሱ አካሉ የሚመለስ ሲሆን ግን የበለጠ እንዲጠነክር እስፖርቱ ያግዛል፡፡
  • ሴቶች እድሜያቸው እየገፋ ሲሄድ የሽንት መቆጣጠር ችግር፣የማህጽን ወደታች የመሹለክ፣የሰገራ መውጫው በማህጸን ውስጥ የመውጣት፣የመሳሰሉት ችግሮች ይከሰታሉ፡፡ ስለዚህም ሴቶች በእርግዝናቸው ጊዜም ሆነ ከእርግዝና ውጪ ባለው ጊዜያቸው እስፖርት  በመስራት ማህጸናቸውን  ወይንም የሽንትና የሰገራ መውጫ አካላቸውን ማጠንከር ይገባቸዋል፡፡ የግድ እስፖርት ቤት በመሄድ ብቻም አይደለም፡፡ ልክ ሰገራ ወይንም ሽንት ሊያመልጥ ሲል ለመያዝ ሲባል ሰውነትን ቆንጠጥ ወይንም ያዝ እንደሚደረገው ብልታቸውን ያዝ ያዝ እያደረጉ እስፖርት ማሰራትም ይጠቅማል፡፡

በእርግዝና ወቅት እስፖርት መስራት የሚቻልበትና የማይቻልበት ሁኔታ  ፡፡
እርግዝና በሶስት ደረጃ ነው የሚከፈለው፡የመጀመሪያው አስራ አራት(14) ሳምንት፣ሁለተኛው እስከ ሀያ ስምንት(28) ሳምንት ከዚያም እስከ አርባ ሁለት(42 )ሳምንት ድረስ በሚል ይከፋፈላል፡፡
የመጀመሪያው አስራ አራት (14) ሳምንት ማለት እስከ ሶስት ወር ድረስ ያለው ጊዜ ሲሆን ይህም  እርግዝናው የሚጀምርበት በመሆኑና ብዙውን ጊዜ ማቅለሽለሽ….ማስታወክ የሚከሰትበት ወቅት በመሆኑ በዚህ ላይ እስፖርት መስራት አስቸጋሪ ይሆናል፡፡  ከአስራ አራት እስከ ሃያ ስምንት ሳምንት ድረስ ባለው የእርግዝና ጊዜ ግን በእርግዝናው ምክንያት የተከሰቱት የተለያዩ ችግሮች የሚቀረፉበት እና የተረጋጋ ጊዜ ስለሚሆን እስፖርቱን መጀመር የሚቻልበት ወቅት ነው፡፡

  • እርጉዝዋ ፈሳሽ ካላት እስፖርት መስራት አይቻልም፡፡
  • ያረገዘችው ሴት  እርግዝናዋ የመጀመሪያ ካልሆነና ቀደም ባለው የእርግዝና ጊዜዋ ምጥ ያለጊዜው የሚያስቸግራት ከሆነ እስፖርት ስትሰራ ተመሳሳይ ችግር እንዳያጋጥማት እስፖርት ከመስራት መታቀብ አለባት፡፡
  • በእርግዝና ጊዜ የሚመጣ የደም ግፊት ሕመም ያለባቸው እርጉዞች እስፖርት መስራት አይችሉም፡፡
  • ማህጸናቸው ልጅ የመሸከም ችግር ያለባቸው ሴቶች በእርግዝና ወቅት እስፖርት እንዲሰሩ አይመከርም፡፡
  • በእርግዝና ክትትሉ ጊዜ ልጃቸው በጣም የጫጨ መሆኑ በአልትራሳውንድ ከተረጋገጠ እስፖርቱ የበለጠ ሊያጫጨው ስለሚችል ለእነዚህ ሴቶችም  እስፖርት አይመከርም፡፡
  • በእርግዝና ጊዜ የደም መፍሰስ ካለ ሁኔታው በሐኪም ሳይጣራ እና ሳይፈቀድ ወደ እስፖርት መሄድ አይገባም፡፡
  • እርግዝናው መንትያ ከሆነ በተለይም ከሶስት እስከ አምስት ልጅ የሚደርስ መንትያ ከሆነ እስፖርት መስራቱ ይከብዳል፡፡
  • እርጉዝ ሴቶች የስኩዋር ፣የታይሮይድ፣የደም ግፊት የመሳሰሉት ችግሮች የሚታዩባቸው ከሆነ እስፖርት መስራት አይመከሩም፡፡

ስለሆነም እርጉዞች በእነዚህ በተጠቀሱትና በሌሎችም ምክንያቶች ጠቅላላ ምርመራ አድርገው እስፖርትን በመስራቱም ረገድ ሐኪምን አማክረው ሲፈቀድላቸው ነው ወደ እንቅስቃሴው መግባት ያለባቸው፡፡ ከዚያ ውጭ ግን በእርግዝና ጊዜ እስፖርት መስራት በጣም ጠቃሚ ነው፡፡

*****************************************************************

አንዲት ሴት ሁለት ብልት እና ሁለት ማህጸን ሊኖራት ይችላል፡፡
                                                ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
ተፈጥሮ አንዳንድ ጊዜ ለየት ያለ ነገር ይስተዋልባታል፡፡ አንዳንድ ሰዎች ስድስተኛ ጣት ይዘው ይወለዳሉ፡፡ አንዳንዶች ደግሞ ጆሮአቸው ላይ ቅጥል ይኖራቸዋል፡፡ ሌላም አይነት ተፈጥሮአዊ ሁኔታዎች ሊያጋጥሙ ይችላሉ፡፡ በዚህ እትም የምናስነብባችሁ አንዲት ሴት ሁለት ብልት እና ሁለት ማህጸን ሊኖራት ይችላል የሚለውን ነው፡፡ ለዚህ መረጃ መነሻ የሆነን አለም አቀፉ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ፌደሬሽን (FIGO) ያወው ጥናታዊ ጽሁፍ ነው፡፡ በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ የሰጡን ዶክተር ሔርጴሳ ጋሮሳ ከጦር ሓይሎች ሆስፒታል ናቸው፡፡ ዶክተር ሔርጴሳ ጋሮሳ የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ስፔሻሊስት እንዲሁም የኢትዮጵያ የማህጽንና ጽንስ ሐኪሞች ማበር ESOG አባል ናቸው፡፡
                ----------------------------////---------------
ኢሶግ/ የሰው አፈጣጠር እንዴት ነው?
ዶክ/  ጠቅለል ባለ ሁኔታ የሰው ልጅ ሲፈጠር በመጀመሪያ የሴቷ እንቁላልና የወንዱ ዘር መገናኘት አለባቸው፡፡ እነዚህ የሚገናኙት ደግሞ በሴቷ ማህጸን ውስጥ ነው፡፡ በዚያ ከሚፈጠረው ግንኙነት በሁዋላ በየደረጃው ጽንሱ እያደገ ይሄድና በተለይም በመጀመሪያው ስምንት ሳምንት ውስጥ ወይንም የመጀመሪያው 12 ሳምንታት ለእያንዳንዱ የሰው ልጅ አካል መፈጠር ወሳኝ ጊዜ ይሆናል፡፡ በእነዚህ ጊዜያት እርጉዞች ያገኙትን መድሀኒት መውሰድ ወይንም የተለያዩ አልኮሆሎችን ወይንም ሱስ አስያዥ እጾችን እንዳይጠቀሙ ይመከራል፡፡ ምክንያቱም እነዚህ ነገሮች ለጽንሱ ተጻራሪ ስለሚሆኑና እያንዳንዱ የሰውነት አካል በትክክለኛው መንገድ መፈጠር ሲገባው ሊያዛባ ይችላል የሚል ስጋት ስላለ ነው፡፡ ስለዚህ እያንዳንዱ የሰው አካል የወንድም ይሁን የሴት የውስጥ አካላት የወደፊት ሁኔታቸው የሚወሰነው እርግዝናው በተጀመረ በመጀመሪያው ሶስት ወራት ውስጥ ነው፡፡ ይህ ወሳኝ ጊዜ በህክምናው ዘርፍም ጥንቃቄ የሚደረግበት ጊዜ ነው፡፡
ኢሶግ/ ሴቶች ሁለት ብልት እና ሁለት ማህጸን ሊኖራቸው ይችላል ?
ዶክ/  አንድ ሴት ሁለት ብልት እና ሁለት ማህጸን ሊኖራት ይችላል፡፡ ይህም የሚከሰተው በአፈጣጠር ከሚከሰት ችግር ተፈጥሮ በትክክለኛው መንገድ አካሄዱን ተከትሎ ወደ አንድ ብልት እና ወደ አንድ ማህጽን ሳይመጣ የቀረ እደሆን ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ ቤት በመጀመሪያ ፕላኑ ሲሰራ ወረቀት ላይ ተዘርግቶ በንጣፍ ይታያል እንጂ ቤቱ በቁመናው እንደሚታየው አይነት የሰውነት ቅርጽ አይኖረውም፡፡ የሰው ልጅም በመጀመሪያ  ሲፈጠር እንደዚሁ አንድ ንጣፍ ወይንም ዝርግ ነገር ሆኖ ነው፡፡ በጊዜ ሂደት ግን ያ ዝርግ ሆኖ የተፈጠረ አካል በመጀመሪያው ስምንት ሳምንት ወደ አንድ በመታጠፍ የግራና የቀኙ ጠርዝ ይገናኝና ይጣበቃል፡፡ ዝርግ ሆኖ የተፈጠረው የሰው ሰውነት በሚታጠፍበት ጊዜ በመሀከል ላይ ያለው ማለትም የቀኙና የግራው ጠርዝ የነበረው እንደ ግድግዳ ስለሚሆን ይህ ግድግዳ  በሂደት መፍረስ ወይም መሟሟት አለበት፡፡ የዚህ ግድግዳ መሟሟት እስከ አምስት ወር ባለው የእርግዝና ጊዜ የሚጠበቅ ነው፡፡ ተፈጥሮ በዚህ መልክ ሂደቷን ካከናወነች እና ያ ዝርግ ተፈጥሮ የግራና የቀኙን ጠርዝ በማገናኘት ከታጠፈ እንዲሁም በመሀከል ያለው ግድግዳ እስከ አምስተኛ ወር ድረስ ከፈረሰ በትክክለኛው መንገድ ሴቷ አንድ ብልት ወይንም አንድ ማህጽን ይኖራታል፡፡ይሄ ሂደት ከተዛባ ግን ሴት ልጅ በቀንና በግራ በኩል ሁለት ብልት በውስጥ አካሉዋ ደግሞ ሁለት ማህጽን ይኖራታል፡፡ እንደዚህ አይነት ችግር ያለባቸው ሴቶች ምናልባት ከአንድ ሺህ ሴቶች ውስጥ ሁለት ያህሉ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡  
ኢሶግ/ አንዲት ሴት ሁለት ብልት ሁለት ማህጸን አላት ሲባል የአካላቱ አቀማመጥ በምን ሁኔታ ነው?
ዶክ/  ሴቶች ሁለት ብልት እና ሁለት ማህጽን አላቸው ሲባል አቀማመጡ በእንዴት ያለ ሁኔታ ነው የሚለውን እራሳቸው ማለትም ይህ ተፈጥሮ የገጠማቸው ሴቶችም በግልጽ የሚያዩት ወይንም የሚያውቁት ነገር አይደለም፡፡ ምክንያቱም ከውጭ ስናየው የብልት ከንፈር የሚባለው አንድ ነው፡፡ ግን የብልት ከንፈሩ ትንሽ ከፈት ሲደረግ አንድ በመሆን ፈንታ በግራና በቀኝ ሁለት ብልት ሆነው ይገኛሉ፡፡ በውስጥ ደግሞ ሲመረመር በግራና በቀኝ ሁለት የማህጽን ግድግዳ ይገኛል፡፡
ኢሶግ/ ሴቷ ይህንን አይነት  ተፈጥሮ እንዳላት ልታውቅ የምትችልበት መንገድ ምንድነው?
ዶክ/  ሁለት ብልት እና ሁለት ማህጽን ያለቸው ሴቶች ይህ ተፈጥሮአዊ ችግር መኖሩን ሊያውቁ የሚችሉበት የተለያዩ ሁኔታዎች አሉ፡፡

    • በወር አበባ ወቅት ወይንም በመውለድ እድሜ ሲደርሱ የሚታይ ችግር አንዱ ነው፡፡ የወር አበባ በሚፈስበት ጊዜ ሁለቱም ብልቶች ክፍተት ሲኖራቸው እና የወር አበባውን በሚገባ የሚያፈሱ ከሆነ ችግር ላይገጥም ይችላል፡፡ ነገር ግን አንዱ መስመር ዝግ ከሆነ የወር አበባ የመፍሰስ ችግር ስለሚገጥመው እና ስለሚጠራቀም አንዳንዶቹ ላይ በብልት አከባቢ እና በሆድ አካባቢ የማበጥ ሁኔታ እና የህመም ስሜትም ሊኖር ይችላል፡፡
    • ሴቶቹ ከወንድ ጋር የግብረስጋ ግንኙነት በሚያደርጉበት ጊዜ ከሌላ ሰው በበለጠ ለየት ያለ ሕመም ሊኖራቸው ይችላል፡፡ምክንያቱም ሁለት ብልት ያላቸው ከሆኑ በግብረስጋ ግንኙነት ወቅት የመለጠጥ እና የወንዱን ብልት ለመቀበል ዝግጁ ያለመሆን ችግር ስለሚገጥመው ነው፡፡   
    • እርግዝና በሚከሰትበት ጊዜ እርግዝናው በብዙዎቹ ሁለት ማህጸን ባላቸው ሴቶች  እስከመጨረሻው ላይቀጥል ይችላል፡፡ በመጀመሪያው ሶስት ወይንም አምስት ወር ላይ በተደጋጋሚ ውርጃ ሊያጋጥም ይችላል፡፡ ጽንሱ እንኩዋን ቢገፋ በሰባት ወር እና ከዚያ በላይም ቢሆን የውጭውን አየር መቋቋም በማይችልበት እድሜ ሊወለድ ይችላል፡፡
    • ሌላው ችግር ደግሞ የልጁ አቀማመጥ ነው፡፡ ጤናኛ የሆነ ማህጽን ያላቸው ሴቶች ሲያረግዙ ዘጠና አምስት ከመቶ የጽንሱ አቀማመጥ ትክክል ሲሆን ሁለት ማህጽን ያላቸው ሴቶች ላይ ግን በወሊድ ወቅት ሕጻኑ በእጅ፣ በቂጡ ወይንም በእግሩ የመምጣት እንዲሁም እንግዴ ልጁ ከማህጽን ጋር የመጣበቅና አልወጣም የማለት እንዲሁም ከሌሎቹ የበለጠ የመድማት ችግር ሊያጋጥም ይችላል፡፡

ኢሶግ/  ሁለት ማህጽን ካለ የሚረገዘው በአንዱ ነው ወይንስ በሁለቱም ማህጸን ነው?
ዶክ/  እርግዝናው ብዙ ጊዜ በአንዱ ማህጽን ነው፡፡ ምክንያቱም ሴቶች በወር አንድ ጊዜ ነው ፍሬአቸው የሚለቀቀው፡፡ ያ ፍሬ ሲለቀቅ እርግዝናው የሚከሰተው በአርባ ስምንት ሰአት ወይንም በአንድ ወር ውስጥ ለሁለት ቀን ያህል ብቻ ነው የማርገዝ እድሉ የሚኖረው፡፡ በዚህን ጊዜ አንድ ማህጽን ላይ የወንዱንና የሴቷን የዘር ፍሬ የሚያገናኘው (Fallopian tube)ፋሎፒያን ቲዩብ በግራና በቀኝ አንዳንድ ብቻ ነው፡፡ እነዚህ ሴቶች ሁለት ማህጽን ቢኖራቸውም ይህ የዘር ማገናኛው መስመር (Fallopian tube)አሁንም አንዳንድ ብቻ ነው፡፡  ስለዚህ እርግዝናው ሊከሰት የሚችለው አንደኛው ማህጽን ውስጥ ነው እንጂ ሁለቱም ማህጸን ውስጥ አይደለም፡፡
ኢሶግ/ ሁለት ብልት መኖር ከወንድ ጋር በሚኖረው የወሲብ ግንኙነት ወቅት የሚያስከትለው ችግር አለ?
ዶክ/  ተፈጥሮ ዝርግነቱን በሚለውጥበት ጊዜ ግራና ቀኙ ጠርዝ ሲገናኝ መፍረስ ወይንም መሟሟት የነበረበት ግድግዳ ባለመወገዱ የሚያስከትለው ችግር መኖሩ እሙን ነው፡፡ ሴት ልጅ ከወንድ ጋር የግብረስጋ ግንኙነት በምታደርግበት ጊዜ የሴቷ ብልት የወንዱን ብልት ማካተት አለበት፡፡ በግንኙነት ወቅት የሴቷ ብልት የመርዘም ወይንም የመለጠጥ ባህሪይ አለው፡፡ ግን ያ መፍረስ ወይንም መሟሟት የነበረበት ግድግዳ ሳይወገድ በመቅረቱ በግንኙነት ወቅት በቀላሉ ስለማይለጠጥ ሴቶቹ በሕመም ሊሰቃዩ ይችላሉ፡፡ ብዙውን ጊዜ ሕመሙን ሊታገሱት ስለማይችሉ የወንድ ጉዋደኛቸውንምሆነ የራሳቸውን ስሜት እስከሚያረኩ ድረስ በግንኙነቱ ሊቀጥሉ ስለማይችሉ እንዲቋረጥ ያደርጋሉ፡፡
ኢሶግ/ ሁለት ብልት እና ሁለት ማሕጸን በመኖሩ ምክንያት የወሊድ ሁኔታ ምን ይመስላል?
ዶክ/  ጥናቶች እንደሚያመለክቱት ይህ ችግር ያለባቸው ሴቶች የመውለድ እድላቸው የተመናመነ ነው፡፡ ሰማንያ ስምንት ከመቶ የሚሆነው እርግዝና በውርጃ ይስተጉዋጎላል፡፡ ስድስት ከመቶ የሚሆኑት እርግዝናዎች ጊዜያቸው ሳይደርስ የሚወለዱ ናቸው፡፡ ሶስት ከመቶ የሚሆኑት እርግዝናዎች ብቻ ናቸው በጊዜያቸው የሚወለዱት፡፡ ነገር ግን  እነዚህ ጊዜያቸው እስኪደርስ ድረስ በእርግዝናው ላይ የሚቆዩትም ቢሆኑ የአቀማመጥ ችግር፣ከማህጸን ጋር የመጣበቅ እንዲሁም የመድማትን ሁኔታ ባብዛኛው የሚያስከትሉ ናቸው ፡፡ ሁለት ማህጸን ያላቸው ሴቶች ተደጋጋሚ ውርጃና የመሐንነት እድላቸው ከሌሎች ሴቶች በጣም ከፍ ያለ ነው ፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሴቶች የመውለድ እድላቸው በጣም የተመናመነ በመሆኑ አስቀድሞውኑም ሕክምና ማድረግ ያስፈልጋቸዋል ፡፡ አንዲት ሴት ልጅ እድሜዋ ወደ አስራ ሰባት አመት ገደማ ሲደርስ ጀምሮ ጤነኛ የሆነ የማህጽንና የብልት አቀማመጥ እንዳላትና እንደሌላት ምርመራ የህክምና ምርመራ በማድረግ ማረጋገጥ ይገባታል፡፡
ኢሶግ/ ይህ ተፈጥሮአዊ ሁኔታ ሕክምና አለው?


ዶክ/  በአሁኑ ወቅት በጣም በተሸሻለ ሁኔታ ሕክምና አለው፡፡ በተፈጥሮ ሂደት አንድ መሆን ሲገባው እንዳይሆን ያደረገውን ግድግዳ በቀዶ ሕክምና በማስወገድ ብልትንም ሆነ ማህጸንንም አንድ ላይ በማዋሀድ ሁለት ከመሆን ይልቅ አንድ እንዲሆን ማድረግ ይቻላል፡፡ ሁለት ብልት እና ሁለት ማህጽን ያላቸው ሴቶች ሕክምና በማድረጋቸው ምክንያት የመውለድ እድላቸውም ይሻሻላል፡፡ በሌሎች አገሮች በጥናት እንደተደረሰበት ሕክምና ከተደረገላቸው ሴቶች መካከል በቀዶ ሕክምና ከተረዱ በሁዋላ መጀመሪያ ከነበረባቸው የተለያየ ችግር ተላቀዋል፡፡ ሰማንያ ስምንት ከመቶ  ውርጃ፣ዘጠኝ ከመቶ ልጅ ሳይደርስ መውለድ ፣ሶስት ከመቶ ልጅ ደርሶ መውለድ የነበረው ሁኔታ …ከታከሙ በሁዋላ ተደጋጋሚ ውርጃ ከሰማንያ ስምንት ከመቶ ወደ አስራ አራት ከመቶ ዝቅ ብሎአል፡፡ ጊዜው ሳይደርስ መውለድ ደግሞ ከዘጠኝ ከመቶ ወደ ስድስት ከመቶ ወርዶአል፡፡ የመወለጂያ ጊዜያቸው ደርሶ የተወለዱ ደግሞ ከሶስት ከመቶ ወደ ሰማንያ ከመቶ ከፍ ብሎአል፡፡  በትዳር ላይ የሚኖረው የግንኙነት ችግር፣ እንዲሁም በወር አበባ ጊዜ የሚኖረው ስቃይም እንደተወገደ መስክረዋል፡፡  ስለዚህ ዋናው ነገር ወደሕክምናው ጣቢያ በመሄድ ሕክምናውን ማድረግ ነው፡፡ ሕክምና ካደረጉ እነዚህን ሴቶች ወደ ጤነኛነት ማምጣት  ይቻላል፡፡    

ትዳር ፍቅርን ብቻ ሳይሆን ግልጽነትንም ይሻል …
                          
                                           ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
(…ይድረስ ለኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር….) መልእክቶች በደብዳቤ ከተለያዩ አቅጣጫዎች ይደርሱናል፡፡ በዚህ እትም ለንባብ ያልነውን የህይወት ገጠመኝ የላከችልን ባለታሪክ ስሙዋ እንዲገለጽ ስላልፈለገች ስም ሰጥተናታል፡፡አንቺን አሉ ትባላለች፡፡ ታሪኩ እንደሚከተለው ቀርቦአል፡፡
    
     እኔና ባለቤቴ የተገናኘነው በስራ አጋጣሚ ነው፡፡ እኔ በወቅቱ ድንግልናዬ ያልተነካ ነበርኩኝና ከባለቤቴ ጋር ጋብቻ እስክንፈጽም ድረስ ምንም የግብረስጋ ግንኙነት አልፈጸንም፡፡ ግን በጣም ተዋደድን፡፡ ወደ አንድ አመት ገደማ በፍቅር አብረን እንደተሳሰርን  ተጉዋዝን፡፡ በዚህ  ላይ  በመስሪያ ቤታችን ማንም  እንዲያውቅብን  ስላልፈለግን  ግንኙነታችን  በጣም  ምስጢራዊ  ነበር፡፡ የሁዋላ ሁዋላ ግን ፍቅራችንን ማሸነፍ  ስላቃተን  የጋብቻ ሂደቱ እንዲሳካ  መንገዶችን  ማመቻቸት ጀመርን፡፡ ባለቤቴ  ወደ እኔ ቤተሰቦች ሽማግሌ እንዲላክ  ለቤተሰቦቹ ሲናገር እናትየው ልክ እንደቀድሞው ባህላችን  ለመሆኑ የማን ዘር ናት ማለት ጀመሩ፡፡ በምን መለኪያ እንደሆነ ባላውቅም የእናትየውን መስፈርት  አልፌ ሽማግሌዎች ወደ እኔ  ቤተሰቦች ቤት ሲመጡ ግን የማን ዘር ነው የሚል ጥያቄ አልቀረበላቸውም፡፡ የእ ቤተሰቦች መልስ እነሱ ከተዋደዱ ምን ችግር አለ የሚል ነበር፡፡
     የእናትየው አንዱ የጋብቻ መስፈርት በቁርባን ከተገባችሁ ነው ጋብቻ የምትፈጽሙት የሚል ነበር፡፡ ለነገሩ የእኔም ቤተሰቦች ያው የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ስለሆኑ ሃሳቡን ለመቀበል አላቅማሙም …ይሁን ምን ቸገርን…ዋናው ነገር ተጋቢዎቹ በጉዳዩ ፈቃደኛ መሆን አለመሆናቸው መታየት አለበት የሚል ነበር መልሳቸው፡፡ እኔ ግን ጉዳዩ አስፈራኝ፡፡ እናም ባለቤቴን
«…እስቲ መጀመሪያ እኔና አንተ እንነጋገር…ለመሆኑ በእኛ ሕይወት ቤተሰቦቻችን መወሰን ይችላሉ እንዴ …ስለ…አይ ምን ችግር አለ …ዋናው ነገር እኮ መዋደዳችን ነው፡፡ እኔና አንቺ ከተዋደድን እንኩዋንስ በቁርባን በምንስ ብንጋባ ምን ችግር አለው…የሚል መልስ ሰጠኝ፡፡ እኔ ደግሞ …
በጋብቻ ወቅት ብዙ አስቀድመን ልናስባቸው የሚገቡን ነገሮች አሉ፡፡ ከፍቅር ባሻገር በመተሳሰብ አብሮ የመኖር ነገር ስላለ በዚህ በአንድ አመት ቆይታችን ይህንን ገምግመን ጨርሰናል ወይ… ከቤተሰቦቻችን ….ከምንመሰርተው ቤተሰብ…ከጉዋደኛ…ከምንሰራው ስራ ከመሳሰሉት ሁሉ የሚከሰቱ ነገሮችን በተገቢው መንገድ ለመወጣት ችሎታው አለን ወይ… በቁርባን መጋባት እኮ እምነትነተ…ጥንካሬን…ጥንቃቄን…ብቃትን…እርጋታን…የመወሰን ችሎታን…ከምንም በላይ ደግሞ የቤተሰብ ጣልቃ ገብነት የሌለበትን ኑሮ …የመሳሰሉትን ሁሉ ይፈልጋል፡፡ ስለዚህ በእነዚህ ነገሮች እርግጠኞች ከሆንን በእኔ በኩል ፈቃደኛ ነኝ አልኩት፡፡ እሱም …ምንም ችግር የለም …ነገሮችን እንደየአመጣጣቸው ለመመለስና ተግባብተን ለመኖር ጥረት እናደርጋለን፡፡ ምክንያቱም ይህ የእናቴ ምርጫ ስለሆነ እሱዋን ማስቀየም ደግሞ አልፈልግም አለኝ፡፡ …እኝህ እናትህ ወደፊትስ የሚቀየሙበት ነገር ቢፈጠር እንዴት እናስተናግደዋለን …የሚል ጥያቄ አቀረብኩ፡፡ እሱም ግድየለም ወደፊት እናየዋለን ..ዋናው የእኔና የአንቺ መፋቀር ነው፡፡ እሱን ብቻ እርግጠኛ ሁኚ አለኝ፡፡»
     ባለቤቴን ብወደውም እናትየውን እጅግ ነበር የፈራሁዋቸው፡፡ ከሌሎቹን ቤተሰቦቹ ጋር ለመገናኘት እንኩዋ ምንም እድል የሚሰጡ አልነበሩም እናትየው፡፡ የሁሉም ነገር አዛዥ እሳቸው ናቸው፡፡ ያው በተፈለገው ፕሮግራም መሰረት እኔና የምወደው ባለቤቴ ጋብቻውን ፈጸምን፡፡ በዚህ ዘመን የማትገኝ ጨዋ ልጅ በመገኘቱዋም እናትየውም ያልታሰበ ደስታ እደገጠማቸው ገለጹልኝ፡፡
     ኑሮዋችን ቀጠለ፡፡ በተጋባን ወደ ስድስት ወር ገደማ ሲሆነን እናትየው ጥያቄ ማቅረብ ጀመሩ፡፡
ምነው…ሆዱዋ ከፍ አይልም እንዴ…ማለት ጀመሩ፡፡ ልጅ እንዲወለድ እንደሚፈልጉ ከተለያዩ አቅጣጫዎች እንዲነገረኝም አደረጉ፡፡ የወሊድ መከላከያ የምወስድ ከሆነም አቋርጬ ልጅ መውለድ እንዳለብኝ ማሳሰቢያው ቀጠለ፡፡ እኔም ለባለቤቴ …ልጅ መውለድን እኔም እፈልገዋለሁ፡፡ ነገር ግን እስከአሁን ድረስ ምንም የተሳካ ነገር የለም፡፡ ይህ ደግሞ የእግዚአብሔር ፈቃድ እንጂ የሰው ስራ አይደለም፡፡ እናትህ ለምን ይህንን ጉዳይ ለእኛ አይተውትም …ስለው…በቃ እሱዋን አታዳምጫት …ተያት…ይሔ የእኛ ኑሮ ነው ይለኛል፡፡ ባለቤቴ በጣም ደግና ጥሩ ሰው ስለሆነ ጥሩ መልስ ነው የሚሰጠኝ፡፡ እንዲህ እንዲህ እያልን ወደ ሶስት አመት ሲሞላን …በቃ እናትየው ለአይናቸው ጠሉኝ፡፡… ይህችን በቅሎ ከየትም ጎትቶ አምጥቶ…ይሉ ጀመር፡፡ ያ የፈራሁት ነገር መጣ፡፡ በእርግጥ ከባለቤቴ ምንም መጥፎ ፊት ስላላይሁ ማድረግ ያለብኝ የሚባለውን ነገር መቻል ብቻ እና ለእግዚአብሔር መጸለይ ነው ብዬ ወሰንኩ፡፡
     በዚህ እትም በአንድ ወቅትInfertility…በአለማችን የብዙዎች ችግር…ያለመውለድ ችግርን የሚመለከት ጽሁፍ ወጥቶ ነበር፡፡  በመጠኑ ለማስታወስ እንዲህ ነበር የሚለው፡፡             «…ልጅ መውለድ አለመቻል ምክንያቱ ብዙ ሲሆን  ከምክንያቶቹ ሶስት እጅ የሚሆነው መንስኤው ያልታወቀ ወይንም የታወቀ ተብሎ ሊለይ ይችላል፡፡ ፍሬ አልባ ወይንም መካን የመሆን እድሉ የማን ነው ? ተብሎ ቢጠየቅ ምናልባትም ለሶስት አጁ ዘር አልባነት ምክንያት ወንዶች ወይንም ሴቶቹም ሊሆኑ እንደሚችሉ ይታመናል፡፡Infertility…ልጅ የአለመውለድን ወይንም መካንነትን ችግር ለመከላከል በተቻለ መጠን ሐኪሞችን ማማከር ጠቃሚ መሆኑን ነው ማይክሮሶፍት ኢንካርታ /2009 /የሚመክረው፡፡ይላል ከአሁን ቀደም የወጣው ጽሁፍ፡፡
ይህንን ጽሁፍ እንደአነበብኩኝ ወደ ሐኪሞች ነበር ለምክር የሄድኩት፡፡ ከዚያም ሁለታችንም መመርመር እንዳለብን ተነገረኝ፡፡ ሐኪሞች የነገሩኝን ለምወደው ባለቤቴ አስረዳሁት፡፡ እሱም …አንቺ ምን አስጨነቀሽ…አንዴ እንደሆነ በቁርባን ጋብቻችንን ፈጽመናል፡፡ ወለድሽ አልወለድሽ በእኛ ሕይወት ላይ የሚያመጣው ምንም ለውጥ የለም… አለኝ፡፡ እኔም …አአይ ...የለም … ምርመራ ማድረግማ አለብን ፡፡ ምክንያቱም እናትህ በየደረሱበት እየሰደቡኝ ነው፡፡ እንዲያውም እኔ የምፈልገው …አንተን ስለምወድህ …ብችል አንድ ልጅ እንኩዋን ብወልድ ብዬ እንጂ…ለኑሮ ግን እናትህ እጅግ አስቸጋሪ ሰው በመሆናቸው የምችላቸው አይመስለኝም አልኩት፡፡ እሱም …አይ…ከእኔ ጋር ለመኖር ከፈለግሽማ እኔ የምልሽን ነገር መስማት አለብሽ …አለኝ፡፡
እኔም …ጥሩ…ለማንኛውም እንሂድና እንመርመር አልኩት፡፡ …አንቺ ሂጂና ተመርመሪና ያንቺን ውጤት ካየሁ በሁዋላ እመረመራለሁ አለኝና …እሱ ወደስራው ሄደ፡፡ እኔም …ግድየለም …እስቲ መውለድ መቻል አለመቻሌን ልየው ብየ ምርመራ አደረግሁኝ፡፡ ሐኪሙ ምንም ችግር እንደሌለብኝ ነገረኝ፡፡ እንደገናም ወደሌላ ሐኪም ሄድኩኝ ፡፡ አሁንም ተመሳሳይ መልስ አገኘሁኝ፡፡
ባለቤቴ ከስራው ሲመለስ የተሰጠኝን የሐኪም ወረቀት አሳየሁት፡፡ ብዙም አልተደሰተበትም፡፡ በል እንግዲህ አንተ ደግሞ ሂድና ተመርመር አልኩት፡፡ እሺም እምቢም ሳይለኝ ነገሩን ቀለል አድርጎ ተወው፡፡ እኔ ደግሞ የእናትየው ወሬ በየዘመድ አዝማዱ…በየመንደሩ ስላስቸገረኝ ተመልሼ ወደሐኪም ቤት ሄጄ ምን ማድረግ አለብኝ የሚል ምክር ጠየቅሁኝ፡፡ ከዚያም ሐኪሙ የባለቤቴን ስም ጠይቆኝ ስነግረው ከፊቱ ላይ ድንግጥ የሚል ነገር አየሁበት፡፡ ምነው …ስለው…አይ ምንም …ምን አየሽ …አለኝ፡፡ አይ ፊትህ ላይ ደስ የሚል ምልክት ስላላየሁብህ ነው ብየ አልኩት፡፡ አይ ዝም ብዬ ነው አለኝና እሱ ጠርቶ እንደሚያነጋግረው ቃል ገብቶልኝ ተለያየን፡፡
ከሐኪሙ ምንም መልስ ባላገኝም በሌላ መንገድ ሳጣራ ግን ባለቤቴ ለካስ ሌላ ታሪክ አለው፡፡ ከአሁን ቀደምም አንዲት ሴት አግብቶ…እንደዚሁ የመውለድ ችግር ገጥሞአቸው…በሕክምና አብረው ምርመራ ሲያደርጉ እሱ የመውለድ ችግር እንዳለበት ተነግሮታል፡፡ ከዚያም ይህንን ምስጢሩን ደብቆ ያችን ልጅ በሌላ ምክንያት አሳብቦ ፍቺ ይፈጽማሉ፡፡ ከዚያም በሁዋላ እንደዚሁ በጉዋደኝነት ከአንዱዋ ጋር በመቆየት መውለድ እንደማይችል አረጋግጦአል፡፡ የሚገርመው ነገር በመጀመሪያ አግብቶአት የነበረችውን ልጅ …የባለቤቴ እናት…እኔ በዘሬ መሐንነት የለብኝም፡፡ …ደግሞ የሴት እንጂ የወንድ መሐን የለውም እያሉ ሊደበድቡዋት እስኪደርሱ ሲያስቸግሩአት እንደነበርና እሱዋ ግን ከእሱ ጋር በተፋታች በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ ከሌላ ሰው በተከታታይ ሁለት ልጆች እንደወለደች ሰማሁ፡፡


     ባለቤቴን በዚህ ጉዳይ ላይ ላነጋግረው ብሞክር መልስ የማይሰጥም ሆነ፡፡ ከዚያም የንሰሐ አባታችንን ጠርቼ የሆነውን ሁሉ አጫወትኩአቸው፡፡ እሱ ልጅ መውለድ እንደማይችል እያወቀ እኔን …ያውም በቅዱስ ቁርባን ማግባቱ…ምን ያህል ጥፋት እንደሆነ ብረዳም …ይሁን ችግሩን ልቀበል ብዬ እንኩዋን እንዳልወስን እናትየው ሊያኖሩኝ አልቻሉም፡፡ ስለዚህ ምን ላድርግ ብዬ ሳማክራቸው…የንሰሐ አባቴ ባለቤቴን ለብቻው አነጋግረው እርሱ እራሱ እኔም ባለሁበት ለእናቱ እንዲነግራቸው ተደረገ፡፡ እናትየው ይህንን ሲሰሙ በፍጹም ለማመን ተቸግረው ነበር፡፡ ነገር ግን ባለቤቴ «…በቃ በዚህች ልጅ ላይ ለፈጸምኩት በደል በሕይወት ዘመኔ በሙሉ ይቅርታን ከፈጣሪዬም ከእሱዋም  እጠይቃለሁ፡፡ባለቤቴን በተፈለገው መንገድ ለመካስ ዝግጁ ነኝ፡፡ ከምንም በላይ ግን ፍቅሬን አላጉዋድልም፡፡ በተረፈ ግን ከዚህ ጊዜ ጀምሮ በትዳር ሕይወቴ በፍጹም እንዳትገቢ» ብሎ ለእናቱ በቄሱ ፊት ስለተናገረ አሁን በሰላም እንኖራለን፡፡ ባለቤቴ ጥሩ ሰው በመሆኑ ዘር የማጣታችንን ነገር የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው በማለት ተቀብየዋለሁ፡፡ ነገር ግን ያለበትን የመውለድ ችግር ደብቆኝ ለፍቺ እንኩዋን በማይመች መልኩ ጋብቻው እንዲፈጸም ማድረጉ እጅግ ነው ያሳዘነኝ፡፡ ማንኛውም ሰው ለትዳሩ ግልጽ መሆንን መማር አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ትዳር ፍቅርን ብቻ ሳይሆን ግልጽነትንም ይሻል፡፡ እኔ ይህንን ጽሁፍ ስልክላችሁ ባለቤቴ እንዲያውቅ አድርጌአለሁ፡፡ ግን ጥፋተኛ መሆኑን አምኖና ሌሎችም እንዲማሩበት በሚል ፈቅዶልኛል፡፡ አሁን በጉዲፈቻ ልጅ ለማሳደግ ይኼው ከሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ጋር በመነጋገር ላይ እንገኛለን፡፡

ለድብድብ የሚጋበዙ አሉ…የተደበደበ ሐኪምም አለ፡፡
                                    ፀሐይ ተፈረደኝ ከአሶግ
በኢትዮያ ከሚታወቁት የመንግስት ሆስፒታሎች ጋንዲ ሆስፒታል አንዱ ነው፡፡ ማህተማ ጋንዲ እንደውጭው አቆጣጠር ከ (1869-1948) የኖሩ ሲሆን ለሀገራቸው ነጻነት በሰላማዊ መንገድ ትግል ያደረጉ ሰው ናቸው፡፡ ይህ ሆስፒታል እንዴት ስያሜውን አገኘ ? መቼ ተቋቋመ የሚለውንና በሆስፒታሉ እንቅስቃሴ ዙሪያ ከሜዲካል ዳይሬክተሩ ጋር ተነጋግረናል፡፡ የጋንዲ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር ዶክተር ደረጀ አለማየሁ የማህጸንና ጽንስ እስፔሻሊስትና የኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር አባል ናቸው፡፡

ኢሶግ/ ጋንዲ ሆስፒታል መቼ ተመሰረተ?
ዶክ/  ጋንዲ ሆስፒታል የተመሰረተው ከዛሬ ሀምሳ አመት በፊት በኢንዲያን ኮሚኒቲ ማህበረሰብ አነሳሽነት ነው፡፡ ሆስፒታሉን ለመመስረት ኢንዲያን ኮሚኒቲ በአዋጣው ገንዘብ ላይ የኢትዮጵያ መንግስትም ተጨማሪ ገንዘብ ተመድቦ እንደኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1950 ዓ/ም አካባቢ ተመሰረተ፡፡ ሆስፒታሉ ስራ ከጀመረ ወደ ሀምሳ አመት ገደማ ሆኖታል ፡፡ የኢንዲያን ኮሚኒቲ ተነሳሽነቱን አሳይተው ሆስፒታሉ ስለተመሰረተ ስያሜውም በማህተመ ጋንዲ ስም እንዲሆን ተወስኖ ጋንዲ ሆስፒታል ሊባል ችሎአል፡፡
ኢሶግ/ ጋንዲ ሆስፒታል ዋናው ስራው ምንድነው?
ዶክ/  ጋንዲ ሆስፒታል ዋናው ስራው የማህጽንና ጽንስ ሕክምና መስጫ ሆስፒታል ነው፡፡ የእርግዝና ክትትል፣የማዋለድ አገልግሎት፣ የማህጽንና ጽንስ ሕክምና በመደበኛና በድንገተኛ የ24 ሰአት አገልግሎት ይሰጣል፡፡
ኢሶግ/ ጋንዲ ሆስፒታል ከማሕጸንና ጽንስ ሕክምና ሌላ የሚሰጠው አገልግሎት ምንድነው?
ዶክ/  ቀደም ሲል በነበረው አሰራር በጋንዲ ሆስፒታል የሚወለዱ ሕጻናት የሙቀት አገልግሎት የሚያስፈልጋቸው ከሆነ ወደጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ነበር የሚላኩት፡፡ አሁን በቅርቡ ከአንድ ወር አካባቢ ጀምሮ ግን በሆስፒታላችን አገልግሎቱን መስጠት ስለተጀመረ አሁን ሆስፒታሉ ወደ እናቶችና ሕጻናት ሆስፒታልነት እያደገ ነው ያለው፡፡
ኢሶግ/ ከ--አርኤች(ሾተላይ) ጋር በተያያዘ ሕጻናቱ ወደጥቁር አንበሳ የሚላኩበት ሁኔታ ነበር፡፡አሁንስ?
ዶክ/  የደም አይነት ኤ፣ቢ፣ ኤቢእና  ኦ ሲሆን ከዚህ በተጨማሪ አር ኤች ፋክተሩ ፖዘቲቭና ኔጌቲቭ በሚል ይለያል፡፡እናትየው አር ኤች ኔጌቲቭ ሆና የተረገዘው ልጅ አር ኤች ፖዘቲቭ ከሆነ አር ኤች ኔጌቲቭ እናት ናት ተብሎ በልጁ ላይ ችግር እንዳይደርስ ለሕክምና ወደ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ይላክ ነበር፡፡ አሁን ግን አር ኤች የሚለው የጤና ጉዳይ አስቀድሞውኑም የታወቀ በመሆኑ እናትየው በምትወልድበት ጊዜ ለሚቀጥለው ወሊድ ወቅት የሚያገለግል መድሀኒት ስለምትወስድ ችግሩ በጣም ተቃሎአል፡፡ አልፎ አልፎ ቢከሰትም እንኩዋን በጋንዲ ሆስፒታሉ ሕክምናው የሚሰጥበት ሁኔታ ተመቻችቶአል፡፡
ኢሶግ/ የጋንዲ ሆስፒታል ከኤችአይቪ ኤይድስ ጋር በተያያዘ የሚሰጠው አገልግሎት ምን ይመስላል?
ዶክ/  ሆስፒታሉ የእናቶች ሆስፒታል እንደመሆኑና የተለያያ የስነተዋልዶ ጤና አገልግሎት እንደመሰጠቱ  በዚሁ ዙሪያ በከተማችን በሞዴል ሴንተርነት የሚያስቆጥረውን የኤችአይቪ አገልግሎት ይሰጣል ፡፡  ጸረ ኤች አይቪ መድሀኒት መስጠት እና የማማከር አገልግሎት እንዲሁም ኤችአይቪ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ የሚያደርግ አገልግሎት ሆስፒታሉ ይሰጣል ፡፡ ማንኛውም ሰው የምርመራና የምክር አገልግሎት ቅዳሜና እሁድን ጨምሮ በነጻ ማግኘት ይችላል ፡፡ ለእርግዝና ክትትልም ሆነ ለመውለድ የሚመጡ እናቶች ሁሉ ኤችአይቪ ምርመራ ይደረግላቸዋል ፡፡
ኢሶግ/ የጋንዲ ሆስፒታል ከሌሎች የጤና ተቋማት ታካሚዎችን በሪፈራል ይቀበላል?
ዶክ/  ሆስፒታሉ ሪፈራል ሆስፒታል ነው፡፡ በአደረጃጀቱም በአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ስር ያለ በመሆኑም በከተማዋ የሚገኙ እና በክልል መስተዳደር ጤና ቢሮ የተመደቡ አስር ጤና ጣቢያዎች ታካሚዎችን ለከፍተኛ ሕክምና ወደ ጋንዲ ሆስፒታል ይልካሉ፡፡  በተጨማሪም በአዲስ አበባ በልደታ፣ቂርቆስ፣ቦሌ፣አቃቂ ቃሊቲ፣ ነፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማዎች የሚገኙ የግል የጤና ተቋማትም ከእነሱ አቅም በላይ የሆነ የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ሲያጋጥማቸው ወደጋንዲ ሆስፒታል ታካሚዎችን ይላካሉ፡፡
ኢሶግ/ ወደሆስፒታሉ የሚመጡት ወላዶች በቀን ምን ያህል ናቸው?
ዶክ/  በቀን ከሃያ አምስት እስከ ሰላሳ ወላዶችን ሆስፒታሉ ያስተናግዳል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ከ18 እስከ ሀያ ሁለት የሚሆኑት በተፈጥሮ ሁኔታ በማህጸን የመውለድ አገልግሎት ሲያገኙ ከአምስት እስከ ስምንት የሚሆኑ እናቶች ግን በየቀኑ በኦፕራሲዮን ይገላገላሉ፡፡ ይህም በወር የመውለድ አገልግሎት የሚያገኙትን እናቶች ቁጥር እስከ ሰባት መቶ ያደርሰዋል፡፡ በሀገራችን ይህንን ያህል የማዋለድ አገልግሎት የሚሰጥ የህክምና ተቋም ስለሌለ ሆስፒታሉን ብቸኛ የማዋለድ አገልግሎት መስጫ ሊያሰኘው ይችላል፡፡
ኢሶግ/ በውርጃ ሁኔታ የሚጎዱ ሴቶች አሁን ያለበት ሁኔታ ምን ይመስላል?
ዶክ/  በጋንዲ ሆስፒታል ድንገተኛ ክፍሎች በየቀኑ ከሚመጡት ታካሚዎች መካከል ከአምስት እስከ ሰባት የሚሆኑ ሴቶች ውርጃ ያካሄዱ ናቸው ፡፡ በእርግጥ የህገ ወጥ ውርጃ ቀደም ካለው ሁኔታ ጋር ስናያይዘው አሁን ቀንሶአል፡፡ ከሰባትና ስምንት አመት በፊት ማህጸናቸው በጣም ተጎድቶ እስከ አንጀታቸው ድረስ በመመረዝ ከፍተኛ ኦፕራሲዮን ተደርጎላቸውም እንኩዋን የሚሞቱ እንደነበሩ ይታወሳል፡፡ አሁን አሁን ግን በተወሰነ መልኩም ቢሆን ውርጃ ለማካሄድ የሚያስችል  በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የወጣ በመሆኑ እና በታወቀ መንገድ የውርጃው አገልግሎት ስለሚሰጥ ጉዳቱ የሚታየው አልፎ አልፎ ነው፡፡
ኢሶግ/ በሆስፒታሉ አገልግሎት ላይ የሚሰማ እሮሮ አለ፡፡ ልትወልድ የመጣችን ሴት አልጋ የለንም የማለት ወይንም በፍጥነት ያለመቀበል ችግር አለ የሚል ነገር ይሰማል ይህ እንዴት ነው ?
ዶክ/  ሆስፒታሉ ለህብረተሰቡ እጅግ አስፈላጊ የሆነ አገልግሎት ይሰጣል ፡፡ በየቀኑ በሃያ አራት ሰአት ውስጥ ከሀምሳ እስከ ስድሳ እርጉዝ እናቶች ወይንም ምጥ የያዛቸው እናቶች ወይንም በአንድ ምሽት እስከ ሀያ እናቶች ምጥ ይዞአቸው ሊመጡ ይችላሉ፡፡ ሆስፒታሉ ባለው አቅም በሙሉ ሓይል ነው አገልግሎት የሚሰጠው፡፡ ከዛ በላይ የሚመጡት እንግዲህ ከሆስፒታሉ የማስተናገድ አቅም በላይ ስለሚሆኑ ወደ ሌሎች ሆስፒታሎች እንዲተላለፉ ይደረጋል፡፡ ስለዚህ ወደሌላ ሆስፒታል ሪፈር የተደረጉ እናቶች ቢያማርሩ በእርግጥ በእነሱ ስሜት ትክክል ሊሆን ይችላል ፡፡ ምክንያቱም ያሉበት ሁኔታ ምጥ ነውና፡፡ ነገር ግን ወደሌላ ሐኪም ቤት የሚላኩት የምጡን ደረጃ በመለየት ስለሆነ ማህጸናቸው ሙሉ ለሙሉ የተከፈተ ሴቶች ሪፈር አይደረጉም፡፡ ነገር ግን የምጥ ባህሪይ አስቸጋሪ ነው፡፡ በምርመራው ወቅት የማህጸኑ መከፈት አምስት ወይንም ስድስት ሴንቲሜትር ሆኖ ለመውለድ ወደ ሌላ ሆስፒታል ሊሄዱ ይችላሉ ተብሎ ከተገመተ በሁዋላ በአንድ ጊዜ በሚመጣ ቁርጠት ግፊቱ ተፋጥኖ በድንገት በመንገድ ላይ ልትወልድ ትችላለች፡፡ ይሄ ግን ሐኪሙ ተሳስቶ ሳይሆን የምጥ ባህሪ ስለሆነ ነው፡፡ነገር ግን ማህጸናቸው ሙሉ በሙሉ ተከፍቶ የሚመጡት ሴቶች እስትሬቸር ላይም ቢሆን ይወልዳሉ እንጂ ወደ ሌላ ሆስፒታል አይላኩም ፡፡ 
ኢሶግ/ ወደሌላ ሆስፒታል እንዲሄዱ በሚነገርበት ወቅት ከተገልጋዮ የሚሰጠው ምላሽ ምን ይመስላል?
ዶክ/  ተጠቃሚዎች ሆስፒታሉ ያለበትን የቦታ ጥበትና የሰው ሓይል ሁኔታ አንዳንድ ጊዜ የማይረዱበት ሁኔታ ያጋጥማል ፡፡ በሆስፒታሉ ያሉ አልጋዎች የሚሞሉ ከሆነ ከዚያ በላይ የሚመጡትን ለመርዳት ስለምንቸገር ይሄንን ስንነግራቸው አውቃችሁ ነው ፣አገልግሎት ላለመስጠት ብላችሁ ነው በሚል ለድብድብም የሚጋበዙ አሉ፡፡ የተደበደበብንም ሐኪም አለ ፡፡ ነርሶችም እያመለጡ እየተቸገሩ የሚንቀሳቀሱበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ ይሄ ግን ለማንም የማይጠቅም ስለሆነ ቦታ የለንም ስንል ተረድተውን ሌላ አማራጭ ከመፈለግ ባሻገር አላስፈላጊ ንትርክ በመፍጠር ጊዜ የሚፈጁ የህክምናውም ስራ የሚያደናቅፉ ተገልጋዮች ያጋጥሙናል፡፡ህብረተሰቡ ችግራችንን እንዲረዳልን እንፈልጋለን፡፡
ኢሶግ/ ሙያተኞቹስ በትክክል ሓላፊነታቸውን ይወጣሉ?
ዶ/   ይሄ ጥያቄ ትክክለኛ ጥያቄ ነው፡፡ በእርግጥ ህብረተሰቡ በሚፈልገው መንገድና ሙያው በሚያዘው ስነምግባር  መሰረት ታካሚውን በተገቢው ሁኔታ ተቀብለው አስፈላጊውን አገልግሎት የማይሰጡ የጤና ባለሙያዎች መኖራቸውን እንረዳለን፡፡ የትህትና ጉድለት፣ምጥ ላይ ያለችን ሴት የማመናጨቅ፣ ተገቢውን መረጃ ያለመስጠት ፣ ለታካሚው ክብርን የመንፈግ የመሳሰሉትን ሁኔታዎች የሚያጉዋድሉ የጤና ባለሙያዎች መኖራቸውን በየጊዜው ከተገልጋዩ ከሚመጡ እሮሮዎች እንረዳለን፡፡ ነገር ግን የህክምናው ስነምግባር በሚያዘው መሰረትና ከዚያም በላይ የህክምና አገልግሎቱን የሚሰጡ ምስጉን የህክምና ባለሙያዎችም እንዳሉን የምንሰጠው አገልግሎት ምስክር ነው፡፡ ስለዚህ ህብረተሰቡ በስራ የሚንገላቱ የህክምና ባለሙያዎች ላይ ጉዳት ለማድረስ ተገቢ አለመሆኑን መረዳት ተገቢ ነው ፡፡ 
ኢሶግ/ የማዋለድ አገልግሎት የሚሰጡ የጤና ተቋማት በቂ ናቸው?የህብረተሰቡን ፍላጎት አሟልተዋልን?


ዶክ/   በአሁኑ ወቅት የማዋለድን አገልግሎት በበቂ ሁኔታ ለማዳረስ እጥረት ያለ ይመስላል፡፡ አልጋ የለንም በሚል የአገልግሎት ፈላጊዎች ከሆስፒታል ሆስፒታል የመዟዟር ሁኔታ ከዚህ የመነጨ ይመስላል፡፡ስለዚህ እንደ ጋንዲ ሆስፒታል ያሉ ተመጣጣኝ የሆነ የማዋለድ አገልግሎት የሚሰጡ የሕክምና ተቋማት መበራከት አለባቸው፡፡በአዲስ አበባ በመንግስት ሆስፒታል ደረጃ ያሉት የማዋለድ አገልግሎት የሚሰጡት ሆስፒታሎች ጋንዲ፣ ጥቁር አንበሳ ፣ፓውሎስ ፣ዘውዲቱና የካቲት ብቻ ስለሆኑ አሁን ላለው የህብረተሰብ ቁጥር ተመጣጣኝ አገልግሎት ሊሰጡ አይችሉም፡፡ ስለዚህ መንግስት ትኩረት ሰጥቶ ሌሎች የህክምና ተቋማትን ቢገነባ ጥሩ ነው፡፡ 

በእርግዝና ወቅት ወደ አንድ ሺህ ሚሊግራም አይረን ያስፈልጋል፡፡
                                       ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ                               
ሁለት ደብዳቤዎች ከተለያዩ ተሳታፊዎች ደርሰውናል፡፡ እነሱም የሚያተኩሩት በእርግዝና ወቅት ከሚያስፈልጉት ንጥረ ነገሮች መካከል ፎሊክ አሲድ እና አይረን የተባሉት ንጥረ ነገሮች ላይ ነው፡፡ ለዚህ አምድ ያስቀደምነው የአይረንን እጥረት የሚመለከተውን ነው፡፡ የፎሊክ አሲድን እጥረት መንስኤና ባጠቃላይም መፍትሔውን የሚመክረውን የባለሙያ ማብራሪያ ሳምንት እናስነብባችሁዋለን፡፡ ለሁለቱም ህትመቶች እንግዳ ያደረግነው / ዳዊት ደሳለኝን ሲሆን / ዳዊት ረዳት ፕሮፌሰርና በአ..ዩኒቨርሲት መምህር እንዲሁም የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ስፔሻሊስት ናቸው፡፡     
ኢሶግበእርግዝና ጊዜ ያስፈልጋሉ የሚባሉ ንጥረ ነገሮች ምን በመባል ይታወቃሉ ;

ዶክ/    በእርግዝና ጊዜ የሚያስፈልጉ ንጥረ ነገሮች በእርግጥ ብዙ ናቸው ፡፡ ነገር ግን ከቀረቡት ጥያቄዎች ስንነሳ እርግዝና የሚፈጥረው በጎም ይሁን አንዳንድ አዳጋች ነገሮች መኖራቸው እሙን ነው፡፡ ነገር ግን አንድ አዲስ ነገር እየተፈጠረ መሆኑን ማወቅ ይገባናል፡፡ ስለዚህ ዋናው መነጋገሪያ የሚሆነው አዲስ እየተፈጠረ ያለው ጽንስ ማንኛውም አይነት የሰውነት አ ል ማለትም የውስጥም ሆነ የውጭ የሰውነት ክፍሎች እያንዳንዱ ነገር ሊሰራ በዝግጅት ላይ መሆኑን ነው፡፡ ስለዚህ እነዚህን የሰውነት ክፍሎች  ለመስራት የሚያገለግሉ  ንጥረ ነገሮች በበቂ ሁኔ  ካልተገኙ በልጁም ላይ ሆነ በእናትየው ላይ ችግር ይከሰታል ፡፡ ከእነዚህ አስፈላጊ ንጥረ ነገሮች ውስጥ አይረን እና ፎሊክ አሲድ የሚባሉት ይገኙበታል፡፡ በእርግጥ እነዚህ ብቸ አይደሉም ፡፡ሌሎችም ንጥረ ነገሮች አሉ፡፡  አይረን ሲበል  በእርግጥ በተለምዶ ብረት የሚባለው ነው ፡፡ ግን ከብረት ጋር ምንም ግንኙነት ስለሌለው በንጥረነገርነት ብንወስደው የተሸለ ነው፡፡

ኢሶግ/ የአይረን እጥረት በምን ምክንያት ይከሰታል ?

ዶክ/    የአይረን እጥረት ከእርግዝና ጋር በተገናኝ የሚከሰተው አንዲት ሴት የደም ማነስ ሲኖርባት ነው ፡፡ ለዚህም ምክንያት ከሚሆኑት መ ከል ለምሳሌ ከእርግዝናወ በፊት የወር አበባ በጣም  ይፈስ ከነበረ ለእጥረቱ ምክንያት ይሆናል፡፡ ምክንያቱም በየወሩ ከሚፈ ው የወር አበባ ጋር አይረነን  ስለሚወጣ ነው፡፡ በእርግዝና ጊዜ የአይረን ፍላጎቱ ይጨምራል ፡፡ ምክንያቱም ልጅ እየተፈጠረ ስለሆነ ለጽንሱ ተጨማሪ አይረን ስሚያስፈልግ ነው፡፡
ኢሶግ/ አይረን በሰውነት ውስጥ ጠቀሜታው ምንድነው?
ዶክ/    አይረን ቀይ የደም ሴልን ለመስራት ያገለግላል፡፡ኦክስጂን ይዞልን ወደሰውነት ክፍላችን የሚያጉዋጉዝልን በዚህ አይረን የተሰራ  ሚከል ሔሞግሎ ን ይባላል፡፡ አንዲት ሴት በምታረግዝበት ሰአት ይህንን ተግባር ሰውነቷ እንዲያከናውን የደም መጠን ከወትሮው   ይጨምራል፡፡ ምክንያቱም ለልጁ በቂ የሆነ ኦክስጂንና ምግብ ማቅረብ ስለሚኖርባትና በወሊድ ወቅትም መድማት ስለሚገጥማት ይህ በተፈጥሮ የምታገኘው የመከሻ መንገድ ነው፡፡ አንዲት ሴት በምታረግዝበት ወቅት የደም ሴሎች በሰውነቷ ውስጥ በ ዛት ይመረ ሉ፡፡ በእርግዝና ወቅት ጽንሱ በሚያድግበት ሰ ት ላይ ደም መሰራት አለበት፡፡ ኦክስጂን መተላለፍ አለበት፡፡ ለእነዚያ ነገሮች ደግሞ አይረን ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ለአንዲት እርጉዝ ሴት በአንድ እርግዝና ጊዜ በአማካይ ወደ አንድ ሺህ ሚሊግራም የሚሆን የአይረን ንጥረ ነገር ያስፈልጋ ል፡፡ ወደ ሶስት መቶ የሚሆነው ለልጁ የቀረው ለእናትየውና ሰውነት ለሚያካሂደው ማጣራት ለመሳሰሉት ተግባሮች ያስፈልጋል፡፡
ኢሶግ ለኤረን እጥረት ምክንያት ናቸው የሚባሉት ምንድናቸው ?
ዶክ/    እናትየው ገና ወደ እርግዝናው ስትገባ አይረን የአጠራት ከነበረች አንዱ ምክንያት ሲሆን ሌላው ደግሞ ምናልባት መን  ከተረገዘ ከአንድ ልጅ ሁለት ልጅ ስለሚሆኑ ፍላጎቱ ስለሚጨምር ነው፡፡ የተመጣጠመነ  ምግብ ያለማግኘት የአይረንን እጥረት ያመጣል ፡፡ በኢትዮጵያ ከስድሳ አምስት እስከ ሰባ በመቶ ያህል ለወባ የተጋለጠ የአየር ጸባይ ስላለ በእንደዚህ ያሉ አካባቢዎች የሚኖሩ ሴቶች የደም ማነስ ችግር ስለሚኖራቸው ለአይረን እጥረት ይጋለጣሉ፡፡ የአንጀት ትላትሎችም የአይረን መጠንን በጣም ሊቀንሱ የሚችሉ ናቸው፡፡
አንዲት ሴት በተደጋጋሚ የወለደች ከሆነችና አይረን ተተክቶላት የማታውቅ ከሆነችም  እንዲዚሁ የአይረን እጥረት ሊያጋጥማት ይችላል፡፡

ኢሶግበኢትዮጵያ እንደ እንጀራ የመሳሰሉ ባህላዊ ምግቦች አይረን ይሰጣሉ ይባላል፡፡በኢትዮጵያ በምግብ እጥረት ምክንያት አይረን ይከሰታል ሲባል ይህንን ከግምት ውስጥ ያስገባ ነውን;
ዶክ/   እንጀራ የሁሉም ሰው ምግብ ነው ማለት አይቻልም፡፡በእርግጥ እንጀራ አይረን አለው፡፡ ግን አይረንን ለመተካት በቂ ነው ተብሎ የሚነገር አይደለም፡፡ ከምግብ ጋር በተያያዘ የአይረን ምንጮች ሁለት ናቸው፡፡እነሱም ከእንስሳ እና ከእንስሳ ውጭ የሚገኙ ናቸው፡፡ ለሰውነት በተለይም ከእንስሳ የሚገኘው ጥሩ የአይረን ምንጭ ነው፡፡  መቶ እጅ የሚሆን አይረን ከምግብ ብናገኝ አስር ከመቶው ያህል ወደ ደም ሲገባ ሌላው ከሰገራ ጋር አብሮ የሚወጣ ነው፡፡ ከአትክልት ዘር በተለይም ሰፋፊ አረንጉዋዴ ቅጠል ያላቸው ምግቦች አይረን በብዛት አላቸው፡፡ ግን መጠኑ ትንሽ የሆነ ስጋ ተበልቶ ብዙ አይረን የሚገኝ ሲሆን ብዙ ቅጠላቅጠል ተወስዶ ግን የሚገኘው አይረን ትንሽ ነው ፡፡ ስለዚህ  የአይረን መጠን ከምንወስደው ምግብ አይነት ብቻ ሳይሆን ምን ያህሉን ነው የምንጠቀመው የሚለውንም የሚወስነው ምንጩ ነው፡፡
ኢሶግ/ የአይረን እጥረት በእርግዝና ጊዜ ምን ችግር ያስከትላል;
ዶክ/   አይረን እናትየው ላይ ትልቁ ስራው ቀይ የደም ሴል መስራት ነው፡፡ የቀይ የደም ሴል ደግሞ ለማንኛውም የሰውነታችን አካል ማለትም ለጭንቅላት ለልብ ለጡንቻ …ወዘተ ኦክስጂን ስለሚያስፈልግ እና በሰአቱ ካልደረሰ ደግሞ መንቀሳቀስ ስለማይቻል ያንን አገልግሎት የሚሰጥ ነው ፡፡አይረን ይህንን ነገር ማሟላት ሲገባው ነገር ግን  እጥረት ካጋጠመ ያረገዘችው ሴት የልብ ትርታዋ በጣም ይጨምራል፣ድካም ያስከትልባታል ፣ስራዋን በተገቢው መስራት አትችልም፡፡ በተጨማሪም ትንፋሽ ማጠር፣ ቶሎ ቶሎ መተንፈስ ጭምር ያስከትልባታል ፡፡ ይህ ችግር በፍጥነት በሕክምና ካልተወገደ ወደልብ መድከም ያመራል፡፡

 

ኢሶግ/ የአይረን ችግሩ በወሊድ ጊዜ የሚያስከትለው ችግር ምንድነው;
ዶክ/   በወሊድ ጊዜ ያው መድማት የማይቀር በመሆኑ የአይረን እጥረት ያለባቸው ሴቶች በዚያ ጊዜ መቋቋም አይችሉም፡፡ ቁስሉም የመዳን እድሉ በአይረን እጥረቱ ምክንያት አስቸጋሪ ሁኔታ ሊገጥመው ይችላል ፡፡
ኢሶግየአይረን እጥረት በሚወለደው ልጅ ላይስ የሚያስከተለው ችግር አለ;
ዶክ/   ደስ የሚለው ነገር የልጆቹ ሁኔታ ነው፡፡ ምክንያቱም በመጀመሪያ አይረኑን እነሱ ናቸው የሚወስዱት፡፡ እናትየው አይረን ከመጠቀሟ በፊት ልጁ አይረን የሚፈልገውን ያህል የሚወስድበትን ሁኔታ ተፈጥሮ አመቻችቶአል፡፡ እናትየው በዚህ ንጥረ ነገር እጥረት ምክንያት ተጎድታለች እየተባለ ልጆቹ ግን በጤና ይወለዳሉ፡፡ ነገር ግን እርግዝናው ሶስት እና ስድስት ወር ላይ እያለ ገና የልጁ አካላት በመሰራት ላይ እያሉ እናትየው የአይረን እጥረት ካጋጠማት በእርግጥ በልጁም ላይ ችግር ይከሰታል፡፡
ኢሶግበልጆቹ ላይ የሚከሰተው ችግር ምንድነው;
ዶክ/   እርግዝናው በመጀመሪያው ስድስት ወር ላይ ባለበት ወቅት እናትየው የደም ማነስ ያለባት ከሆነ እና የአይረን እጥረት እያለባት እርግዝናው ከጀመረ ምጡ ከጊዜው ቀድሞ የመምጣትን የልጆቹ ክብደት ትንሽ መሆን ያጋጥማል፡፡ ሳንባቸው ቶሎ አይተነፍስም፡፡ ከተወለዱ በሁዋላ ከማህጸን ውጭ ያለውን አካባቢያቸውን ለመልመድ ይቸገራሉ፡፡አንጀታቸው በደንብ ስለማያድግ በተቅማጥ በመሳሰሉት ችግር ይገጥማቸዋል ፡፡ጭንቅላታቸው ውስጥ ደም የመፍሰስ ሁኔታ ይታያል፡፡ የጉበት ፣የአይን የመሳሰሉ በሽታዎች የሚገጥማቸው ሲሆን ባጠቃላይም በሽታን የመቋቋም ኃይላቸው በደንብ ስለማይዳብር ይጎዳሉ፡፡ ነገር ግን ልጆቹ እንደ እናትየው በአይረኑ ማነስ ምክንያት የሚጎዱት በቀጥታ ሳይሆን በተዘዋዋሪ መንገድ ነው፡፡
                                                      ይቀጥላል
*******************************************************   

ፎሊክ አሲድ (Folic Acid)በእርግዝና ወቅት
                                                ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ

“ ይድረስ ለኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማሽበር፡፡ በተለያዩ ጊዜያት በአዲስ አድማስ  የም ወጡአቸው የስነተዋልዶ ጤና ጉዳዮች እጅግ ጠቅመውኛል፡፡ ለዛሬ የምጠይቃችሁ በእው ላይ ስለደረሰ የጤና ችግር ነው፡፡ የፎሊክ አሲድ (Folic Acid ) እጥረት እንዳለብኝ የተነገረኝ የመጀመሪያ ልጅ ስወልድ ነበር፡፡ ነገር ግን በምጥ ሰአት  ፍኖ ሞቶአል፡፡ ነገር ግን ሕጻኑ ጀርባው ክፍት እንደሆነ ተነግሮኛል፡፡ ለወደፊቱም ማርገዝ ብትፈልጊ ከሶስት ወር ቀድመሽ ፎሊክ አሲድ የተባለውን መድሀኒት መውሰድ አለብሽ ብለው አዘዙልኝ፡፡ አሁን መድሀኒቱን እየወሰድኩ ነው፡፡ በጠቅላላው ግን ስለ ፎሊክ አሲድ ማወቅ እፈልጋለሁ፡፡ ፎሊክ አሲድ ምንድነው ? እጥረቱስ እንዴት ይከሰ ል ? “
      ከላይ ያስነበብናችሁ ከተሳ ፊ የደረሰን መልእክት ነው፡፡ ባለፈው እትማችን በአይረን እጥረት ምክንያት የሚከሰተውን ችግር በሚመለከት ከተሳ ፊ ለደረሰን ጥያቄ ዶክተር ዳዊት ደሳለኝ ማብራሪያ የሰጡ ሲሆን ለዚህ እትምም የፎሊክ አሲድ እጥረትን በሚመለከት መልስ ሰጥተዋል፡፡ ዶ/ር ዳዊት ደሳለኝ ረዳት ፕሮፌሰርና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ፋክልቲ መምህር እንዲሁም የማህጽንና ጽንስ ሕክምና ስፔሻሊስት ናቸው፡፡
            -------------------------//////--------------------------

 

            ፎሊክ አሲድ በሰውነ ችን ውስጥ  ነጭ የደም ሴል እና ቀይ የደም ሴልን የሚሰራ ንጥረ ነገር ነው፡፡ ፎሊክ አሲድ ከዚህ በተጨማሪ አንድን ሴል በዋናነት በምን መልኩ መስራት እንዳለበት የሰውነ ችን ሂደት የሚወስነውን ነገር ለመስራት የምንጠቀምበት ነው፡፡ ስለዚህ የፎሊክ አሲድ እጥረት በማንኛውም የሰውነት ከፍል ላይ ጉዳት ሊያደርስ የሚችል ነው፡፡  የፎሊክ አሲድ መገለጫው በተለይም በእርግዝና ሰአት ላይ የደም ማነስ ሲሆን በእርግጥ የአይረን እጥረትን እንደሚያስከትለው ከባድ አይነት የደም ማነስ አይደለም፡፡ የፎሊክ አሲድ የነጭ የደም ሴል በሚጎዳበት ጊዜ ተያይዞ የሚመጣ ችግር ነው፡፡
      የፎሊክ አሲድ እ ረት በተለይም ከእርግዝና ጋር በተያያዘ በልጅ ላይ ከፍተኛ ጉዳት የሚያስከትል ነው፡፡ ፎሊክ አሲድ ያነሳቸው ልጆች ሲወለዱ የተለያዩ ተፈጥሮአዊ ችግሮችን ይዘው ሊወለዱ ይችላሉ ፡፡ አንዳንዴ የጀርባቸወ አጥንት ሳይዘጋ ክፍት ሆኖ የመወለድ ችግር ሊከሰት ይችላል፡፡ አንዳንዴ አንድ እጅ ሳይኖር ወይንም ነርቮቹ ሳይሸፈኑ ወደውጭ ተጋልጠው ይወለዳሉ፡፡ ነርቮች ሳይሸፈኑ ከተወለዱ ልጆቹ ከፍተኛ አደጋ ይደርስባቸዋል፡፡ እግር እንዳይንቀሳቀስ ወይንም ሽንትን መቆጣጠር እንዳይችሉ...ወዘተ  ሆነው ሊወለዱ ይችላሉ፡፡
የፎሊክ አሲድ እጥረት ወይንም አለመኖር የሚከሰተው ንጥረ ነገሩ በምግብ ውስጥ በሚኖረው እጥረት ጭምር ነው፡፡ ለምሳሌ በአደጉት አገሮች በማንኛውም ምግብ ላይ የተወሰነ መጠን ፎሊክ አሲድ እንዲገባ ይደረጋል፡፡  ፋብሪከዎች በሚያመርቷቸው ምግቦች ላይ ይህንን ንጥረ ነገር አከተው ለመስራት ግዴ  አለባቸው፡፡ፎሊክ አሲድ በሩዝ በዳቦ  በፓስ  በመሳሰሉት ሁሉ ይጨመራል፡፡ ስለሆነም ማንኛዋም ለመውለድ የምትፈልግ ሴት ይህንን ንጥረ ነገር ያካተተውን ምግብ መመገብ ይጠበቅባ ል፡፡ በእርግጥ በእኛ ሀገር በዚህ ሁኔ  የተዘጋጁ ምግቦች ስለማይገኙ በሕክምና የሚ ዘዘውን መድሐኒት መውሰድ ይጠበቅባቸዋል፡፡ መጠኑን በሚመለከት ለምሳሌ አንድ ልጅ ያረገዘችና መን  ያረገዘች እኩል መጠን አይወስዱም ፡፡ በተለይም ቀደም ሲል በነበራቸው የመውለድ አጋጣሚ ችግሩ የገጠማቸው ሴቶች ከሆኑ በመቀጠል ለተጨማሪ ችግር እንዳይጋለጡ ለማድረግ የሚሰጣቸው መድሀኒት ምንም ችግር ገጥሞአቸው ከማያውቁት ጋር እኩል አይደለም፡፡
ባለፈው ህትመት ለንባብ ወዳበቃነው የአይረን እጥረት ስንመለስ እ ረቱን ለማስወገድ እርምጃ የሚወሰደው በእርግዝናው ጊዜ ነው፡፡ ምክንያቱም ችግሩ መኖሩ የሚታወቀው እርግዝናወ ሲከሰት በመሆኑ ነው፡፡ በዚህ ላይ ችግሩ የሚከሰተው በእናትየው ላይ ነው እንጂ በተረገዘው ልጅ ላይ አይደለም፡፡ የፎሊክ አሲድ ግን እርግዝናው ከመከሰቱ አስቀድሞ ነው ክትትሉ መደረግ ያለበት፡፡ ምክንያቱም እናትየው ላይ የሚ የው ችግር እጅግ አናሳ በመሆኑና በአብዛኛው ችግሩ የሚከሰተው ጽንሱ ላይ ስለሆነ ነው፡፡ ጽንሱ ለችግር እንዳይጋለጥም ገና እንደተረገዘ በሚደረገው ክትትል እርጉዝዋ ሴት  ፎሊክ አሲድ በብቃት እንዳላትና እንደሌላት መረጋገጥ አለበት፡፡ የፎሊክ አሲድ እጥረት ያለባት ሴት እጥረቱን የሚከላከልላትን መድሀኒት መውሰድ ያለባት ግን ከማርገዝዋ አስቀድሞ ነው፡፡ ነገር ግን ይህንን ለማድረግ በተለይም ባላደጉት አገሮች በአብዛኛው እንደማይቻል ነው ሁኔ ዎች የሚያሳዩት ፡፡ ምክንያቱም በአላደጉት አገሮች ልጅ የሚወለደው ብዙውን ጊዜ አቅዶና ተዘጋጅቶ ስለማይሆን ነው፡፡ ምናልባትም ልጅ መውለድ እንፈለጋለን ብለው አስበው ይወልዳሉ ቢባል እንኩዋን ዝግጅቱ ከኢኮኖሚ አንጻር እንጂ የጤናን ሁኔ  አስቀድሞ የማረጋገጥ አንሄድ የለም ማለት ይቻላል ነገር ግን ሴቶች ልጅ መውለድ ሲፈልጉ አስቀድመው የህክምና ምርመራ በማድረግ ጤንነ ቸወ ያለበትን ሁኔ  የማረጋገጥ ግዴ  እንዳለባቸው ቢያውቁ ለመፍትሔው ይረዳል ፡፡
ምአጠቃላይም የአይረንንም ሆነ የፎሊክ አሲድን እጥረት ለመከላከል በመድሀኒት መልክ የሚሰጡ ነገሮች አሉ፡፡ በቀን ምን ያህል የሚለውን የተጠቃሚዋ ሁኔታ ይወስነዋል፡፡ ሕክምናው የሚሰጠው በሁለት መልክ ነው፡፡ አንድ ሴት የአይረን እጥረቱ ተጠቂ ሳትሆን ነገር ግን ካላት ንጥረ ነገር ላይ ብዙ እንዳታወጣና በሁዋላ እንዳትጎዳ ሲባል መድሀኒቱ የሚሰጥበት ሁኔታ አለ፡፡ይሄኛው እርዳታ እንጂ ሕክምና አይደለም፡፡  በእርግዝናው ወቅት ችግሩ መኖሩ ሲረጋገጥ ግን በሕክምና መልክ ይሰጣል፡፡ በሁለቱ መንገዶች ማለትም በተለያየ ሁኔ  ለሚጠቀሙት መጠኑ የተለያየ ነው፡፡
 መድሀኒቱ በሕክምና መልክ በሚወሰድበት ጊዜ አንዳንድ የህመም ስሜቶችን ሊያስከትል ይችላል፡፡ ለምሳሌ እንደጨጉዋራ ሕመም ወይንም ድርቀት የመሳሰለውን ችግር ሊያስከትል ይችላል፡፡
  ከምግብ ጋር ከሚ ሰደው አይረን ከአስር እስከ አስራ አምስት በመቶ ያህል የሚሆነው ብቻ  ነው ወደ ደም የሚገባው፡፡ ስለዚህ እጥረቱን ለመከላከል መድሀኒቱ በሚወሰድበት ሰአት ላይ በተለያዩ የህመም ምክንያቶች ወይም በአመጋገብ ካለን ልምድ በመነሳት መድሐኒቱን ከወተት ወይንም ከጭማቂ፺ጁውስ፻ ከመሳሰሉት ጋር የሚወስዱ ታካሚዎች ያጋጥማሉ ፡፡ ነገር ግን ከወተት ጋር መድሀኒቱን መውሰድ ትክክል አይደለም ፡፡ ምክንያቱም በወተት ውስጥ ካልሲየም ስላለና ካልሲየም ደግሞ ከአይረን ጋር በተመሳሳይ ጊዜ ሲወሰድ አይረኑ ወደደም እንዳይገባ ስለሚከላከል ጉዳት አለው፡፡ አይረን በደንብ ወደደም እንዲገባ የሚያደርገውን ማንኛውም ቫይታሚንን የያዘ ለምሳሌ እንደብርቱካን የመሳሰሉ ነገሮችን አብሮ መውሰድ ይጠቅማል፡፡አይረን ወደደም እንዳይገባ የሚከላከሉትን ምግቦች ግን ከመድሀኒቱ ጋር ባልተቀራረበ ሰአት መጠቀም ይቻላል፡፡  መድሐኒቱ በሚወሰድበት ጊዜ የአይነምድር መጥቆር ወይንም መድረቅ ሊከሰት ይችላል፡፡ ሽንት ሊቀላ ይችላል፡፡ ይሄ ግን ችግር እያመጣ ሳይሆን እንዲያውም ያቺ እርጉዝ ሴት መድሐኒቱን በትክክል እየወሰደች መሆኑን ነው የሚያመላክተው፡፡


መድሐኒቱ በአንድ ጊዜ ለሶስት ወር እና ከዚያም በላይ እስከሚወልዱ ድረስ ሊሰጥ ይችላል፡፡ ስለሆነም ያላደጉ ልጆች በቤት ውስጥ ሊኖሩ ስለሚችሉ እና ይህ ኪኒን ደግሞ እንዱ ፍሬ እንኩዋን ለአንድ ሕጻን ከፍተኛ ጉዳት ሊያስ ትል ስለሚችል ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግን የሚፈልግ ነው፡፡ መድሐኒቱ ሕጻናት በሚደርሱበት አካባቢ መቀመጥ የለበትም፡፡ ከዚህ ውጪ ግን መድሐኒቱን የሚወስዱ ሴቶች ምናልባት የጨጉዋራ የመሳሰሉትን ችግሮች መቋቋም እንኩዋን ባይቻሉ እንደስጋ  አሳ  ወይንም እነዚህ ምግ ች የያዙትን ቫይታሚን የመሳሰሉትን የሚያሙዋሉ ሌሎች ምግቦችን በመመገብ

*******************************************

ሕጻናት እና ኤችአይቪ  ኤይድስ

  • በአለም ላይ በየሰአቱ ሰላሳ አንድ (31)ሕጻናት በኤችአይቪ ምክንያት ይሞሉ፡፡

ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
                                               
      ኤችአይቪ ኤይድስ  በሕጻናት ላይ የሚያደርሰውን ዘርፈ ብዙ ችግር በድህረገጹ ለንባብ ያበቃው በምህጻረ ቃሉ  AVERT   የተሰኘው በኤችአይቪ ዙሪያ የሚሰራ አለምአቀፍ ግብረሰናይ ድርጅት ነው፡፡
እንደ   AVERT   እማኝነት በአለም ዙሪያ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሕጻናት በየአመቱ በኤችአይቪ ኤይድስ ቫይረስ ይያያዛሉ፡፡  ከሚሊዮን የሚበልጡት ሕጻናት ደግሞ ኤችአይቪ ኤይድስ እራሳቸውን ባይያዛቸውም እንኩዋን በቫይረሱ ምክንያት በቤተሰቦቻቸወ ላይ እና በህብረተሰቡ ዘንድ በሚደርሰው የኢኮኖሚና  ማህበራዊ ችግር ማለትም እንደስራ ማጥት ህመም እና ሞት በሚያስከትሉት ችግር ምክንያት ለከፋ ስቃይ ይዳረጋሉ ፡፡
      ሕጻናቱ በኤችአይቪ እንዳይያዙና እነሱን በሚንከባከቡዋቸውም ላይ በሚደርሰው ችግር ምክንያት እንዳይሰቃዩ ለማድረግ ብዙ ስራዎችን መስራት ይጠበቃል፡፡ ነገር ግን በአለም ላይ በጉዳዩ ዙሪያ ሰፋ ያለና ሁሉን ነገር ያካተተ ጥናት ባለመደረጉ ምክንያት መ ሄድ የሚገባቸወ ምርመራዎች፣ የሚሰጡ ጸረ ኤችኤቪ መድሀኒቶች እና የመከላከል ስራዎች በእጅጉ እጥረት የሚ ይባቸው በመሆኑና አድሎና መገለሉ ባለመወገዱ በአለማችን እጅግ በርከ  ሕጻናት ለስቃይ ይዳረጋሉ፡፡
            AVERT ባወጣው መረጃ መሰረት፣  

  • በአለማችን እስከ 2008 ዓ/ም መጨረሻ ድረስ ሁለት ነጥብ አንድ ፺2.1 ፻ሚሊዮን ሕጻናት ከኤችአይቪ ቫይረስ ጋር እንደሚኖሩ ተመዝግቦአል፡፡
  • በግምት አራት መቶ ሰላሳ ሺህ፺430.000፻የሚሆኑ ሕጻናት በየጊዜው በኤችአይቪ የሚያዙ መሆኑ በዚሁ በ2008 ዓ/ም ተመዝግቦአል፡፡
  • በአለም ላይ በኤችአይቪ ኤይድስ ምክንያት ከሞቱት ሁለት ሚሊዮን ሰወች ከሰባቱ አንዱ ሕጻን እንደሆነ በ2008 ዓ/ም ተመዝግቦአል፡፡
  • በየሰአቱ ወደ ሰላሳ አንድ፺31፻ የሚሆኑ ሕጻናት በኤችአይቪ ኤይድስ ምክንያት ይሞ ሉ፡፡

በአለም ላይ በኤችአይቪ ምክንያት ከሚሞቱት አስር ሕጻናት ውስጥ ዘጠኝ ያህሉ የኤችአይቪ ቫይረስ በስፋት በሚሰራጭባቸውና ለመከላከል እርምጃውም ተገቢውን ድጋፍ ለማድረግ ችግር ባለባቸው ከሰሐራ በ ች ባሉ የአፍሪካ ሐገራት ውስጥ እንደሆነ ነው መረጃው የሚጠቁመው፡፡ ከሰሀራ በ ች ካሉት ሀገራት በመቀጠል ያለውን ድርሻ የሚወስዱት በካሪቢያን ፣ ላቲን አሜሪካና ደቡብ ምስራቅ እስያ ውስጥ ያሉት ሐገራት ናቸው፡፡
የህጻናቱ በኤችአይቪ ቫይረስ የመያዝ ምክንያቶች ሲፈተሹ ወደ ዘጠና በመቶ የሚሆኑት ኤችአይቪ ቫይረስ የያዛቸው ከእና ቸው በእርግዝናና በወሊድ ጊዜ ወይንም ደግሞ በጡት ማጥባት ወቅት እንደሚሆን ጥናቶች ያስረዳሉ፡፡ ሕጻናቱ በኤችአይቪ የሚያዙበት ምክንያት ከወሊድና ከጡት መጥባት ጋር በተያያዘ ብቻም አይደለም፡፡ በተለይም የኤችአይቪ ስርጭት በብዛት በሚ ይበት አካባቢ የሚኖሩ ከሆነ እራሳቸውም ሆኑ ቤተሰቦቻቸው በቀጥ  በቫይረሱ ባይያዙ እንኩዋን ከሌሎች ጋር በሚኖረው የተለያየ ግንኙነት በቫይረሱ የመያዝ እድላቸወ የሰፋ ይሆናል፡፡
ከላይ ከተጠቀሱት ምክንያቶች በተጨማሪም አንዳንድ ሕጻናት በሚደረግላቸው የህክምና ስራ ከጥንቃቄ መጉዋደል የተነሳ ወይንም በጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች ፺እንደግርዛት፻ በመሳሰሉት ምክንያቶች በቫይረሱ ሊያዙ ይችላሉ፡፡ ይህ በተለይም ባላደጉ አገሮች የሚ ይ ችግር ነው፡፡ በእርግጥ በእድሜያቸው ከፍ ያሉት ሕጻናት እራሳቸው በሚፈጽሙት ወሲብ እና በአደንዛዥ እጽ አጠቃቀማቸው ምክንያት በቫይረሱ ሊያዙ ይችላሉ፡፡
ኤችአይቪ ልቅ በሆነ የግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት ይተላለፋል የሚለው ከህጻናቱ የእድሜ ሁኔ ጋር ሲ ይ ብዙም ተያያዥ ባይመስልም ነገር ግን አንዳንድ ጊዜ ሕጻናቱ ያለእድሜያቸው በሚፈጽሙት የግብረስጋ ግንኙነት ምክንያትም ይሁን በቫይረሱ በተያዙ ሰዎች በሚደርስባቸወ ተገዶ የመደፈር ሁኔ  ለኤችአይቪ ኤይድስ ይጋለጣሉ፡፡ ከሰሀራ በ ች ባሉ የአፍሪካ አገራት አስራ ስድስት ከመቶ የሚሆኑት ወጣት ሴቶች ማለትም በእድሜያቸው ከአስራ አምስት እስከ አስራ ዘጠኝ የሚሆኑት እና አስራ ሁለት ከመቶ የሚሆኑት ወጣት ወንዶች የግብረስጋ ግንኙነት የፈጸሙት በእድሜያቸው አስራ አምስት አመት ሳይሞሉ መሆኑ ተረጋግጦአል ይላል መረጃችን AVERT  ፡፡

በአፍሪካ ኤችአ ቪ በደማቸው ውስጥ ኖሮ ከሚወለዱ ሕጻናት ከሶስቱ አንዱ ከአንድ አመ  ልደ ቸው አስቀድሞ የሚሞቱ ሲሆን ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ደግሞ ሁለተኛ አመ ቸውን ሳይደፍኑ ይሞ ሉ፡፡ በእነዚህ የእድሜ ክልሎች ያልሞቱት አብዛኞቹ ሕጻናት ደግሞ ከአምስት አመት ልደ ቸው አስቀድሞ ሕይወ ቸው እንደሚያልፍ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
ኤችአይቪ ህጻናቱን የሚጎዳበት ሶስት መንገዶች አሉት ፡፡

  • በኤችአይቪ ቫይረስ ሕጻናቱ እራሳቸወ በመያዛቸው፣
  • ቤተሰቦቻቸው በቫይረሱ በመያዛቸው፣
  • አብረዋቸው የሚኖሩ የሕብረተሰብ ክፍሎች በቫይረሱ በመያዛቸው    

በእነዚህ ምክንያቶች ሕጻናት በቀጥ  የሚያገኛቸው የህይወት ውጣ ውረድ ደግሞ፣

      • ሕጻናቱ በኤችአይቪ ቫይረስ ከተያዙ ቤተሰቦቻቸው ጋር ይኖራሉ፡፡
      • በኤችአይቪ የተያዙ ቤተሰቦቻቸውን በስራ እንዲያግዙ ይገደዳሉ፡፡
      • ሕጻናቱ ከወላጆቻቸው አንዳቸውንም ሆነ ሁለቱንም ስለሚያጡ ወላጅ አልባ ይሆናሉ፡፡

ኤችኤቪ ኤይድስ በሚያደርሰው ችግር ምክንያት በሕጻናቱ አስተዳዳሪነት የሚመሩ ቤቶች ቁጥራቸው እየጨመረ በመምጣት ላይ መሆኑም አንዱ በህጻናቱ ላይ ካለአቅማቸወ የሚደርስባቸው ችግር ነው፡፡

ኤችአይቪ ኤይድስ ሕጻናቱን በሚያገለግሉ አካላት ላይ በሚያደርሰው ችግር ምክንያትም የተለያዩ መሰረ ዊ ነገሮችን ያጣሉ፡፡

  • ኤይድስ በህብረተሰቡ ላይ በሚያደርሰው የህይወትና የጤና ችግር ምክንያት ሕጻናቱ ከሚያጡት ነገር መካከል የአስተማሪዎች ሁኔ  ይገኝበ ል፡፡ትምህርት ቤቶች መምህራኖቻቸውን ባጡ ቁጥር በትምህርት አሰጣጡ ላይ ችግር ያስከትላል፡፡
  • የህክምና ባለሙያዎችም በቫይረሱ ከሚያዙትና ከሚሞቱት መካከል በመሆናቸው የሕጻናቱን የጤና ሁኔ  በመከ ተሉ ረገድ ችግር ሊያስከትል ይችላል ፡፡
  • ሕጻናቱ ከምንም በላይ የሚያቀርቡዋቸውንና አቻዎቻቸውን በኤችአ ቪ ቫይረስ ምክንያት ሲ ያጡ በብቸኝነት ይጎዳሉ ፡፡
  • ሕጻናቱ ከቤተሰቦቻቸው መካከል በኤችአይቪ ቫይረስ የተያዘ መኖሩ በሌሎች ከ ወቅ የሚቀርባቸው ስለሚያጡ መገለል ይደርስባቸዋል፡፡

ኤችአይቪ ኤይድስ በተለይም ባላደጉ አገራት ልማትን ወደሁዋላ እንደጎተተና የኢኮኖሚን እድገት ከፍ እንዳይል ማድረጉ እሙን ነው፡፡ በር   ቤተሰቦች እንዲሁም ጉዋደኛሞች እና የህብረተሰብ ክፍሎች ላይ መጥፎ ስሜትን ማሳደሩም እርግጥ ነው፡፡ ሕጻናቱን ስንመለከት ደግሞ ቤተሰቦቻቸውም ሆኑ እራሳቸው ሕጻናቱ በቫይረሱ ባይያዙም እንኩዋን በተዘዋዋሪ መንገድ ሕይወ ቸውን እንደሚያሰናክለው የሚ ይ እውነ  ነው፡፡
ሕጻናቱ በኤችአይቪ ምክንያት ሊያጡዋቸው ከማ ገቡ መሰረ ዊ አገልግሎቶች ዋና ዋናዎቹን እንኩዋን ብንመለከት አንዱ የሕክምና አገልግሎት ነው፡፡የጤና ተቋማት በኤችአይቪ ሕመምተኞች የመጣበብ ሁኔ ን ጨምሮ የሙያተኞች በቫይረሱ ምክንያት መጉዋደል አንዱና ትልቁ ችግር ነው፡፡ ሌላው ሕጻናቱ ሊያጡት የማይገባ መሰረ ዊ ነገር የትምህርት ጉዳይ ነው፡፡ ፺በስዋዚላንድ በ2020 እስከ ሰባት ሺህ ፺7000 ፻ አዳዲስ መምህራን በኤይድስ ሕይወ ቸው ያለፉትን መምህራን እንዲተኩ ይዘጋጃሉ፡፡፻ በሌላ በኩል ህጻናቱ በቫይረሱ እንዳይያዙ ትምህርት ቤቶች ሊያስተምሩዋቸው ይገባል፡፡ ቤተሰብ ለህጻናቱ ስለኤችአ ቪ ግልጽ ውይይት በማድረግ ሕጻናቱ ማግኘት የሚገባቸውን መረጃ እንዲያገኙ ማገዝ ይገባል፡፡ከዚህ በተጨማሪ ኤችአይቪ ኤይድስ በእርግዝና ጊዜ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ የሚረዳ የህክምና ክትትል ማድረግና እንዲሁም ጡት በማጥባት ቫይረሱ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ ተገቢውን አገልግሎት መስጠት ተገቢ ነው፡፡ በአገራችንም ይህ ኤችአይቪ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ ለማድረግ የሚያስችለው ስራ፺     ) በመ ሄድ ላይ ነው፡፡ ፕሮጀክቱ ከምን ደረጃ ደርሶአል? በቀጣዩ ሳምንት ለንባብ እንለዋለን፡፡

********************************

ከሰላሳ እስከ አርባ (30-40) ሚሊዮን ሰዎች ከኤችአይቪ ቫይረስ ጋር ይኖራሉ፡፡
                                        ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ

በኢትዮጵያ ፣

      • አስራ ስድስት ሚሊዮን ሰዎች የኤችኤቪ ምርመራ አድርገዋል፡፡
      • አንድ መቶ ሰባ ሽህ ሰዎች የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡         
      • በ2007/አስራ አራት ሺሕ ሕጻናት ሲወለዱ የኤችአይቪ ቫይረስ ተገኝቶባቸዋል፡፡

                                               
ፒኤምቲሲቲ (pmtct…prevention mother to child transmission) ኤችአይቪ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ የሚደረግ የመከላል ስራ በመንግስት ሆስፒ ሎች ቀደም ሲል የተጀመረ ቢሆንም በግል የህክምና ተቋማት ተግባራዊ እንዲሆን የሚያግዘው ፕሮግራም የተጀመረው ግን እንደውጭው አቆጣጠር በ2007/2008 ነው፡፡ የኢትዮጵያ የማህጽንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር ፺ኢሶግ፻ ባደረገው የዳሰሳ ጥናት የኤችአይቪ ቫይረስ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ የሚያስችለውን የህክምና አገልግሎት በመስጠቱ ረገድ በግል የህክምና ተቋማቱ የሚ የውን ችግር ለመፍ ት መደረግ ያለበትን እንቅስቃሴ ይፋ ካደረገ ጀምሮ ስራው በተለያየ መልኩ ተጀምሮአል፡፡ ኢሶግ ስራው የተጀመረባቸውን የግል የህክምና ተቋማትንና ድጋፍ የሚያደርጉ አካላትን በአመት ሁለት ጊዜ ወደ መድረክ በመጋበዝ የስራ አካሄዱን ይፈትሻል፣ ምን ተሰርቷል፣ ምን ችግርስ ነበረ፣ ምን ጥሩ ነገር አለ ፣ወደፊትስ የሚለውን ይነጋገራል፡፡ ይህንኑ ስብሰባ እንደውጭው አቆጣጠር ዲሴምበር 31/2009 በአዲስ አበባ በማህበሩ ፕሮጀክት ቢሮ የስብሰባ አዳራሽ አካሂዶአል፡፡
ዶ/ር አሸብር ጋይም የኢሶግ ፕሬዝደንት እንደተናገሩት ኤችአይቪ ከተከሰተ 30 አመት ሆኖ ል፡፡ አለም ከተፈጠረች ጀምሮ የተለያዩ በሽ ዎች በአለማችን ችግር አስከትለው የነበረ ቢሆንም እንደ ኤችአይቪ ግን አስከፊ የተባለ የለም፡፡ ብዙዎቹ ወረርሽኞች ተፈጥረው ከአምስት አመት በላይ  ሳያስቆጥሩ ነው መፍትሄ የተገኘላቸው፡፡ ወረርሽኞቹም በተወሰኑ የአለም ክፍሎች ይከሰ ሉ እንጂ እንደኤችአይቪ በመላው አለም ሕዝብ ላይ የጤና ችግር አያስከትሉም ፡፡ ሌሎቹ በሽ ዎች ለምሳሌ ...ኢንፍሉዌንዛ እስያን አውሮፓን እና የተወሰኑ የአለም ክፍሎችን ባባዛኛው ያጠቃ ሲሆን ኤችአይቪ ግን ያልነካው የአለም ክፍል የለም፡፡ኤችአይቪ ከሌሎች በሽ ዎች የተለየ የሚያደርገው ለህልፈት በዳረጋቸው ሕዝቦች መጠንም የተለየ መሆኑ ነው፡፡ ሌሎቹ ወረርሽኞች እንደተከሰቱ ችግር ቢያስከትሉም ሂደ ቸውን ጨርሰው ቆመዋል፡፡ ኤችአይቪ ግን በዚህ ሰላሳ አመት አሁንም ሂደቱን አላቆመም፡፡
ኤችአይቪ ኤይድስ በአለም ላይ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ሕይወት ከማጥፋቱም በላይ ከቫይረሱም ጋር የሚኖሩትን በተመለከተ የአለም የጤና ጥበቃ ድርጅት እንደሚገልጸው ከ፺30-40፻ ከሰላሳ እስከ አርባ ሚሊዮን ይሆናሉ፡፡ ኤችአይቪ ከዚህ በሁዋላ ለምን ያህል ጊዜ ጥፋቱን እንደሚቀጥልም አይ ወቅም፡፡ በእርግጥ የኤችአይቪን ስርጭት በብዙ የአለም ክፍል የተቆጣጠሩት ሲሆን ከሰሀራ በ ች ባሉት የአፍሪካ ሀገራት ግን እስከአሁንም መግ ት ያልተቻለበት ሁኔ  ላይ ነው ያለው፡፡ በኢትዮጵያም ምንም እንኩዋን እንደ አንዳንድ የአፍሪካ ሀገራት የሰፋ ባይሆንም ችግሩ ቀላል የሚባል አይደለም፡፡ ይህንን ችግር ለመፍ ት በመንግስት በሙያ ማህበራት መንግስ ዊ ያልሆኑ ድርጅቶችና አለም አቀፍ ድርጅቶች ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ ነው፡፡
በኢትዮጵያ ኤችአይቪን በመከላከሉ ረገድ አመርቂ የሚባሉም ባይሆኑ ከፍተኛ ውጤት እየ የባቸው ካሉት ነገሮች መካከል እንደ ኤችአይቪ መከላከልና መቆጣጠሪያ       መረጃ ወደ አስራ ስድስት ሚሊዮን የሚሆኑ ሰዎች የኤችአይቪ ምርመራ በማድረግ እራሳቸውን አውቀዋል፡፡ ወደ አንድ መቶ ሰባ ሽህ የሚሆኑ ደግሞ የጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡              
ጤና ለማንም ሰው በችሮ  የሚሰጥ ሳይሆን በተፈጥሮው ሊገኝ የሚገባወ መብት ነው፡፡ ስለዚህ አንድ ሕጻን ከኤችአይቪ ነጻ ሆኖ የመወለድ መብት አለው፡፡ በእርግጥ በመንግስት ደረጃ ሌሎችም አደገኛ የሆኑና ትኩረት የተሰጣቸው ማለትም እንደ ወባ ...የእናቶችና የህጻናት ጤና ...ቲቪ የመሳሰሉ በሽ ዎች ቢኖሩም ኤችአይቪ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ የማድረግ ሂደቱም ሌላው ትኩረት የተደረገበት ነው፡፡ ይሁን እንጂ ውጤቱ እንደሚያሳየው ኤችአይቪ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ የሚደረገው የስራ ሂደት ገና ብዙ እንደሚቀረው ነው በጤና ጥበቃ ሚኒስ ር ተወካይ ዶ/ር ንግስት ተስፋዬ የተገለጸው፡፡ እንደ ውጭው አቆጣጠር በ2007/ዓ/ም ወደ አስራ አራት ሺሕ የሚሆኑ ሕጻናት ከኤችአይቪ ቫይረስ ጋር ተወልደዋል፡፡ ይህ መረጃ በህክምናው ስራ ላይ ለተሰማሩ ባለሙያዎችም ሆነ ለመላው ሕብረተሰብ  እጅግ አሳሳቢ ነው፡፡  ቀደም ባሉት ጊዜያት ማለትም ጸረ ኤችአይቪ መድሀኒት ባልነበረበት ወቅት በኤችአይቪ ቫይረስ ለተያዘ ሰው የሚሰጥ መድሀኒት ስላልነበረ አገልግሎት ፈላጊዎች ወደሕክምና ተቋማቱ ቢሄዱም እንኩዋን ለመርዳት አስቸጋሪ የሆነ ሁኔ  እንደነበር እሙን ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት ግን መድሀኒቱ በአገር ውስጥ ስላለ እርጉዝዋ ሴት በጊዜ ወደ ሕክምና ተቋሙ በመሄድ አስፈላጊውን አገልግሎት ከገኘች ሕጻናቱ ከኤችአይቪ ነጻ ሆነው የመወለድ እድል አላቸው፡፡ ኤችአይቪን በመከላከሉ ረገድ ይህንን ያህል አገልግሎት ተሰጠ ወይንም ይህንን ያህል ሴቶች ትምህርቱን ወሰደዋል በሚል በቁጥር ከመግለጽ ባሻገር አገልግሎቱንያገኙት እናቶችና ሕጻናት  በምን መልክ እንደተስተናገዱ እና ምን ያህል የሚረኩበት ምላሽ ከጤና ተቋማቱ እንዳገኙ ማረጋገጥ ሌላው ሊተኮርበት የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ በትህትና ከማነጋገር ጀምሮ በሚያውቁት ወይንም በሚገባቸው ቋንቋ መረጃ መለዋወጥ እንዲሁም ተገቢውን ክብርና ትኩረት መስጠት፣ምስጢርን መጠበቅ ከሕክምና ባለሙያው ይጠበቃል ፡፡ ምክንያቱም ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ እናቶች የህክምና ክትትሉን ሊያቋርጡ ስለማይገባ በፍቅርና በፍላጎት እንዲሁም በእምነት በአስፈላጊው ጊዜ ሁሉ ወደ ሕክምና ተቋሙ እንዲሄዱ ስለሚያስፈልግ ነው፡፡                                                                                                                                                                                                                                                                                                                                                                                                                          
እንደ ዶ/ክ እያሱ መስፍን የፒኤምቲሲቲ ፕሮጀክት አስተባባሪ ኤችአይቪ ከእናት ወደልጅ እንዳይትላለፍ የሚያስችለውን ስራ ለመስራት የተነደፈው ፕሮጀክት ከተጀመረ እስከአሁን ባለው የስራ ጊዜ አርባ ከሚሆኑ የግል ህክምና ተቋማት ጋር ስራው መልክ እንዲይዝ እየተደረገ ነው፡፡ እነዚህ አርባ የግል የህክምና ተቋማት በመላው አገሪቱ የሚገኙ ሲሆን ሶስት ክልሎችን ማለትም አፋር፣ ቤንሻናጉልና ጋምቤላን ግን አይመለከትም፡፡ በአፋር፣ ቤንሻንጉልና ጋምቤላ ላይ የግል ሆስፒ ል ወይንም የእናቶችና የህጻናት ክሊኒኮች ባለመኖራቸው ስራውን መስራት ለጊዜው ባይቻልም ወደፊት ግን የግል የህክምና ተቋማቱ ሲኖሩ ሊጀመር እንደሚችል  ውቆአል፡፡ ከአርባው ሆስፒ ሎች አብዛኞች ማለትም ሰላሳዎቹ የሚገኙት በአዲስ አበባ ነው፡፡ አዲስ አበባ ላይ የግል የህክምና ተቋማትንም ሆነ የመንግስት የህክምና ተቋማትን የሚጠቀሙ ተገልጋዮችን ለመርዳት ሲባልም በመንግስት ነርሶች ሰልጥነው በህብረተሰቡ ውስጥ ዘልቀው በመግባት አስፈላጊውን የኤችአይቪ የመከላል ስራ የጀመሩበት ሁኔ  አለ፡፡በዚህ ዘርፍ በማህበራዊ አገልግሎቱ ደረጃ የመከላከል ስራውን ሕብረተሰቡ እንዲሳተፍበት ማድረግ የሚያስችለውን ስራ መስራት አስፈላጊ ሲሆን አንዲት እናት ወደህክምና ጣቢያው ከአንድ ግዜ በላይ ሳትሄድ ብትቀር ምክንያቱን የማወቅ ጥረት መኖርና የድጋፍ እርምጃውንም ማስተከከል እንደሚገባ በስብሰባው ተጠቁሞአል፡፡
በፒኤምቲሲቲ (pmtct ) ፕሮጀክት 2008/2009  ቅዶ ከነበረው፣

    • ኤችአይቪ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ የሚደረገውን የህክምና ክትትል በሰላሳ የግል የህክምና ተቋማት ለማስጀመር በ ቀደው መሰረት ተግባራዊ ሆኖአል፡፡
    • ፺9450፻ ዘጠኝ ሺህ አራት መቶ ሀምሳ ለሚሆኑ እናቶች የኤችአይቪ ምርመራ በማድረግ  እራስን ማወቅና ኤችአይቪን የመከላከል የምክር አገልግሎት የመስጠት እንዲሁም ሌሎች ተዛማጅ ስራዎችን የማከናወን ስራ ከ ቀደው በላይ   ወደ ፺12,100፻ አስራ ሁለት ሺህ አንድ መቶ ያህል ለሚሆኑት አገልግሎት ተሰጥቶዋል፡፡
    • 180 የጤና ባለሙያዎች እንዲሰለጥኑ  ቅዶ ወደ 190 የሚሆኑ ስልጠናውን አግኝተዋል፡፡  

ኤችአይቪ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ ለማድረግ ስራው የሚጀመረው በእርግዝና ወቅት ሲሆን ከወሊድ በሁዋላና ጡት በማጥባት ወቅትም የሚቀጥል ነው፡፡ አንዲት እናት በእርግዝና ክትትል ወቅት የኤችአይቪ ቫይረስ በደምዋ ውስጥ ይኑር አይኑር ማረጋገጥ የሚገባት ሲሆን ቫይረሱ በደምዋ ከተገኘ የመከላከያ መድሀኒቱን መውሰድ አለባት ወይንስ መውሰድ አያስፈልጋትም የሚለው በህክምና ባለሙያ ይወሰናል፡፡ መድሀኒቱን መውሰድ ካለባት ግን ከእርግዝናው ፺28፻ሀያ ስምንተኛ ሳምንት ጀምሮ ልጁ እስኪወለድና ከተወለደም በሁዋላ እንደሁኔ ው እንድትወስድ ይደረጋል፡፡ የተወለደው ልጅም እንደአስፈላጊነቱ ከአንድ ሳምንት እስከ አራት ሳምንት ድረስ መድሀኒቱን እንዲወስድ ይሆናል፡፡በጡት ማጥባት ጊዜ ያለው ሁኔ  እናትየው በም ገኘው የምክር አገልግሎት የሚወሰን ይሆናል፡፡ እናትየው ሕጻኑ ስድስት ወር እስኪሞላው ድረስ የተዘጋጀ ወተት ልትመግበው የምትችል ከሆነ የጡት ወተት እንዳትሰጠው ወይንም ደግሞ በኢኮኖሚ አቋሟ የተዘጋጀ ወተት ልትሰጠው የማትችል ከሆነ የእናት ጡት ብቻ እንድትመግብ በባለሙያዎች ምክር ይሰጣ ል፡፡


የኤችአይቪ ቫይረስ በደማቸው ከሚገኝ እናቶች ከሚወለዱ አንድ መቶ ከሚያህሉ ህጻናት መ ከል ከስድሳ እስከ ስድሳ አምስት በመቶ የሚሆኑት ህጻናት ከኤችአይቪ ቫይረስ ነጻ ሆነው የሚወለዱ ሲሆን ወደ አርባ በመቶ የሚሆኑት ግን ከቫይረሱ ጋር ይወለዳሉ፡፡የ ፒኤምቲሲቲ ፺      ፻ ፕሮጀክት አላማ እነዚህ ከቫይረሱ ጋር የሚወለዱ ሕጻናትን ከቫይረሱ ነጻ እንዲሆኑና ወደዚህች አለም እንዲመጡ ማስቻል ነው፡፡ በዚህ ሂደትም እየዋለ እያደረ የኤችአይቪ ስርጭት እንደሚቀንስ እሙን ነው፡፡

********************************

<<ሕይወትን ለመስጠት... ሕይወት መጥፋት የለበትም >>
                                      ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ

 

፵በአለም አቀፍ ደረጃ ፺40ኀ፻ አርባ ከመቶ የሚሆኑ ሴቶች በእርግዝና በወሊድና ከወሊድ በሁዋላ የተለያዩ የጤና ችግሮች የሚደርስባቸው ሲሆን ከእነዚሀም እስከ አስራ አምስት በመቶ የሚሆኑት እስከ ሕይወት ዘመናቸው ፍጻሜ በተለይም የስነ ተዋልዶ ጤና አ ሎቻቸውን ለሚያሰቃያቸው የጤና መጉዋደል ይጋለጣሉ፡፡ በተለይም በ ዳጊ አገሮች ሴቶች በእርግዝና ወይንም በወሊድ ወቅት ሞት ወይንም የአ ል ጉድለት ሊገጥማቸው እንደሚችል በተደጋጋሚ የሚያጋጥም ነው፡፡ በተለያዩ ጥናቶች እንደተረጋገጠው በኢትዮጵያም ማንኛዋም ሴት በእርግዝና በወሊድ እና ከወሊድ ጊዜ በሁዋላ ባልተጠበቀ እና ከፍተኛ በሆነ የጤና መ ወክ ውስጥ የሚወድቁ ሲሆን ይህንን ለማስቀረት ተገቢው ጥረት ሊደረግ ይገባል፡፡፶
መረጃው የተገኘው በፌደራል ጤና ጥበቃ ሚኒስ ር ከወጣው በራሪ ጽሁፍ ነው፡፡ ይህ ወር ከጥር 1 እስከ ጥር 30 /2002 ድረስ የእናቶች ሞት እንዲቀንስና ጤናማ ሕይወትን ተላብሰው ዘር እንዲተኩ የሚለው ሀሳብ በጎላ መልኩ የሚንጻባርቅበት የተለያዩ እንቅስቃሴዎችም የሚደረግበት ነው፡፡
   የእናቶች ሞት በኢትዮጵያ ከአንድ መቶ ሺህ ፺100.000፻ ወደ ፺871፻ ስምንት መቶ ሳባ አንድ ያህል ሲሆን  ይህንን የሞት ቁጥር እስከ 2005 ዓ/ም ድረስ ወደ 673 ዝቅ ለማድረግ እቅድ ተነድፎአል፡፡ በዚህም እቅድ መሰረት የጤና ባለሙያዎችን በብቃት ማፍራት እንዲሁም የጤና ተቋማቱን ማስፋፋትና በበቂ ማደራጀት በመደረግ ላይ ካሉት ተግባራት መከከል ናቸው፡፡
በዚህ እትም ለንባብ የምንለው ለእናቶች ሞት ምክንያት ከሆኑት ውስጥ ከእርግዝና ጋር በተያያዘ የሚነሱ ጥያቄዎችንና የተሰጡ መልሶቻቸውን ነው፡፡ መረጃውን ያገኘነው ከኢን ር  2009 ሲሆን ጸሓፊው ፔኒ ሲምከን ናቸው፡፡ ፔኒ ስለእርግዝና ብቻም ሳይሆን ልጅን ስለመውለድና  ስለአዲሱም ልጅ የተለያዩ መረጃዎችን ለአንባቢዎች የሚሉ ናቸው ፡፡  

ጥ/1      እርጉዝ ከመሆኔ በፊት አልኮሆል በጣም እጠጣ ነበር፡፡ ይህ ነገር በእርግዝናው ላይ ችግር ያመጣ ይሆን ? ምን ማድረግስ አለብኝ?
ፔኒ/         አንዳንድ ሴቶች እርጉዝ ከመሆናቸው አስቀድሞም ብቻ ሳይሆን ማርገዛቸውን ካወቁም በሁዋላ መጠጥ ይጠጣሉ፡፡በእርግጥ አልኮሆል ጽንሱን ይጎዳል አይጎዳም የሚለውን አስቀድሞ መተንበይ ቢያስቸግርም ነገር ግን መጠኑ ከበዛና በተደጋጋሚ የሚወሰድ ከሆነ ጽንሱን ብቻም ሳይሆን እናትየውንም ሊጎዳ እንደሚችል አያጠራጥርም፡፡ ነገር ግን መጠጥን በተደጋጋሚ ሳይሆን አልፎ አልፎ እና መጠኑም አነስተኛ በሆነ ደረጃ የሚወሰድ ከሆነ የጎላ ችግር ላያስከትል ይችላል፡፡ በእርግዝና ጊዜ ጽንሱ በሆድ ውስጥ እንዳለ በመጠጥ ተጎድቶአል ወይንስ አልተጎዳም የሚለውን በውል ለመለየት ግን ማስቸገሩ አይቀርም፡፡ምናልባትም የልብ ምት አለመስተከከል እንዲሁም የእድገቱ ሁኔ  ካልተስተከከለ እና የመሳሰሉት ሁኔ ዎች በምርመራ ከተገኙ እናትየው ከምትወስደው መጠጥ ጋር የተያያዘ ነው ሊያሰኝ ይችላል፡፡ እዚህ ላይ ግን ሁሉም የተረገዙ ሕጻናት ከእናቶቻቸው አልኮሆልን ይወስዳሉ ማለት አይቻልም፡፡ ለማንኛውም ገደብ የሌለው አጠጣጥን ማስወገድ ተገቢ ነው፡፡
ጥ/2         ጭንቀት በእርግዝና ወቅት ምን ጉዳት ያስከትላል ?
ፔኒ/         ጭንቀት በእርግዝና ወቅት ብቻ ሳይሆን በማንኛውም ወቅት ለጤና አስቸጋሪ ነው፡፡ ለማንኛውም ጭንቀት የሚያስከትለውን ችግር ከመመልከ ችን በፊት ጭንቀት በምን ምክንያት ይፈጠራል የሚለውን ማሰብ ተገቢ ነው፡፡ ጭንቀት በእርግዝናም ወቅት ሆነ በማንኛውም ጊዜ ከተለያዩ ቤተሰባዊ ወይንም ከጉዋደኛና እና ከግል ሁኔ  ጋር በተያያዘ ሊከሰት ይችላል ፡፡
               በቤተሰብ ወይንም በጉዋደኛ አለዚያም በግል ሕይወት ላይ የሚደርሱ ከፍተኛ ለውጦች ማለትም ሞት ወይንም ከፍተኛ ሕመም እንዲሁም በተለያዩ ምክንያቶች የሚደርሱ መፈናቀሎች አለዚያም የንብረት ማጣት ሁኔ  የገቢ መቀነስ የመሳሰሉት ሁሉ ለጭንቀት ይዳርጋሉ፡፡ እርግዝናው በራሱም አንዳንዴ ጭንቀት የሚፈጥርበት ሁኔ  ያጋጥማል፡፡ ጭንቀት የሚበዛ ከሆነ ጭንቀትን የሚያባብሱ እጢዎችን በሰውነት ውስጥ በብዛት ስለሚፈጥር የጤና ችግር ያስከትላል፡፡
               ጭንቀት ምን ያስከትላል የሚለውን ስንመለከት በተለይም እርጉዝ ሴቶች እንደ ድብርት፣ ፍርሀት ፣ሀዘን ወይንም ቁጣና ንጭንጭ የመሳሰሉትን ስሜቶች ሊፈጥሩባቸው ይችላል፡፡ እነዚህ ስሜቶች ደግሞ ለስነልቡና ቀውስ ያጋልጡዋቸዋል፡፡ ከዚህ ሁኔ  የሚከተለው እርጉዝዋ ሴት ለተለያዩ ሕመሞች መጋለጧ ነው፡፡ ለምሳሌ እንደ ደም ግፊት የመሳሰሉ ሕመሞች ከመፈጠራቸውም በላይ የተረገዘው ልጅም እድገቱ እንዲቀጭጭ መጠኑ ትንሽ እንዲሆን አስተዋጽኦ ያደርጋል፡፡
               ስለዚህ በእርግዝና ጊዜ የሚከሰተውን ጭንቀት ለማስወገድ አንዳንድ የሚያስደስቱ ፕሮግራሞችን መፍጠር ሰውነት የሚዝናኑበትን እስፖር ዊ ፕሮግራም መንደፍ ያስፈልጋል፡፡ከዚህ ባለፈም ከሕክምና ባለሙያዎች ጋር መመ ከር ጠቃሚ ነው፡፡ ጭንቀት ላለባቸው ሴቶች የምክር አገልግሎት በተለይም በሚቀርቡትና በሚወዱት ሰው ቢሰጥ መፍትሔው የጎላ ነው፡፡ የምክር አገልግሎቱ እርጉዘዋ ሴት ጭንቀትዋን እንዴት እንደም ስወግድ እና ለተፈጠረው ጭንቀትም ተገቢውን ምላሽ እንድትሰጥ ያስችላ ል፡፡
               ከዚህ ጋር በተያያዘ ግን አንድ የማይ ለፍ ነገር አለ፡፡ እርጉዝ ሴቶች ጭንቀት ሲገጥማቸው ብዙውን ጊዜ ጽንሱን ሲያማርሩ ይስተዋላሉ፡፡ ይህ ግን በጣም ስህተት ነው፡፡ ለተከሰተው ጭንቀት የተረገዘው ልጅ በምክንያትነት የሚገለጽ ከሆነ በሚወለድ ጊዜም ተንከባክቦ ለማሳደግ የባህርይ ችግር ጋጥማል፡፡ የተረገዘው ልጅ ከተፈጠረው ጭንቀት ጋር ምንም ተያያዥነት ስለሌለው ልጁን በተገቢው መንገድ ለመቀበልና ተንከባክቦ ለማሳደግ ዝግጁ መሆንን ይጠይቃል፡፡

ጥ/3      በእርግዝና ወቅት ሊወሰዱ የሚገባቸው ቫይ ሚኖች ምንድናቸው?
ፔኒ/            ለአንዲት እርጉዝ የሆነች ሴት ጥሩ የሆነ የቫይ ሚን ምንጭ ነው የሚባለው የተመጣጠነ ምግብ ማግኘት ነው፡፡ ይህም ማለት ከአዝርእት ፣ከጥራጥሬ ፣ከአትክልት፣ ከፍራፍሬ እንዲሁም ከእንስሳት ውጤቶች ማለትም ከወተት ፺ስጋ ፣አሳ፣ ዶሮ፣ እንቁላል፻ ከመሳሰሉት እንደ ባቄላ ፣ኦቾሎኒ እና ቅባት በተጨማሪም ጣፋጭ ምግቦችን በተመጣጠነ መልኩ መውሰድ ይገባል፡፡ ከዚህ ውጪ ግን በአንዳንድ የጤና ሁኔ ዎች በሕክምና ባለሙያዎች አማ ኝነት የሚመከሩ የምግብ አይነቶች ሊወሰዱ ይችላሉ፡፡ ለእርጉዝ ሴቶች ከምግብም በተጨማሪ እንደ ልሲየም ፣አይረን የመሳሰሉ ተጨማሪ ድጋፍ የሚያደርጉ መድሀኒቶች ሊ ዘዙም ይችላሉ፡፡
               ከላይ ከተገለጸው ውጪ ማንኛቸውንም የቫይ ሚን መድሀኒቶች ያለ ሐኪም ምክርና ፈቃድ መውሰድ ወይንም ምግቦችን ከተገቢው በላይ መመገብ ተገቢ አይደለም፡፡ ቫይ ሚኖች አለአግባብ ከተወሰዱ ባልተወለደው ልጅ ላይ ችግር እንደሚያስከትሉ መ ወቅ አለበት፡፡ ቫይ ሚኖች እንደ መድሀኒትም ሊያገለግሉ ስለሚችሉ ጥንቃቄ ሊደረግባቸው ያስፈልጋል፡፡
ጥ/4         በእርግዝና ጊዜ ጽንሱ እስከ ምን ያህል ኪሎ ቢጨምር ትክክል ነው?
ፔኒ/         በቅድሚያ እርጉዝዋ ሴት የተመጣጠነ ክብደት ሊኖራት ይገባል፡፡ ከዚያ በሁዋላ ግን በእርግዝናው ጊዜ ጽንሱን ለመርዳት ሲል ሰውነት የሚያደርገው ዝግጅት ስላለ መጠነኛ የክብደት ለውጥ ሊኖር ይችላል፡፡ ከዚያ በተረፈ ግን የተረገዘው ልጅ ከ6-9 ፓውንድ እንግዴ ልጁ ከ1-2 ፓውንድ ማህጽን 2 ፓውንድ የሽርት ውሀ ከ2-3 ፓውንድ ተጨማሪ የጡት ክብደት ከ1-2 ፓውንድ ተጨማሪ የደም መጠን ከ2-3 ፓውንድ ተጨማሪ በሰውነት ውስጥ የሚኖር ፈሳሽ ከ4-6 ፓውንድ ስብ ከ5-8 ፓውንድ በድምሩ ከ23-25 ፓውንድ ድረስ በእርግዝናው ምክንያት ክብደት ሊጨምር ይችላል፡፡         
ጥ/5         በእርግዝና ጊዜ ሰውነትን የመ ሸት (Massage)  ማሳጅ አገልግሎት መውሰድ ጠቃሚ ነውን ?
ፔኒ/         በእርግዝና ጊዜ (Massage) ገላን መ ሸት፻  ማሳጅ መውሰድ በእርግጥ ጠቃሚ ነው፡፡ ነገር ግን እርጉዝዋ ሴት ሰውነቷን ለመ ሸት የምትሄደው  በዚህ ስራ በተለይም እርጉዝ ሴቶችን በተመለከተ የሚሰጠውን አገልግሎት በሚመለከት በትክክለኛው መንገድ ልዩ ስልጠና ያገኙ ባለሙያዎችጋ ካልሆነ በስተቀር ማንኛውም ሰው ገላን ለመ ሸት በሚገለገልበት ቦ  መሆን የለበትም፡፡ ለእርጉዝ ሴቶች የማሳጅ አገልግሎት የሚሰጠው በእርግዝናው ጊዜ ያላቸውን የሰውነት ለውጥ በመከ ተል የደም ስር ሁኔ ዎችን ሁሉ ባገናዘበ መልኩ መሆን አለበት፡፡ ለምሳሌ በጀርባ ማስተኛት በሆድ ማስተኛት እንዲሁም የጡት መጠን ከፍ ማለት የሰውነት ማበጥ የመሳሰሉት ሁሉ ልዩ ጥንቃቄን የሚሹና መደረግ የሚገባውነቀ የማይገባው በደንብ ተለይቶ እንዲ ወቅ ስለሚያስፈልግ በዚህ መስክ ከሰለጠኑ ባለሙያዎች አገልግሎቱን ማግኘት ተገቢ ነው፡፡ የሰውነት መ ሻው አልጋም የእርጉዝ ሴቶችን ሁኔ  ከግምት ያስገባና ምቹ መሆን ይጠበቅበ ል፡፡

***************************************************************

ጤናማ እናትነት ...

                                                ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ

በኢትዮጵያ የእናቶችን ሞት ከሌሎች አገሮች ጋር በተለይም ከሰሀራ በ ች ካሉት አገራት ጋር ሲነጻጸር በከፍተኛ ደረጃ ልዩነት ያሳያል፡፡ ለእናቶች ሞት በምክንያትነት የሚጠቀሱት ደግሞ በቀጥ ፣ በተዘዋዋሪ መንገድ እና ለሞት ምቹ ሁኔ ን የሚፈጥሩ ተብለው ይለያሉ፡፡ በቀጥ  ለሞት የሚዳርጉ የሚባሉት በወሊድ ወቅት ከምጥ ጋር በተያያዘ የሚከሰቱ የማህጽን መመረዝ ፣መሸርከት ፣በወሊድ ወቅት መድማት የመሳሰሉት ሲሆኑ በዚህ ምክንያት የሚሞቱት ሴቶች በጠቅላላው ከሚሞቱት እናቶች 85% ሰማንያ አምስት በመቶ የሚሆኑት ናቸው፡፡
በተዘዋዋሪ መንገድ የእናቶችን ሞት ያስከትላሉ የሚባሉት ደግሞ በእርግዝና ወቅት የሚያጋጥሙ እንደ ወባ ፣የሳምባ ምች ፣ሄፒ ይተስ፺ከጉበት ጋር በተያያዘ ማለት ነው፻ኤችአይቪ ኤይድስ ፣የተመጣጠነ ምግብ እጦት፣ የሳንባ ነቀርሳ ...ወዘተ ሲሆኑ እነዚህ የጤና ችግሮች በእርግዝና ላይ ላሉም ሆነ ለወለዱ እናቶች ሞት ምክንያት ይሆናሉ፡፡
ወደጤና ማጣት ከሚገፋፉ ወይንም ለሞት ምቹ ሁኔ ን ከሚፈጥሩ መከከል ደግሞ ሴቶች የሚኖሩት በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ መሆኑ ወይንም ከአቅማቸው በላይ በሆነ የስራ ዘርፍ ላይ ከተሰማሩ እንዲሁም ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች የተፈጸመባቸው ከሆነ እና በአመጋገብ ደረጃም ያልተመጣጠነ ምግብ የሚያገኙ ከሆነ ለሞት ሊዳረጉ ይችላሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ብዙ ልጆችን መውለድ እና ባልተራረቀ የጊዜ ሁኔ  ልጅን መውለድ እንዲሁም ለእርጉዝና ወላድ ሴቶች ተገቢው የጤና ክትትል አለመኖሩ የእናቶችን ሞት ቁጥሩን እንደሚያበዛው በተለያዩ ጥናቶች ተረጋግጦአል፡፡ ስለዚህ የእናቶችን ሞት ለመቀነስ ሁሉ አቀፍ እርምጃ መውሰድ እንደሚያሻ ነው የተረጋገጠው፡፡
የእናቶችን ጤናማ ሕይወት ማረጋገጥን በተመለከተ የኢትዮጵያ ማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር ኢሶግ ከጤና ጥበቃ ሚኒስ ር ጋር በመተባር ጥር 21/2002 በተለያየ የሙያ ዘርፍ የተደራጁ ማህበራትን ለውይይት በመጋበዝ የእናቶችን ሞት ከመቀነስ አንጻር ውይይት አድርጎአል፡፡ በዚህም ወቅት ከተነሳው ጉዳይ አንዱ የእናቶች ጤናን በሚመለከት የተደነገጉ ሕጎችን የሚመለከት ነው፡፡
የእናቶችን ጤናን በተመለከተ የሰብአዊ መብት ህግ አስተሳሰብ መሰረት ተደርጎ የሚቆጠረው ከሁለተኛው የአለም ጦርነት ወዲህ አለም አቀፍ ስምምነት የተደረሰበት የመጀመሪያው የሰብአዊ መብት ህግ የዩኤን ቻርተር ነው፡፡ ከዚያ ወዲህ በእርግጥ ሌሎች አለምአቀፍ ስምምነቶች ተፈርመዋል፡፡ ከእነዚህም አንዱ የአለምአቀፍ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች ሲሆን በዚህም የሰዎች የመኖር መብት ተረጋግጦአል ፡፡ በሕይወት የመኖር መብት ጽንሰ ሀሳቡ አወዛጋቢ ስለነበር ሀገሮች እንደገና ሁለተኛውን ስምምነት እንዲፈርሙ ተደረጎ አለምአቀፉ ኢኮኖሚያዊ ማህበራዊና ባህላዊ መብት ፡፡ (                                                                     )  ወጥቶአል፡፡ በዚህ ስምምነት ውስጥ የሰፈረው አንዱ መሰረ ዊ መብት የጤና መብት ነው ፡፡ የጤና መብትን በተመለከተ የመንግስት ግዴ  ምንድነው የሚለውን በተለያዩ ጊዜያት አገሮች እየቀየሱ በየጊዜው የተለያዩ ሪፖርቶች ለተባበሩት መንግስ ት ይቀርባል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት የእናቶችን ጤና ከማረጋገጥ አኩዋያ አሁን እየተገበረ ያለው ይህንን አለምአቀፍ መብት መሰረት ያደረገ ብሔራዊ ህግ ስላወጣ ነው፡፡  የእናቶች ጤና ትኩረት የሚደረግበት እናቶች ካላቸው ለአደጋ የመጋለጥ ሁኔ  ነው፡፡ ስለእናቶች ጤና ሲወራ መሰረ ዊ መብቶቹ በህይወት የመኖር መብትና ጤናማ ሕይወት የመኖር መብቶች መሰረ ዊ መብቶቹ ናቸው፡፡
ኢትዮጵያ አለም አቀፍ ሕጎችን ፈራሚ በመሆኑዋ አለም አቀፉ የሰብአዊ መብትና ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊና ባህላዊ ሁኔ ዎችን የሚመለከቱት ነጥቦች በህገ መንግስቱ እንዲ ተቱ ተደርገዋል፡፡ በህገመንግስቱ የመኖር መብት በአንቀጽ 15 የጋብቻና የቤተሰብ መብት አንቀጽ 31 ላይ ተ ትቶአል፡፡ ከእናቶች መብት አንዱ ያለእድሜ ጋብቻን የሚመለከት ነው፡፡ የጋብቻ ሁኔ  የሚፈቀድበት እድሜ በብሔራዊ ደረጃ አስራ ስምንት አመት ሲሆን  በእርግጥ በክልል መስተዳድሮች የሚለይበት ሁኔ  ሊኖር ይችላል፡፡ ነገር ግን ጋብቻ ከአስራ ስምንት አመት በ ች አይፈጸምም የሚለው ምክንያቱ የአእምሮ መጎልበት ወይንም የኑሮ ብልሀትን ከማወቅ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ ከአስራ ስምንት አመት በ ች የሆኑ ልጆች ለትዳር መምራት የሚያስፈልገውን ብልሀትና አቅም ስለማይኖራቸውና እንዲሁም ከጤና ጋር በተያያዘ በልጅነት እድሜ እርግዝናና መውለድ ስለሚከሰት በአስቸጋሪ ሁኔ  ውስጥ ስለሚወድቁና ለሞት ሊዳረጉም ስለሚችሉ ነው፡፡
ሌላው በአለም አቀፍም ይሁን በአገር አቀፍ ደረጃ የወጡ ድንጋጌዎች ጤናማ እናትነትን በሚመለከት የደነገጉት የስራ ሁኔ ን የሚመለከት ነው፡፡ አለም አቀፉን ስምምነት መሰረት ያደረገው ፺    ) እናቶች ከእናትነት ጋር በተገናኝ እንክብ ቤ እንደሚያስፈልጋቸው ይገልጻል፡፡ ይኼውም እናቶች ከወሊድ በፊትና ከወሊድ በሁዋላ ፈቃድ ማግኘት አለባቸው የሚለው ይገኝበ ል ፡፡ በተጨማሪም አገሮች የእናቶችን የስራ መብት በማክበሩ ረገድ በኢኮኖሚው እድገ ቸውና ፖለቲ ዊ ፈቃደኝነ ቸውን ሊያሳዩ በሚችሉበት መንገድ መብቶችን በተሻለ ሊያስከብሩ የሚችሉበትን እርምጃ የመውሰድ ግዴ  እንዳለባቸውም ይገልጻል ፡፡ አሰሪዎች ለእናትየው ፈቃድ እንዲሰጡ የሚፈለግበት ምክንያት ለሚወለደው ሕጻን እና ለምትወልደው እናት መብት ለማክበርና ጤና ለመጠበቅ ሲባል ነው ፡፡ የእናትየውንም ሆነ የህጻኑን መብት በሚመለከት ቀጣዩ እረፍት የሚያስፈልገው የማጥባትን  መብት የሚመለከት ነው ፡፡ የእናትየውን ጤና ከመጠበቅ አገር በአደጉ አገሮች ለአባትየውም ፈቃድ የሚሰጥበት ሁኔ  በመብት ተደንግጎ ይገኛል፡፡ አባትየውም የሚያገኘው እረፍት አለው፡፡ የእናቶችን ጤና በመጠበቁ ረገድ ሌላው ህግ ሴቶች በጣም አደገኛ በሆኑ የስራ መስኮች ወይንም በምሽት፣ ወይንም በእረፍት ቀናት ስራ መስራት አይገባቸውም የሚል ነው ፡፡
ወደኢትዮጵያ ሲመጣ ያሉት ህጎች አንዱ የሰራተኞች መብት ሲሆን ሌላው ደግሞ የሲቪል ሰርቪስ  ህግ ነው፡፡ በእነዚህ ህጎች ከእናቶች መብት ጋር የተያያዘው አንዱ ለህክምና ምርመራ የሚሰጥ ፈቃድ ሲሆን ይሔም ያለክፍያ ሳይሆን በክፍያ እንዲሰጥ ነው ህጉ የሚደነግገው፡፡ ይህንን ህግ ከመተግበር አኩዋያ ግን በአገራችን የተዘበራረቀ ሁኔ  ይ ያል፡፡ የመንግስት የልማት ድርጅቶችና የሲቪል ሰርቪሱ መስሪያ ቤቶች ይህንን መብት ሲያከብሩ በግል የስራ ተቋማት ግን ብዙውን ጊዜ ሲተገበር አይ ይም፡  በግል መስሪያ ቤቶች ባሉ የስራ ቅጥሮች የወሊድ ፈቃድ ከክፍያ ጋር ካለመሰጠቱም በላይ አንዳንዴ ሰራተኛዋ እርጉዝ መሆንዋ ከ ወቀ የቅጥር ሂደቱ  እንዲቋረጥ የሚሆንበት አጋጣሚ ይስተዋላል፡፡ ለምትወልደው እናት ፈቃድ ቢሰጥ እንንኩዋን ከክፍያ ነጻ ነው፡፡ ይህ አሰራር ግን የእናቶችን ጤናማነት የሚጋፋ ነው፡፡
      ፺    ) አለም አቀፉ የሰራተኞች ህግ እናቶች በምሽት፤ከባድ መሳሪያዎችን በማንቀሳቀስ፤ በቁም የሚሰሩ ስራዎችን ፤በማእድን ቦ ዎች ላይ ሴቶች እንዲሰሩ አይፈቀድም፡፡ እንደዚህ ያሉ የስራ ባህርይዎች አደገኛ ሲባሉ ነገር ግን አደገኛ የስራ ሁኔ ዎች የሚባሉት የትኞቹ ናቸው ሲባል የአገራችን አሰሪና ሰራተኛ ሕጋችን አይለየውም፡፡
 የእናቶችን ጤና ከመጠበቁ አንጻር ተጠቃሽ የሚሆነው ሌላው የወንጀል ህግ ነው፡፡ የወንጀል ህጉ እናቶች እንደማንኛውም ሰው ወንጀል ሲፈጸምባቸው የሚሰጣቸወ ዳኝነት እንዳለ ሆኖ በተለይ ግን ለምሳሌ ከማስወረድ ጋር በተገናኝ የተደነገገው እንደተጨማሪ የእናቶችን ደህንነት መጠበቂያ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ሞራልን ለመጠበቅ የሚረዳ አንቀጽ አለ፡፡ ለምሳሌ በቤተሰብ መ ከል የተፈጸመ እርግዝና ካለ ውርጃ እንዳ ሄድ የመፍቀድ ሁኔ  ያለ ሲሆን እንዲሁም ከእናትየው ጤና ጋር በተያያዘም አደጋ የሚያስከትል ከሆነ ውርጃ ይፈቀዳል፡፡ በወንጀል ህጉ የተደነገገወ ይህ ብቻም ሳይሆን ለምሳሌ ጎጅነት ያለው የህክምና አገልግሎት መስጠት ፣ሕክምናው በሚሰጥበት ወቅት   ሚዋ ብትሞት፣ ለእናትየውም ሆነ ለጽንሱ አደጋ ለያስከትሉ በሚችሉ ፣በቸልተኝነት፣ ጤናን በሚጎዳ መልክ ሕክምናው ቢሰጥ ፣መድሀኒት ቢ ዘዝ በመሳሰሉት ሁሉ ሓላፊነትን የሚመለከቱ  አንቀጾች አሉ፡፡  
የእናቶችን ጤናማ ህይወት በመጠበቁ ረገድ ወይንም ሞትን ለመቀበስ እንዲቻል የወጡ ሕጎችን ለማስፈጸም የሚረዱ ፺                  ) ናቸው፡፡ ይህም አንድን የጤና ዘርፍ በተመለከተ የህክምና ደረጃውን ለይቶ ማስቀመጥ ፣የህክምና ባለሙያው  የእውቀት ደረጃ ፣የህክምናው አይነት ምን መሆን አለበት የሚለውን ከመወሰን አቅጣጫ የማስፈጸሚያ ህጎችቸ ደንቦችና መመሪያዎች ሊኖሩ ይገባል፡፡   
የእናቶችን ጤና ከመጠበቅ አንጸር የህክምና ፈቃድ አሰጣጥ ሁኔ  ትኩረትን የሚሻ ነው፡፡ ይሔውም ፈቃዱ በሚሰጥበት ጊዜ የቱ ባለሙያ በምን የእውቀት ደረጃ መስራት አለበት የሚለውን ለመለየት ይረዳል፡፡
የእናቶችን ጤናማነት እና በህይወት መኖር እውን ለማድረግ አስፈላጊ ከሚባሉት ውስጥ  ስነስርአትን ማስከበር ወይንም ተጠያቂነትን ማስፈን አንዱ ነው፡፡ ይኼውም የጤና ተቋሙን እስከመዝጋት ባለሙያውን በተገቢው ተጠያቂ እስከማድረግ ፈቃድን እስከመሰረዝ ወይንም እገዳ እስከመጣል የሚያደርስ የህግ እርምጃ ነው፡፡ ሙያዊ ብቃትን መከ ልና በዛው መሰረት ደግሞ ሕክምናው መሰጠቱን መቆጣጠርና ካልተሰጠ ደግሞ ሕጋዊ እርምጃዎችን መውሰድ የመሳሰሉት አንዱ የማስፈጸሚያ ሕጎቸ አ ሄድ ነው፡፡ በእርግጥ ከዚህ ጋር በተያያዘ ሌሎች ህጎችም ተፈጻሚ ይሆናሉ፡፡ ለምሳሌ በቸልተኝነት ወይንም የህክምና ሙያውን መሰረት አድርጎ አንድ የህክምና ባለሙያ አንዲትን እናት እንድትሞት ቢያደርግ በወንጀል ህጉም ተጠያቂ ሊሆን ይችላል ፡፡  

 *****************************************************************************

... ለራሴ ጠፍቼ ...ደሞ ልጄ ትጥፋ?

                                          ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ

፵ለላንቺና ላንተ የጋዜጣ አምድ...

እኔ ይህንን ጽሁፍ ለመጻፍ ያነሳሳኝ ሰሞኑን ሲነገር የከረመው የእናቶቸ ሞት ጉዳይ አነሳስቶኝ ነው፡፡ እኔ በተለይ ባደግሁበት አከባቢ ማለትም በአማራ ክልላዊ መስተዳድር ይልማና ደንሳ ወረዳ አከባቢ ማለት ነው... ሴቶች የምንዳረው ገና ጡት ጠብተን ሳንጨርስ በሚያሰኝ እድሜ ባለንበት እስከ አስራ ሁለት አስራ ሶስት አመት እድሜ ባለንበት ነበር፡፡ እኔ አሁን እድሜዬ ገና ሰላሳ አምስት አመት ሲሆን ግን የአስራ ስምንት አመት ጎረምሳ ልጅ አለኝ፡፡ ከዚያም በ ች ሁለት ልጆች አንድ ወንድና አንዲት ሴት አሉኝ፡፡ ነገር ግን ልጆቹን ከማርገዝና ከመውለድ በስተቀር እኔ ሰውየውን የማፍቀር ነገር ምንም አልነበረኝም፡፡ በየቀኑ ከባለቤ  ጋር ጭቅጭቅ ሆነ፡፡

በዚያ ላይ እናትየው ምንም አ ውቂም ገልቱ ነሽ ይሉኛል፡፡ የእኔን ሕጻናነት ምንም አልተረዱትም፡፡ በቃ ኑሮዬ ፈተና ሲሆንብኝ እኔም ሁሉንም ልጆቼን እና  ላይ ጥዬ ወደ አዲስ አበባ ከአንዲት ጉዋደኛዬ ጋር መጣሁ፡፡ ልጆቼ እናት ሳያውቁ በአያት እጅ ነው ያደጉት፡፡ ያው ዛሬ ወንዶቹ ሁሉም ገበሬዎች ናቸው፡፡ አሁን ግን ወደእናንተ ለመጻፍ ያበቃኝ ይህች ሴቷ ልጄ እድሜዋ ገና አስራ አራት አመት ሲሆን ከፊ ችን ፋሰ  ትዳራለችና ለሰርግ የሚሆን አንዳንድ ነገር እርጂን ብለው ቤተሰቦቼ ይልኩብኛል፡፡ እኔ አሁን የጨነቀኝ እኔ ትቼው የመጣሁትን ያንን የልጅነት ትዳር ለእሱዋ ሲያመቻቹ እኔም ተባባሪ ልሆን ነው ማለት ነው፡፡ እንደገና ደግሞ እሱዋ በትምህርቷ ወደ ሰባተኛ ክፍል የደረሰች ልጅ ስትሆን አሁን ሲድሩዋት ግን ትምህርቱዋንም ል ቋርጥ መሆኑ ቆጨኝ፡፡ ዝምብዬ አስኮብልዬ እንዳላመጣት እኔም የምኖር ከሰው ቤት ወጥ ቤት ሆኜ ነው፡፡ በአዲስ አበባ ኑሮም ምን ያህል ችግር እንዳሳለፍኩ እኔ ነኝ የማውቀው፡፡እንዲያው እናንተዬ ምንትሉኛላችሁ ?ዛሬ እንዲህ ያለው ስህተት እንዳይሰራ የሚደረግበት መንገድ የለም እንዴ ? ለራሴ ጠፍቼ ደሞ ልጄ ትጥፋ? ምን ትመክሩኛላችሁ? ፶
-------------------------------------////------------------------------------------
ይህ ጽሁፍ ከደረሰን ወደ አንድ ሳምንት ይሆነዋል፡፡ ያለእድሜ ጋብቻ ለሴቶች በብዙ አቅጣጫ የሚጎዳ በመሆኑም በጎጂ ልማዳዊ ድርጊትነት ተፈርጆአል፡፡ ነገር ግን በአንዳንድ አከባቢዎች ዛሬም የሚፈጸም መሆኑን የተለያዩ ጥናቶች ያስረዳሉ፡፡ይሁን እንጂ በተለያዩ አ ባቢዎች ሴት ልጆቹ እራሳቸው በትምህርት ቤቶቻቸው እና በአቅራቢያቸው ባሉ የህግ ተቋማት እንዲሁም ወደሴቶች ማህበራት እየሄዱ ያለእድሜያችን ትዳር መስርቱ ተብለናል እያሉ በማመልት ያለእድሜያቸው እንዳይዳሩ የሚደረግበት ሁኔ ም እንዳለ ለማስ ወስ እንወዳለን፡፡ አመል   በጠቀሱት አ ባቢ የሚፈጸመውን ያለእድሜ ጋብቻ በተመለከተ የተደረገ ጥናትን በዚሁ አጋጣሚ ልናስነብባችሁ ወደድን፡፡  
ጋብቻና የወሲብ አፈጻጸም በወጣትነት እድሜ በኢትዮጵያ በተለይም በአማራ ክልላዊ መስተዳድር በምእራብ ጎጃም ዞን በምን ሁኔ  ላይ እንዳለ የሚገልጸው ይህ ጥናት በአናቤል እሩልንር ፣ተክለአብ መክብብ ፣ሄለን አምደሚከኤል እና ጋሪ ኮናይል አማንኝነት በኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር በሚ ተመው                                          ) ለንባብ ቀርቦአል ፡፡
በኢትዮጵያ ጋብቻ በልጅነት እድሜ ከሚፈጸምባቸው አከባቢዎች የአማራ ክልላዊ መስተዳድር በብዛት ሲሆን ወደ 46% የሚሆነው ጋብቻ ሴቶቹ የአስራአምስት አመት እድሜ ክልል ሲደርሱ ሲሆን ከዚህ በተረፈ ግን ሴቶቹ በአስራ ስምንት አመ ቸው የግድ ወደትዳሩ አለም እንዲገቡ የሚደረግ መሆኑን ጥናቶች ይጠቁማሉ፡፡
በእነዚህ አ ባቢዎች ጋብቻ የሚመቻቸው በቤተሰብ ስምምነት እንጂ በተጋቢዎቹ ፍላጎት አለመሆኑን ነው ለመረዳት የሚቻለው፡፡በተደረገው ጥናት እንደ የው ምናልባት ምክክር እንኩዋን ይደረጋል ቢባል ከሙሽራው ጋር አንደሆነ ነው እንጂ ከምት ጨው ልጅ ጋር ምንም አይነት ምክክር እንደማይደረግና አግቢ የተባለችውን የማ ውቀውን ሰው ያለምንም ተቃውሞ እንድ ገባ ይደረጋል፡፡የጋብቻውን እድሜ በሚመለከት ከ10-19 ከአስር እስከ አስራ ዘጠኝ አመት አድሜ ካሉት ውስጥ በአማ ይ በ17 አመት እድሜያቸው ጋብቻን የሚመሰርቱ ቢሆንም ይህ እድሜም ገና ከህጻንነት ክልል ያልወጣ እና የትምህርት እድሜ መሆኑ አያጠያይቅም ፡፡ ቤተሰቦች በባህላዊው መንገድ ወንድ ልጆቻቸው ማንን ወይንም የማንን ዘር እንዲሁም በየትኛው እድሜ ማግባት እንዳለባቸው ይወስናሉ፡፡ ይህም የሚያሳየው በባህሉ የጋብቻ ምርጫና ውሳኔ የሚሰጠው ለወላጆች መሆኑን እና ወላጆች ልጅን ለጋብቻ ማድረሳቸው እንደ አንድ የኢኮኖሚ ማገዣ እና እንደ ማህበራዊ ዋስትና ከመቆጠሩም ባሻገር ለልጃቸው የፈለጉትን ሰው ዘር መርጠው መዳራቸው እንደ አንዱ የህይወት ስ ት የሚቆጠር ነው፡፡

አብዛኞቹ ልጃገረዶች ከጋብቻ በፊት የወሲብ ግንኙነት አድርገው የማያውቁ ሲሆን በሌላ በኩል ግን በህብረተሰቡ ልማድ መሰረት በልጅነት ወደጋብቻ እንዲሄዱ በመገደዳቸው ወሲብን በልጅነት ይፈጽማሉ፡፡ በቅርቡ በተደረገ አንድ ጥናት እንደሚ የው በልጅነት ጋብቻ የፈጸሙ ልጆች ወደ ትዳሩ አለም ሲቀላቀሉ ግን ትዳር ናልያዙት ነገር ግን ወሲብ ከሚፈጽሙት ጉዋደኞቻቸው ይበልጥ ማለትም በ፺50ኀ፻ ለኤች አይ ቪ ኢንፌክሽን

መጋለጣቸው ጨምሮ ነው የ የው፡፡ በትዳሩ አለም የገቡት  ዳጊዎች እንቅስቀሴያቸው ወይንም ከሌሎች ሰዎች ጋር የሚኖራቸው ግንኙነት በትዳር ጉዋደኞቻቸው ወይንም ቤተሰቦቻቸው ጥበቃ የሚደረግለት ወይንም የተገደበ እንደሚሆን እሙን ቢሆንም  ዳጊዎቹ ግን በትዳር ጉዋደኞቻቸው አማ ኝነትም ይሁን በሌላ ተያያዥ በሆነ ምክንያት ለበሽ ው ይበልጥ የተጋለጡ መሆኑን ነው ሁኔ ው የሚያሳየው፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ የሚ የው እውነ  በልጅነት የተዳሩት ልጆች ወደጋብቻ ማፍረሱ የመሄድ እድላቸውም ከፍተኛ መሆኑን ነው፡፡ በተደረገው ጥናት እንደ የው በእድሜያቸው ከ15-24 ከሚሆኑት ያገቡ ሴቶች መከከል አስራ ሁለት ከመቶው ፺12%) ጋብቻቸውን አፍርሰዋል፡፡ በእርግጥ ጋብቻቸውን በማፍረስ ወደተለያዩ ከተሞች ፈልሰው የገቡ ሴቶችም ሁኔ  ሲ ይ በአብዛኛው በገጠሩ አከባቢ በትዳሩ አለም የሚፈጠረውን ችግር ለመፍ ት ከመቸገር የተነሳ የወሰዱት እርምጃ መሆኑን የተለያዩ መረጃዎች ይጠቁማሉ ፡፡የጋብቻ መፍረስ በአብዛኛው የልጅነት ጋብቻ ወይንም ያልተፈለገና ያል ቀደ ጋብቻ ውጤት አንደሆነ ብዙ መረጃዎች ያረጋግጣሉ፡፡
በልጅነት ጋብቻ በሚፈጸምባቸው አከባቢዎች ያሉ ሴቶች ከጋብቻው ጋር በተያያዘ በሚፈጠሩ እንደፌስቱላ ያሉ ሕመሞች እና ሌሎች የስነተዋልዶ ጤና አከላት መጎዳት ጋር በተያያዘ ለከፍተኛ ሞትና አ ል መጎዳት ይዳረጋሉ፡፡ የልጅነት ጋብቻ በሚፈጸምባቸው አ ባቢዎች ያሉ ሴት  ዳጊዎች ትምህር ቸውን እንዲያቋርጡ ስለሚገደዱና በእነሱ ፈቃደኘነት ላይ በተመሰረተ መልኩ ሳይሆን በቤተሰብ ውሳኔ ወደትዳሩ አለም እንዲገቡ ከመገደዳቸውም በላይ በአገቡ አመት ባልሞላው ጊዜ ልጅ እንዲወልዱም በህብረተሰቡ በጉጉት ይጠበቃል፡፡ እነዚህ በልጅነት ጋብቻ ምክንያት ቤት የማስተዳደር  ላፊነትን የተረከቡት ሴት  ዳጊዎች ትዳሩን ለማስተዳደር አቅም የሌላቸው ከመሆኑም በላይ ልጃቸውን በተገቢው ተንከባክበው ሊያሳድጉ በማይችሉበት እድሜያቸው ልጅ እንዲወልዱ መፈለጉ በወሊድ ወቅት ከሚደርስባቸው የጤና መ ወክ ባሻገር በወለዱት ልጅ አስተዳደግም ላይ ችግር እንደሚያስከትል እሙን ነው፡፡
 ጋብቻ በልጅነት እድሜ እንዳይፈጸም ማድረግ ሴት ልጆቹን እንዲጠቀሙ ከሚያደርግባቸው መንገዶች አንዱ እድሜያቸው ከመብሰሉ በፊት ከሚፈጸም የወሲብ ግንኙነት እና ልጅን ለመውለድ ከሚቻልበት የሰውነት መዳበር በፊት ልጅ እንዳይወለድ እንዲሁም የተወለደውን ተንከባክቦ ለማሳደግ ከመድረስ ወይንም  ላፊነትን ለመወጣት ከመብቃት በፊት  ላፊነት ውስጥ እንዳይወድቁ ማድረግ ነው፡፡ከዚህም ጋር ተያይዞ ሴት ልጆቹ በወደፊቱ ሕይወ ቸው ሊገጥማቸው የሚችለውን የሕይወት ውጣ ውረድ ለመቋቋም እንዳይችሉ ከሚያደርጋቸው የኢኮኖሚ ጥገኝነት ፣ ትምህርት ያለመማር ፣ለ ላፊነት ያለመ ጨት፣ በህብረተሰቡ ውስጥ እንዲሁም በአገር ደረጃ ተገቢውን የልማት ስራዎች እንዳይሰሩ ከሚያደርጋቸው ኋላቀርነት እንዲላቀቁ የሚያስችላቸውን አቅም ለማጎልበት የሚረዳቸው በቂ ጊዜ እንዲኖራቸው ያደርጋቸዋል፡፡
ጋብቻን ማዘግየት እና በጋብቻ ወቅትም ልጃገረዶቹን በተለያዩ መንገዶች  መርዳት ከፍተኛ ስራ እንደሆነ ይ መናል፡፡ ያለ እድሜ ጋብቻ እንዲቀር ለማድረግ የሚቀረጹ ፕሮጀክቶች ደግሞ ውጤ ማ እንዲሆኑ በህብረተሰብ ደረጃ ተሳትፎን ይጠይቃል፡፡ ህብረተሰቡ እራሱ የሚሳተፍበትና ያመነበት ጉዳይ ከሆነ ያለእድሜ ጋብቻንም ሆነ ሌሎች ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን ለማስወገድ ቀላል ይሆናል፡፡

ከላይ እንደተገለጸው ያለእድሜ ጋብቻ በሚፈጸምበት አ ባቢ በተለያዩ መንግስ ዊና መንግስ ዊ ባልሆኑ ድርጅቶች እንዲሁም በሴቶች ማህበራትና ቢሮዎች አማ ኝነት ስልጠና እንደመስጠት የመሳሰሉ የግንዛቤ ማስፊያ ስራዎች የሚሰሩ ሲሆን  ዳጊ ሴት ልጆችም በቤተሰቦቻቸው አማ ኝነት ጋብቻ እንዲፈጽሙ የሚደረግባቸውን ተጽእኖ ባለመፍራት በቅርብ ላሉ ህጋዊ ተቋማት እንዲሁም ትምህርት ቤት ጉዳዩን በማመልከት እራሳቸውን የሚያድኑበት አጋጣሚ ብዙ ነው፡፡ ስለሆነም ከምንም በላይ  ዳጊዎቹ እራሳቸው ይህንን ጎጂ ልማዳዊ ድርጊት እንዲከላከሉ የማስቻል አቅም እንዲያጎለብቱ የማድረጉ ስራ እጅግ አስፈላጊ መሆኑንም ጥናት አቅራቢዎቹ ጠቁመዋል፡፡   

*******************************************

አስገድዶ መድፈር ከወሲብ ፍላጎት ጋር የተያያዘ አይደለም፡፡
                                  ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
     
አስገድዶ መድፈር ብዙ ጊዜ ወንድ በሴት ላይ የሚያደርሰወ ቢሆንም ወንድ ወንድን ወይንም ሴትም ወንድን የሚደፍሩበት ሁኔ  አለ፡፡ አንዳንድ ጊዛ በቡድን በመሆን ብዙ ሴቶች ወንዶችን አስረው የሚደፍሩበት አጋጣሚ አለ፡፡ግን ይሄ ብዙ ጊዜ የሚ ይ ስላልሆነ ወደዛ አናተኩርም፡፡ በዚህ ርእሰ ጉዳይ የምንመለከተው ወንድ ለምን ሴትን ይደፍራል የሚለውን ይሆናል፡፡ምክንያቱም ብዙ ጊዜ የሚ ይ ስለሆነ ነው፡፡ለዚህ ማብራሪያ የጋበዝናቸው ዶ/ር ዳዊት ደሳለኝ የማህጸንና ጽንስ ሕክምና እስፔሻሊስትና ረዳት ፕሮፌሰር ናቸው፡፡
      ወንድ ሴትን የሚደፍረው ብዙ ጊዜ የስርአተ ጾ  ክፍፍል ልዩነቱ ወይንም ጀንደር ሚለው ሁኔ  ጋር ይያያዛል፡፡ ሴት እንዲህ ነች ወንድ ደግሞ እንዲህ ነው የሚለውን ህብረተሰቡ የሚያምንበትና ተግባራዊ እያደረገው ካለው ጋር በተያያዘ አስገድዶ መድፈሩ ብዙ ጊዜ ይፈጸማል፡፡ ምክንያቱም ህብረተሰቡ ለወንድ ልጅ  ይል ወይንም አቅም እንዳለው እየነገረ ስለሚያሳድገው ወንዱ በተፈጥሮው ካገኘው ጥን ሬ ባሻገር በአስተሳሰብም  ይል እንዲኖረወ ያደርገዋል፡፡ከዚህም በተለየም በልጅነ ቸው የመደፈር ወይንም የመገለል እንዲሁም የተለያዩ ጥቃቶች የደረሰባቸው ከሆነ አስገድዶ መድፈርን እንደ እልህ መወጫ ይጠቀሙበ ል፡፡ አንድ ወንድ እንደዚህ ያለ ጉዳት እየደረሰበት ያደገ ከሆነና እሱም ጥቃቱን መፈጸሙ በሳይንሳዊው መንገድ ሲተረጎም አእምሮው በሚያድግበት ሰአት የተለያዩ ኢንዛይሞች ማለትም ነርቭ ከነርቭ የሚገናኝበት መልእክት የማስተላለፊያ  ሚ ሎች በደም ውስጥ እየቀነሰ ይመጣል፡፡ አእምሮው እያደገ ሲመጣ ደሙ ግን እየቀነሰ መምጣቱ በሚያድጉበት ሰአት ላይ ይህንን ወሲባዊ ጥቃትም ሆነ ማንኛውንም ወንጀል እንደሰው መግደል የመሳሰሉትን ጨምሮ የመፈጸም እድላቸወ የሰፋ ይሆናል፡፡ ብዙ ጊዜ አስገድዶ መድፈር የሚፈጽሙ ሰዎች ከአንድ ሰወ ጋር ወይንም ከተለያዩ ሰዎች ጋር ጥሩ አይነት ግንኙነት መመስረት የማይችሉ ናቸው፡፡ ይህ እንግዲህ ከአስተዳደግ ወይንም ከተለያዩ የህይወት አጋጣሚዎች ሊሆን ይችላል፡፡ በተረጋጋ ሁኔ  ከሰዎች ጋር መኖር ካልተቻለ ወይንም ህብረተሰቡ የሚጠብቀውን ደረጃ ማሟላት ካልተቻለ እንደመሸሻ የሚቆጠረው የአስገድዶ መድፈር ወንጀልን የመሳሰሉ ሊሆኑ ይችላሉ ፡፡
      አስገድዶ መድፈርን በሚመለከት የተሳሳተ ግንዛቤ እንዳይኖር ያሰጋል፡፡ አስገድዶ መድፈርን የሚፈጽም ወንድ የግብረስጋ ግንኙነት ፍላጎት ኖሮት ስሜትን ለማር ት ሲባል አይደለም፡፡አንድ ወንድ አስገድዶ መድፈርን በሚፈጽምበት ወቅት በግብረስጋ ግንኙነት ወቅት የማ ገኘውን እር   ያገኛል ማለትም አይደለም፡፡ እንዲያውም የወንድ የዘር ፍሬያቸውን ሳይለቁ አስገድዶ መድፈሩ ሊያበቃም ይችላላ፡፡ ስለዚህ ዋናው የአስገድዶ መድፈር ምክንያት ሐይልን መግለጽ መሆኑ ነው በተለያዩ ጥናቶች የተደረሰበት ፡፡ አንድ ወንድ በህብረተሰቡ የተሰጠው  ይል ከሴት የተሸለ እንደሆነ እንዲያስብ አድርጎ ል፡፡ በጾ  ክፍፍሉ ወንድ ከሴት ይበልጣል የሚል ነገር በአእምሮው ውስጥ ስላለ አስገድዶ መድፈር በጥቅሉ ሲ ይ የ ይል መግለጫ ነው፡፡ ስለሆነም አስገድዶ መድፈር እኔ እበልጣለሁ የሚለውን ስሜት መግለጫ እንጂ ወሲብን ማርኪያ አይደለም፡፡
      የተፈጠረው የሃይል ልዩነት እንዳለ ሆኖ የኢኮኖሚው ሁኔ  እንዲሁም በፖለቲ ና እና በእድሜም አጥቂው ከተጠቂው የበለጠ መሆኑን በሚረዳበት ጊዜ  ይህንን አስገድዶ መድፈርን በመፈጸሙእና  ይሉን በማሳየቱ ጊዜያዊ እርከ  ሊያገኝ ይችላል፡፡ አስገድዶ መድፈር በማን ይፈጸማል ሲባል ባልተማሩ ወይንም ስራ በሌላቸወ ሰዎች የሚፈጸም ተደርጎ ይ ሰብ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ብዙ ጥናቶች እንደሚያስረዱት ለከፍተኛ ደረጃ የደረሱ የተማሩና በ ላፊነት ደረጃ ያሉም ሰዎች እንደሚፈጽሙት ነው፡፡ በእንደዚህ ደረጃ በደረሱ ሰዎች ሁኔ  ሲ ይ ደግሞ ባላቸው አቅም ወይንም ኢኮኖሚ ምክንያት ምንም ነገር መፈጸም እንደሚችሉ ወይንም የፈለጉትን ማድረግ እንደማያቅ ቸወ ማሳያ አድርገው ነው የሚወስዱት ፡፡ በእንደነዚህ አይነት ሰዎች የሚደፈሩ ሴቶች ጉዳዩን ለህግም ይሁን ለሕክምና ለማድረስ ስለሚፈሩና ሰዎቹንም ስለሚያከብሩ ወንጀሉ ተዳፍኖ እንዲቀር ይሆናል፡፡ ባጠቃላይ ሲ ይ ግን ተገደው የተደፈሩ ሰዎች ብዙ ጊዜ በህብረተሰቡ ውስጥ መገለል ይደርስባቸዋል፡፡ ጥፋቱን ያደረሱትም እነሱ እንደሆኑ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ አንዲት ሴት ተገዳ ተደፈረች ሲበል በህብረተሰቡ ውስጥ የሚሰጣት ግምትም ይቀንሳል፡፡

      ሌላው  አስገድዶ መድፈር የመፈጸም ሁኔ  የተወሰኑ ወንዶች በቡድን ሆነው ፺ጋንግ ሬፕ ፻ተብሎ በሚገለጸው መንገድ የሚፈጽሙት ነው፡፡ ይሄም ሰዎቹ ለምንድነው እንዲህ ያለ ጥቃት

የሚፈጽሙት ተብሎ ሲጠየቅ በልጅነት ዘመናቸው ወይንም ካደጉም በሁዋላ በህብረት ወንጀል መፈጸምን እያዳበሩ የመጡ መሆናቸውን ነወ መረጃዎች የሚጠቁሙት፡፡ በአ ባቢ ፣ በዘር ወይንም በትምህርት ቤት በመሳሰሉት እነእገሌ እኮ  ይለኞች ወይንም ጎበዞች ናቸወ ተዋጊዎች ናቸወ የሚል አይነት መገለጫን እያዳበሩ የመጡ ሰዎች ናቸው አስገድዶ መድፈር ወንጀልን የሚፈጽሙት ፡፡ እንደዚህ ያለው ወንጀል በተለያዩ የአፍሪካ አገሮችና በሌሎችም የሚ ይ ነው፡፡ ለምሳሌ ኮንጎ ውስጥ የሄ ትልቅ ችግር ነው፡፡ አንዱ ሌላውን ከመዋጋት ይልቅ የተቃራኒውን ወገን አስገድዶ በመድፈር ሃይልን መወጣት ይበልጥ የሚያስደስትበት ሁኔ  ይ ያል፡፡ በሴራሊዮን በባንግላዴየሽ ሁሉ በከፋ ሁኔ  ይፈጸማል፡፡
      አልኮሆል ወይንም ሱስ አስያዥ እጽን መጠቀም አንዱ ለአስገድዶ መድፈር የሚዳርግ ነገር ነው፡፡ ሰዎች በተፈጥሮ ህብረተሰቡ የሰጠውን ሁኔ  ተቀብሎ በማደግ ያልሆነ ነገር ውስጥ እንዳይገቡ የሚመልሳቸው በጭንቅላት ውስጥ የሚገኝ ተፈትሮአዊ ነገር አለ፡፡ ያ ተፈጥሮአዊ ነገር ድርጊትን ለመፈጸም በሚፈለግበት ጊዜ ይሄ ትክክል አይደለም ይሄ ትክክል ነው የሚል ከመጥፎ ነገር የሚከላከለ ነው፡፡  አልኮሆል ወይንም ሱስ አስያዥ ንጥረ ነገር ግን ይህንን ጥሩና መጥፎ ነገር አመላንች የሆነውን ነገር በማደብዘዝ ይገ ዋል፡፡ ስለሆነም ይህንን ነገር ማድረግ የለብኝም ያስቀጣኛል ወይንም ሰው እጎዳለሁ ወይንም ህብረተሰቡ ይህንን ድርጊት ያወግዘዋል ብሎ ለመተው ከመሞከር ይልቅ እንዲያውም ድርጊቱን ለመፈጸም የሚገፋፋ የሚያደፋፍር ነገር ይፈጠራል፡፡  
      አሰድገድዶ መድፈር በህጻናት ላይ ሲፈጽም እነዚህ ደፋሪዎች ሕጻን ወዳጆች ሆነው እንጂ የወሲብ እር   ከሕጻናት ለማግኘት አይደለም፡፡ የሁለትና የሶስት አመት ልጆችን የሚደፍሩ ሰዎች በተፈጥሮአቸው በሕጻን ልጅ የሚሳቡ ናቸው፡፤ በእርግጥ ሁሉም ሕጻናትን የሚደፍሩ ሰዎች ሕጻናትን አፍቃሪ ሆነው ነው ብለን ለመደምደም አይደለም፡፡ ሓይልን ለመግለጽ የሚለው በአዋቂዎች ላይ የሚፈጸመው ወንጀልም አይደለም ሕጻናቱን ለመደፈር የሚያበቃቸው፡፡ ህጻናትን አስገድደው የሚደፍሩ ሰዎች ለወሲብ ፍላጎት መወጫ ሳይሆን ቤተሰብን ለመጉዳት ወይንም አ ባቢዋን ፣በጣም የሚወዳትን ሰው ለመጉዳት ሲባል እንደሆነ ነው ጥናቶች የሚገልጹት፡፡
      አስገድዶ መድፈርን የሚፈጽሙት ወንዶች የግብረስጋ ግንኙነትን ፈልገው ሳይሆን ሓይልን ለመግለጽ የሚያደርጉ ሲሆን በዚሁ አጋጣሚ ግን አንዳንድ ጊዜ ሴቶች ተገደው እየተደፈሩ ሳሉ ወደ ወሲባዊ ስሜት የሚገቡበት ሁኔ  መኖሩም ተረጋግጦአል፡፡ ሴቶቹ በዚህ ስሜት ምክንያት ማለትም ተገድጄ እየተደፈርኩ ግን ደስተኛ ሆንኩ በሚል ብዙ ጊዜ እራሳቸውን ያማርራሉ፡፡ ነገር ግን እንዲህ ያለው ነገር የሚከሰተው ስሜቱ ከተፈጥሮ ቁጥጥር ውጭ በመሆኑ ነው፡፡ ይሄ ሁሉም ተገደው የሚደፈሩ ሴቶች ላይ የሚኖር ሳይሆን አንዳንድ ሴቶች ላይ የሚፈጠር ነው፡፡ ወንዶቹም አስገድደው በሚደፍሩበት ጊዜ  ይላቸውን አሳይተወ ይተዋሉ እንጂ የዘር ፍሬ እስኪለቁ ድረስ ወሲባዊ ግንኙነቱን እያደረጉ አይቆዩም፡፡
አስገድዶ መድፈርን የሚፈጥሩ ሰዎች ምንጊዜም ተጠያቂዎች ናቸው ፡፡ የአስገድዶ መድፈር ወንጀል የሚፈጽሙ ሰዎችን እንደአስቸጋሪ እንጂ እራሳቸው ችግር ደርሶባቸዋል የሚል እምነት የለም፡፡ እነዚህ ሰዎች የአእምሮ ችግር የለባቸውም፡፡ለዚህ ለወንጀሉ የሚገፋፋቸው ቀደም ሲል የነበራቸው ለዚህ የሚያጋልጥ ልምድ ነው ፡፡ አስገድዶ መድፈርን የሚፈጽሙት  ይላቸውን ለመግለጽ ሲሉ ጉዳቱን ስለሚያደርሱ በህብረተሰቡም ሆነ በመንግስት እንዲሁም በሌሎች በሚመለከ ቸው አ ላት ምክር ክትትልና ቁጥጥር ሊወገድ ይገባዋል፡፡  

      ወንጀሉን ለመከላከል ህግን ተግባራዊ ማድረግ ፣ህብረተሰቡን ማስተማር ፣ቤተሰብ ልጆቹን ተንከባክቦ እንዲጠብቅ ማድረግ ፣የራስን ሁኔ  ወይንም ክብርን መጠበቅ፣ በትምህርት ቤት በመኖሪያ ቤት አ ባቢ ያሉ ልጆችን በትክክለኛወ መንገድ መንከባከብ ፣ሴትን ልጅ ማስተማር ጠቃሚው አ ሄድ ነው ፡፡ ወንዶች ብዙውን ጊዜ ለሴቷ ገንዘብና የተለያዩ ንብረቶችን በመስጠት ወይንም ግብዣ በመጋበዝ ስለሚያ ልሉዋቸው ይህንን ለማስወገድ ሴቷ  በኢኮኖሚም አቅምዋን ያጎለበተች እንድትሆን ማስቻል ችግሩን ለመቅረፍ ያስችላል፡፡
ሴቶች የደረሰባቸውን ጉዳት ለማስወገድ በተለይም የሕክምና ክትትል በሚያደርጉበት ጊዜ እራሳቸውን ግልጽ አድርገው መቅረብ ያስፈልጋቸዋል፡፡ ከተገዶ መደፈር በሁዋላ ለሚደርሱ የጤና ችግሮች ማለትም የስነአእምሮ መጎዳት ፣እርግዝና ፣የአባላዘር በሽ  የመሳሰሉት ሁሉ ሊከሰቱ የሚችሉ ስለሆኑ በወቅቱ ሕክምና ማድረግ ተገቢ ነው፡፡ ሴቶች ተገደው በመደፈራቸወ በወደፊቱ ሕይወ ቸው እነሱም አጥቂ እንዳይሆኑ ወይንም የተለያዬ ወንጀሎችን እንዳይፈጽሙ ለማስቻል የምክር አገልግሎት እንዲያገኙ ማድረግ ተገቢ ነው፡፡ የምክር አገልግሎት ካላገኙ ግን እራሳቸውን ከሌሎች ዝቅ አድርገው መኖር፣  ሰውን ለመቅረብ መፍራት፣ እራሳቸውን አሻሽሎ የመኖር እቅድ የሌላቸው ፣እራሳቸውን መግለጽ የማይችሉ ፣መስራት ፣ መማር የማይችሉ ይሆናሉ፡፡

***************************************

...የእናትህም አህያ ያችውልህ...
                                                              ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
ይድረስለኢትዮያየማህጸንናጽንስሐኪሞችማህበር ...እንደምንሰንብችሁዋል፡፡እኔ የምኖረው በአሁኑ ሰአትአዲስአበባሲሆንየኑሮዬመሰረትየትውልድአንባቢዬግንወደአንኮበርነው፡፡
ከላይ ባነበባችሁት መግቢያነት የደረሰንን የተሳ ፊያችንን የወንድወሰን  ይሉን ከኤችአይቪ ኤይድስ ጋር የተያያዘ እውነተኛ  ሪክ  ነቡ ዘንድ ጋብዘናችሁዋል፡፡ የአቶ ወንድወሰንን ደብዳቤ መነሻ በማድረግም ኤችአይቪን በተመለከተ በጥናት የተደገፈ መረጃ ለንባብ ብለናል፡፡ ምንጫችን                                         )ነው፡፡
        
፵ይድረስ ለኢትዮያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር ...እንደምን ሰንብ ችሁዋል፡፡እኔ የምኖረው በአሁኑ ወቅት አዲስ አበባ ሲሆን የኑሮዬ መሰረት የትውልድ አ ባቢዬ ግን በሰሜን ሸዋ አ ባቢ ነው፡፡ እኔ አሁን በእድሜዬ ወደ ሀያ አመት ተጠግቻለሁ፡፡  ዲያ ለእናንተ ለመጻፍ የተገደድኩት  ሪክ ምን መሰላችሁ ..የእናትና አባ  ጉዳይ ነው፡፡ እናትና አባ  ሁለቱም ማለት ይቻላል በእድሜያቸው ገና ሰርተው ያልጠገቡ ናቸው፡፡ እና  እድሜዋ ወደ ሰላሳ ስድስት አመት አከባቢ ስትሆን አባ  ግን ወደ አርባው የተጠጋ ነው፡፡ እነዚህ ሰዎች ሁለቱም ማለት ይቻላል ኤችአይቪ በአገራችን በ ወቀበት ጊዜ ገና ሮጠው ያልጠገቡ ሕጻናት ናቸው ብል ማጋነን አይሆንብኝም፡፡ አባ  በባህርይው እጅግ አስቸጋሪ ሰው ነው፡፡ ለእና ም ሆነ ለእኛ ለልጆቹ የማይመች እንዲያውም በመጠጥ  ይል እየተመረዘ ሁልጊዜ በምሽት ንትርክና ጭቅጭቅ የሚያበዛ እንዲሁም ለእኛ ለልጆቹም መጥፎ ምሳሌ የሆነ ሰው ነው፡፡ እና ም ሁልጊዜ ወደ እግዚአብሔር ስ ማርር እንዲያውም እኔ በቤቱ ትልቅ ልጅ ስለነበርኩ አጽናናት ነበር፡፡
      አንድ ቀን ጠዋጽ በማለዳ አባ  ፈረሱን እየሳበ መንገድ ጀመረ፡፡ ከተል ብዬ ..አባዬ በጠዋት ወደየት ነህ አልኩት.. እሱም ምንአገባህ ብሎኝ ሄደ፡፡ ወደቤት ተመለስኩና ለእና  ስነግራት ተወው ይሂድ አለችኝና እሱዋም ወደገበያ ይዛው የምትሄደውን ነገር መቆጣጠር ጀመረች፡፡ እኔም ዝም ብዬ ወደትምህርት ቤ  መንገዴን አቀናሁ፡፡ ትምህርት ቤት ስደርስ አስተማሪው አልመጣምና እንሂድ ተባብለን ከጉዋደኞቼ ጋር ተለያየን፡፡ እኔ እና ን ላግዛት ብዬ ወደገበያ ሄድኩ፡፡ ...እና  ከምትቀመጥበት ቦ  ስሄድ የለችም... በአይኔ እያማተርኩ ሳፈላልግ የአባ ን ፈረስ ከአንድ ጠጅ ቤት ደጃፍ አየሁት፡፡ ወደዚያ ሄድኩና እሱን ለማግኘት ስሞክር ጠጅ ቀጂው አባትህ ከሰው ጋር ክፍል ይዘዋል አለኝ፡፡ በጣም ደነገጥኩ፡፡ ጠጅ ቀጂውም መልሶ ምነው ደነገጥክ እንዴ? ምን አዲስ ነገር አለ ...ሁሉም አኮ እንደዚህ ያደርጋሉ፡፡ የእናትህም አህያ ያችውልህ አለኝ፡፡ እኔም እሱዋ እንደዚህ ያለውን ነገር ከማየትዋ በፊት ቀድሜ ላግኛትና ...በቃ ወደቤ ችን እንሂድ ብዬ ወደአህያዋ ገሰገስኩኝ፡፡ እዚያም አህያዋ የቆመችው እንደዚሁ ከሌላ ጠጅ ቤት ደጃፍ ነው፡፡ ቀስ አልኩና አየት አየት ሳደርግ እና  ከአንድ የሰፈራችን አባወራ ጋር ከአንድ ጥግ ቁጭ ብላ ጠጅ ትጠጣለች፡፡ ከሰውየውም ጋር ይሳሳቃሉ፡፡ አለፍ አለፍ እያለም ትከሻዋን ይደባብሳ ል፡፡ እስከአሁን ድረስ እኔን የሚገርመኝ ነገር ግን የአባ ን ሁኔ  በትዝብት አልፌ እና  ጋ ስደርስ ግን እራሴን መቆጣጠር ሲያቅተኝ ነው፡፡ አልቻልኩም፡፡ ዘው አልኩና ተነሽ እንሂድ አልኩዋት፡፡ ሰውየውም ቢያፈጥብኝ እና ም ብ ፍር እኔ ግን ንዴ ን መቆጣጠር አቃተኝ፡፡ በሁዋላ ሰውየው ዘወር በል ከፊ  ሌላ ነገር እንዳይከተልህ ...ሰው መጫወት አይችልም እንዴ ? ሲለኝ... ጠጅ ቀጂው መጥቶ እየገፈተረ አስወጣኝ፡፡ እኔም ሳስበው ከዚያኛው ጠጅ ቤት ያለው አባ  ጸቡን ቢሰማና ቢመጣ... የምንደባደበው ደግሞ ቤተሰቦቹ መሆናችንን ሲያይ...ከዚያ በላይ ደግሞ ሚስቱ ከሌላ ሰው ጋር እየተዝናናች መሆኑን ሲያውቅ ሌላ እልቂት ይፈጠራል ብዬ እያዘንኩ ወደቤተ አመራሁ፡፡ ግን በመንገዴ ላይ እያለሁ አንድ ነገር ወሰንኩ፡፡ በቃ... ከዚያች አከባቢ መልቀቅ ... አባ  ከሌላ ሴት ጋር ... እና  ደግሞ ከሌላ ወንድ ጋር ሆነው ከማየት ከመስማት በላይ ምንም የከፋ ነገር እንደማይመጣ ተሰማኝ፡፡ የሶስት ልጆች እናትና አባት የሆኑት ሰዎች እንደዚህ ያለ ጥፋት ሲፈጽሙ የዘመኑንም ነገር እንዳልተረዱት ገባኝ፡፡ ስለዚህ በዚያኑ ሰሞን ደህና ሁኑ ሳልል ወደ አዲስ አበባ መጣሁ፡፡
ይህንን ጽሁፍ ለመላክ የተነሳሳሁበት ምክንያት ከዚህ የሚቀጥለው ነው፡፡ እናትና አባ  ፍቺ ከፈጸሙ እነሆ ሶስት አመ ቸው ነው፡፡ ከአባ  ከተፋ ች በሁዋላ ጉዶበረት ከምትባል ከተማ ለስላሳና አረቄ እየሸጠች መተዳደር ጀምራ ነበር፡፡  ዲያ የዛሬ ስድስት ወር ገደማ እናትህ በጣም  ማለችና ድረስላት ተብዬ ተነስቼ ሄድኩ፡፡ ወደ አዲስ አባባ አምጥቼም ሳሳክማት የሚያሳዝነው ነገር ኤችአይቪ ፖዘቲቭ ሆናለች፡፡ እንግዲህ ለቫይረሱ የተጋለጠችው ከስራዋ ጋር በተያያዘ መሆኑን አንዳንድ መረጃዎች ከአ ባቢው አግኝቻለሁ፡፡ የእና  በቫይረሱ መያዝ በሕይወት ዘመኔ ከገጠሙኝ ሀዘኖች የበለጠው እንደሆነ እገም ለሁ፡፡ ምክንያቱም  እና ን ከጉዋደኛዋ ጋር ባገኘሁዋት ጊዜ ስለኤችአይቪ ምንነት ላስረዳት ስሞክር እኔ ሁሉንም ነገር ሰምቻለሁ አውቃለሁ ...አንተ አትነግረኝም የሚል መልስ ነበር የሰጠችኝ፡፡ ውሎ አድሮ ግን ከዚህ ቫይረስ አለማምለጧ አሳዝኖኛል፡፡ እራስዋን የምትከላከልበትን ነገር አልተጠቀመችም ወይንም የባህርይ ለውጥ አላመጠችም ፡፡እባከችሁ በእንደዚህ ያለ ሁኔ  ለሚጎዱ ሰዎች ምክር ለግሱዋቸው፡፡፶

***               ***
የተሳ ፊያችንን የአቶ ወንድወሰን  ይሉን ጽሁፍ ካነበብን በሁዋላ በኤችአይቪ ዙሪያ በቡ ጅራ አ ባቢ ወደ ሶስት ሺህ ሰባት መቶ አርባ ሶስት ወጣቶች ላይ የተደረገውን ጥናት ተመልክተናል፡፡ በተደረገው ጥናት እንደተረጋገጠው ለጥናት ከተመረጡት ሰዎች መ ከል ወደ ዘጠና ሰባት በመቶ ፺97%) የሚሆኑት ስለኤችአይቪ ኤይድስ መተላለፊያ መንገዶች መረጃ እንደአገኙ ወይንም እውቀቱ እንደአላቸው ተረጋግጦአል፡፡ ጥያቄ ከተደረገላቸው መ ከልም ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ሙሉ በሙሉ መተላለፊያውንና መከላከያውን ጭምር ትክክለኛውን መልስ አጠናቀው እንደሰጡ ጥናቱ ያሳያል ፡፡ ነገር ግን አንዳንዶቹ ማለትም ጥናቱ ከተደረገባቸው ሰዎች መ ከል ወደ አርባ ስምንት ከመቶ የሚሆኑት ፺48 %) የመተላለፊያ መንገዱን ካለማወቃቸው የተነሳ በወባ አማ ኝነት እንደሚተላለፍ ነበር የገለጹት፡፡ ሽንት ቤት በመጋራት እንዲሁም አብሮ በመብላትና በመጨባበጥ በመሳሰሉት መንገዶች ጭምር እንደሚተላለፍ የገመቱም ነበሩ፡፡ ከዚህ በተጨማሪም አንዳንዶች ቀደም ሲል በነበረው ባህሪያቸው ሳቢያ ኤችአይቪ እንደማይይዛቸውና ማሰብ የሚፈልጉት በወደፊቱ ሕይወ ቸው ምክንያት ሊደርስ የሚችለውን ብቻ እንደሆነ ነው የተናገሩት፡፡ በቡ ጅራ የተደረገው ጥናት እንደሚመሰክረው ብዙዎቹ ሰዎች ኤችአይቪ ኤይድስ ከሰው ወደሰው እንደሚተላለፍ ቢያውቁም በምን ምክንያት እንደሚተላለፍ ግን ብዙዎቹ ስለማያውቁ ፺በመጨባበጥ አብሮ በመብላት...ወዘተ፻ በአኑዋኑዋራቸውም ላይ ችግር የፈጠረበት ሁኔ   ይቶአል፡፡
በኤችአይቪ ቫይረስ መያዛቸውን ያወቁ ሰዎችም እራሳቸውን በመንከባከቡና ፀረ ኤችአይቪን በመጠቀም ረገድ ብዙም እርምጃ የማይወስዱ ሰዎች ብዙዎች ሲሆኑ በተለይም ጋብቻ የፈጸሙ ወጣቶች የትዳር ጉዋደኞቻቸውን በማመን እንዲሁም ጋብቻ ያልፈጸሙትም ጭምር ፀረ ኤችአይቪን በመውሰዱ ረገድ ወደሁዋላ ያፈገፈጉበት ሁኔ  ተስተውሎአል፡፡
አንዳንድ ሰዎች ስለኤችአይቪ ኤይድስ በከፍተኛ ደረጃ እውቀቱ እንዳላቸው ቢረጋገጥም ይህ ነገር ግን እያንዳንዱ ሰው እራሱን ከቫይረሱ እንዴት መከላከል እንዳለበትና ምናልባትም በቫይረሱ ከተያዘ በሁዋላ ምን እርምጃ መውሰድ እንዳለበት ባጠቃላይም የባህሪይ ለውጥ ለማምጣት ከሚያስችለው ደረጃ ላይ ደርሶአል ለማለት አያስደፍርም፡፡
 የኤችአይቪ ኤይድስ ስርጭትን በሚመለከት በገጠርና በከተማ ያለው ሁኔ  ሲ ይ ሰዎች በተለያየ ምክንያት ማለትም በንግድና በመሳሰሉት ማህበራዊ እንቅስቃሴዎች ከቦ  ቦ  ስለሚዘዋወሩ ለስርጭቱ እንደ አንድ ምቹ መንገድን እንደፈጠረ ምክንያት ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ለተለያዩ ስራዎች በከተሞች ተሰማርተው የነበሩ የገጠር ሰዎች ሕመሙ በሚከሰትባቸው ጊዜ ተመልሰው ወደቤተሰቦቻቸው ማለትም ወደገጠር የሚሄዱ በመሆኑና በዚያም ባለው የተለያዩ አገልግሎቶች እና በሚፈጠረውም የፍቅር ግንኙነት ሳቢያ ቫይረሱ ሊሰራጭ እንደሚችል ይ መናል፡፡
ኤችአይቪን በመከላከሉ ረገድ ተቀዳሚው ተግባር ሰዎች በቫይረሱ ስርጭትና በመከላከሉ ረገድ ምን መደረግ እንዳለበት በተገቢው እንዲያውቁ ማድረግ ነው፡፡ ነገር ግን ከእውቀትም በላይ ሰዎች የባህርይ ለውጥ እንዲያመጡ የሚያስችላቸውን ዘዴ መጠቀምም ሊ ለፍ የማይገባው ነገር ነው፡፡ የባህርይ ለውጥ ሳይኖር ስለ ኤችአይቪ ኤይድስ ምንነትና ስለስርጭቱ እውቀት መኖሩ ብቻውን ከቫይረሱ ራስን ለመከላከል እንደማያበቃ ነው ጥናቶች የሚመሰክሩት፡፡

ማንኛውም ሰው ምርመራ በማድረግ እራሱን ማወቅ ያለበት ሲሆን ምናልባት በኤችአይቪ ቫይረስ የመያዝ እድል እንኩዋን ተፈጥሮ ቢሆን የህክምና ባለሙያዎችን ምክር መቀበል እና ጸረ ኤችአይቪ መድሀኒትን መጠቀም ተገቢ ይሆናል፡፡ ከዚህም ባለፈ አድሎና መገለልን እንዲወገድ ማድረግ እንዲሀም ሌሎች ሰዎች ለኤችአይቪ ቫይረስ ተጋላጭ እንዳይሆኑ ማስተማር ከሁሉም የህብረተሰብ ክፍል እንዲሁም ጉዳዩ ከሚመለከ ቸው አ ላት ሁሉ ይጠበቃል፡፡

*********************************

     Hymen----እድሜ ልክ ልጃገረድ ሆኖ መቀጠል ...
                                   ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
" የልጅቷ ጽሁፍ"

 

ጠያቂያችን በጽሁፍዋ ያሰፈረችው ቁምነገር
ከወንድ ጋር ምንም አይነት የወሲብ ግንኙነት ሳትፈጽም የቆየች መሆኗንና በሁዋላም ከወንድ ጉዋደኛዋ ጋር ወሲብ ስትፈጽም በተለመደው መልኩ ደም አልፈሰሰኝምና ለምንድነው?
ጉዋደኛዬ ለጊዜው ከሌላ ወንድ ጋር እንዳልተገናኘሁ ስግረው ግድየለም አምንሻለሁ ከለ በሁዋላ ግን ---የለም የለም---ከሌላ ወንድ ጋርማ ተገናኝተሸል ---ይኸው ጡትሽ ---ሰውነትሽ ይመሰክራል አለኝ ---የሚል ነው፡፡
ይድረስ ለኢሶግ በሚል ስለ ልጃገረድነት ከተሳ ፊያችን የደረሰንን ጥያቄ መሰረት በማድረግ የተለያዩ መረጃዎችን አመሳክረናል፡፡ በእንግሊዝኛው       በሚል የሚ ወቀው ድንግልናን በሚመለከት የማህጽንና ጽንስ ሕክምና እስፔሻሊስት እና ረዳት ፕሮፌሰር ዶ/ር እያሱ መስፍን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መልስ ሰጥተውናል ፡፡ አፈጣጠሩ ምን እንደሚመስል ከኢንተርኔት ያገኘነውን ምስልም ለግንዛቤ አቅርበነዋል፡፡
     ---በአማርኛው ድንግልና ፺ልጃገረድነት፻ የሚባለው አ ል ድፍን ሆኖ የሚፈጠር ሲሆን በሂደት በእድገት ጊዜ ግን ወደ ወንፊትነት ከዚያም መሀከሉ ክፍት እየሆነ ይሄዳል፡፡ መሀከሉ ክፍት ሲሆን ክብ ወይንም ጨረቃ ቅርጽ ነው የሚሆነው፡፡
     ..በተፈጥሮ ሂደቱን አስተ ክሎ ቅርጹን የማይለውጥ ከሆነ ግን ድፍን ፺ጭንጫ፻ ሆኖ ይቀራል፡፡ ጭንጫ ወይንም ድፍን ሆኖ የሚቀረው ብልት ግን እንኩዋንስ የወንድ ብልት ሊያስገባ የወር አበባ እንኩዋን የማያስወጣ በመሆኑ በህክምና እርዳ  እንዲከፈት ይደረጋል፡፡
በሀገራችን በተለምዶ      .---ድንግልና  በተለያዩ የአኑዋኑዋር ሁኔ ዎች ወይንም የእስፖርት እንቅስቃሴዎች በመሳሰሉት ሊገሰስ እንደሚችል ሲነገር የኖረ ቢሆንም እንደዶክተር እያሱ መስፍን መልስ ግን በምንም አይነት በአኑዋኑዋር ሁኔ  ወይንም በእስፖርት እንቅስቃሴ አይገሰስም፡፡
ሌላው ከጠያቂያችን የተሰነዘረው የወንድ ጉዋደኛዬ ድንግልናሽን ለሌላ ወንድ እንደሰጠሸ የሚያሳይ መረጃ አለኝ---ጡትሽና ሰውነትሽ ይመሰክራል---ለሚለው አንዲት ሴት ድንግልናዋን ለወንድ ብትሰጥም እንደዚህ አይነት የሰውነት አ ል ምስክርነት እንደማይኖር ነው ዶ/ር እያሱ የገለጹት፡፡
      ..ድንግልና አይነቶች
       ----ክብ የሆነ
      ክብ የሆነ ድንግልና የሚባለው በአብዛኛው ብዙ ሴቶች የሚኖራቸወ ሲሆን ዙሪያውን እንደቀለበት ጠርዝ ያለው ነው፡፡ ከወንድ ጋር በሚኖረው ግንኙነት ዙሪያውን ያለወ ቀለበቱ ስለሚሰነጠቅ መድማት ከተላል፡፡ አንዳንድ ጊዜ በግንኙነቱ ጊዜ የሚሰነጠቀው       አልፎ ብልቱንም ስለሚሰነጥቀው የመድማት ሁኔ ው በዛ ያለ ይሆናል፡፡ ከለበለዚያ ግን ደሙ የጠብ  ያህል ብቻ ሆኖ የሚቀርበት ሁኔ  ያጋጥማል፡፡  
C       ---------የጨረቃ ቅርጽ
የዚህ አይነቱ ድንግልና በቅርጹ ክብ ናለመሆኑ በስተቀር ከወንድ ጋር በሚኖረወ ግንኙነት ወቅት የሚፈጠረው የመድማት ሁኔ  ክብ ከሆነው ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡
C         ---------ወንፊት የሚመስል
ድንግልና በመጀመሪ ሲፈጠር ድፍን የሆነ ሲሆን ቀጥሎ የሚያመራው እንደወንፊት ወደመሆን ነው፡፡ ከዚያ በሁዋላ እድገቱን ናልቀጠለ ግን ወንፊት ሆኖ ይቀራል፡፡ ከወንድ ጋር በሚኖረው የወሲብ  ግንኙነት ወቅት ምንም ምቹ ያልሆነ ነው፡፡ በእርግጥ የወር አበባ በማሳለፍ ረገድ ምንም ችግር የሌለው ነው፡፡  
I          ---------ድፍን ወይንም ጭንጫ
የዚህ አይነት ተፈጥሮ ያላቸው ሴቶች እጅግ በአስቸጋሪ ሁኔ  ላይ የሚገኙ ሲሆን የወር አበባቸው የማይፈስ እንዲሁም ከወንድ ጋር ለሚኖራቸው የወሲብ ግንኙነት ምንም ዝግጁነት የሌለው ተፈጥሮ ያላቸው ናቸው፡፡ እንደዚህ ያለው ተፈጥሮ በሕክምና ማለትም በቀዶ ጥገና ካልተስተ ከለላቸው ሕይወ ቸውም እጅግ አስቸጋሪ ሁኔ  ይገጥመዋል፡፡
       
ቀደም ሲል ለማሳየት የተሞከሩት የድንግልና አይነቶች ብቻ አይደሉም በተፈጥሮ የሚከሰቱት፡፡ አንዲት ሴት በተፈጥሮዋ የምት ደለውን በሁዋላም ከወንድ ጋር ለሚኖራት ወሲባዊ ግንኙነት መነሻ የሚሆነው ድንግልና       አንዳንድ ጊዜ የሚለጠጥ          ሆኖ ይፈጠራል፡፡ ይህ አይነቱ ድንግል ከወንድ ጋር ወሲባዊ ግንኙነት እየተፈጸመ እንዲያውም ልጅ ተረግዞ እየተወለደ ጭምር ለዘለአለሙ ሊኖር ይችላል፡፡ በተፈጥሮው የሚለጠጥ በመሆኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ከወንድ ጋር በሚፈጸም ወሲባዊ ግንኙነትም ምንም አይነት የመተርተር እና የመድማት ሁኔ  ሳያጋጥመው በመለጠጥ እና በመመለስ የሚገጥመውን  ሁኔ  ይቀበላል፡፡
እንግዲህ ወደጠያቂየቃችን ሁኔ  ስንመለስ ምናልባትም በተፈጥሮው የሚለጠጠው         አይነት       ኖሮ ሊሆን ይችላል ምንም አይነት የመድማት ምልክት ሳይ ይ የቀረው፡፡ ይህ ደግሞ የጠያቂያችን ብቻ ሳይሆን የብዙ ሴቶችም ተፈጥሮአዊ ሁኔ  ሲሆን በዚህም ሳቢያ በተፈጥሮ አንድ ነገር እንደጎደለ አድርጎ ማሰብ እንደማይገባ ነው ከተለያዩ መረጃዎች የተመለከትነው፡፡ እንዲያውም ከወንድ ጋር ከሚኖረው ወሲባዊ ግንኙነት ባሸገርም በመውለድ ጊዜም እየተለጠጠ የሚመለስ በመሆኑ እድሜ ልክ ልጃገረድ ሆኖ መቀጠል እንደማለት ነው የሚል ምላሽም ተሰጥቶበ ል፡፡

***************

ወርቅ ወተት...
                                                ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ

፵ስሜ ናርዶስ ይባላል፡፡ አሁን የመጀመሪያ አመት የዩኒቨርሲቲ ተማሪ ነኝ ፡፡ እኔ የምሰጠው አስተየት በተለይም ከጡት ወተት ጋር በተየያያዘ ነው፡፡ ከሕጻንነ  ጀምሮ እንደጉንፋን ለመሳሰሉ የተለያዩ ሕመሞች የተጋለጥኩ ነኝ፡፡ አብራኝ የምትማር ጉዋደኛዬ ደግሞ አንድም ነገር ሕመም የሚባል ነክቶአት አያውቅም፡፡  ዲያ እኔና እርስዋ ስንወያይ ያገኘሁት መልስ እስዋ ጡት በደንብ በመጥባትዋ ምክንያት ከእኔ የተሸለ አቅም ያላት በመሆኑ ምንም አይነት ሕመም እንደማያጠቃት ነው፡፡ ይህንኑ ሰምቼ የእኔን አስተዳደግ እና ን ብጠይቃት ምናልባትም ከሶስት ወር ላልበለጠ ጊዜ ...እሱም ወደስራ እየሄደች እየመጣች እንዳጠባችኝ ነው የነገረችኝ፡፡ ...አላሳዝንም? እኔ አሁን የማስበው ልጅ ስወልድ ያለምንም ማቋረጥ ቢያንስ ለአንድ አመት ማጥባት ነው፡፡ ምናልባት የስራ ሁኔ  ሊኖር ይችላል፡፡ ነገር ግን ከማገባወ ሰው ጋር በቅድሚያ የምስማማው ነገር ቢኖር ...ምን መሰላችሁ? እኔ ልጅ ስወልድ ስራዬን ትቼ ቁጭ ብዬ በደንብ ማጥባት እንዳለብኝ ነው፡፡ እንደእኔ አይነት ጉንፋናም ልጅ ከማሳድግ ጤነኛ ልጅ ማሳደግ በጣም እፈልጋለሁ፡፡ እስቲ በዚህ ዙሪያ ባለሙያ አማክሩና ለእኔም ሆነ እንደእኔ ለተቸገሩ በደንብ ምክር ለግሱን፡፡፶
      ጠያቂያችን ባደረሰችን መልእክት መሰረት ለዚህ ርእሰ ጉዳይ የጋበዝናቸው ዶ/ር መንግስቱ  ፈሰ የህጻናት ሕክምና እስፔሻሊስት ናቸው፡፡ ዶ/ር መንግስቱ በአሁኑ ሰአት የሚሰሩት     (                                           ) በሚባል ድርጅት ውስጥ ነው፡፡
***                  ***

    • ሕጻኑ 50% ሀምሳ በመቶ የሚሆነውን ሓይል ሊያገኝ የሚችለው ከጡት ወተት ነው፡፡
    • እንገር...የመጀመሪያው ብጫ ወተት በቫይ ሚን የበለጸገ ወርቅ ወተት ነው፡፡

የሕጻንነት ትርጉም ከሕግ አንጻር ከተወለዱበት ጊዜ አንስቶ እስከ አስራ ስምንት አመት ሲሆን  በሕክምና ግን የተለያዩ አተረጉዋጎሞች አሉት፡፡ ለምሳሌ በአሜሪካ የሃያ አንድ ፺21፻ አመት ልጅ በልጅነት እድሜ ክልል ውስጥ ይመደባል፡፡ ያልተወለዱትን በሚመለከት ጽንስ በሚባል ደረጃ የሚ ወቅ ነው፡፡
የህጻናት አመጋገብ የሚጀምረው ከተጸነሱበት ጊዜ አንስቶ ነው፡፡ እንዲያውም እናትየው ቢቻል ከመጸነስዋ በፊት የተመ ጠነ የአመጋገብ ሁኔ  ሊኖራት ይገባል፡፡ ከማርገዝዋም በፊትን በእርግዝና ወቅት የተመጣጠነ ምግብ የምትወስድ እናት የተስተ ከለ ጽንስ እንዲኖራትን ወይንም ጽንሱም ተገቢውን የሚያስፈልገውን ንጥረ ነገር እና ሌሎች ምግቦች እያገኘ እንዲያድግ ይረዳዋል፡፡ ስለሆነም የህጻናት አመጋገብ ሲባል ከጽንሱ መጀመር ጋር የተያያዘ ነው፡፡
ጽንሱ በማህጸን ውስጥ እያለ ከእናትየው የሚያገኘው ምግብ ቫይ ሚን፣ ሚኒራል፣ ሓይል፣ ኢነርጂ ባጠቃላይም ለሰውነት እድገት የሚረዳውን ሁሉ እንዲያገኝ ይረዳዋል ፡፡ እናትየው የተዛባ የአመጋገብ ስልት ካላት ለጽንሱም የም  ፍለው ነገር በቂ ስለማይሆን የጽንሱ ተጠቃሚነት የቀነሰ ሊሆን ይችላል፡፡ ባአብዛኛው ግን ተፈጥሮ የሚያደላው ወደ ጽንሱ ስለሚሆን እናትየው ብትጎዳም ለሽሉ የሚያስፈልገው ነገር ይቀጥላል፡፡ ምግብን ማስተ ከል የሚያስፈልገወ ለሁለት ነገር ነው፡፡ አንደኛው ለእራስዋ ለእናትየው ሲሆን በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ጽንሱ ይሆናል፡፡ብዙ ጊዜ እናቶች እርግዝና ሲጀምራቸው የምግብ አለመስማማት ይኖራል፡፡ በዚህ አጋጣሚ  ሽሉ ተገቢውን ምግብ ከእናትየው ካላገኘ የክብደት መቀነስ የመሳሰለው ችግር ይከሰ ል፡፡
የህጻናት አነስተኛ ክብደት ይዞ መወለድ ምግብ ከማነስ ብቻም ሳይሆን ከተለያዩ ነገሮች ጋር ይያያዛል፡፡ እንደ ደም ግፊት፣ ስኩዋር የመሳሰሉት ከአመጋገብ ጋር የተያያዙ ችግሮች በእናትየው ላይ ካሉ የጽንሱ ክብደት ሊቀንስ ይችላል፡፡ በተጨማሪም የአንጎል ስራ ላይ ለምሳሌ ትምህርት አቀባበል ፣የስራ ተነሳሽነት የመሳሰሉትን ሁሉ ያላሙዋ ሕጻናት ሊወለዱ ይችላሉ፡፡
የእርግዝናው ጊዜ አልቆ ሲወለዱ ተፈጥሮ መፍትሔ ይዞ ነው እነዚህ ልጆች የሚወለዱት፡፡ ሕጻን በተወለደ ከ30 ደቂቃ እስከ አንድ ሰአት ባለ ጊዜ ውስጥ ጡት መጥባት አለበት፡፡ ልጁ ቀደም ብሎ ጀምሮ ጡት መሳብ ከጀመረ ወተቱ ያለችግር ይመረ ል፡፡ ይወርዳል፡፡ የጡት ወተት ከምግብነቱ በተጨማሪ ሕጻናት በተለያዩ በሽ ዎች እንዳይጠቁ የሚረዳቸው ነው ፡፡ እናትየው በተለያዩ ጊዜያት ያመረተቻቸው መከላከያ          ) የሚባሉት አስቀድሞም ለጽንሱ ከመተላለፋቸው በላይ በእናት ጡት ወተት አማ ኝነት ልጁ ያገኛቸዋል፡፡
በመጀመሪያው ሰባሁለት ሰአት ወይንም እስከ አንድ ሳምንት ድረስ ያለው የእናት ጡት ወተት መልኩ ብጫ ሲሆን ይህም በቫይ ሚን ኤ የበለጸገ ወተት ነው፡፡ በአገራችን አጠራር እንግር የሚባለው ይህ ወተት አንዳንድ ጊዜ ቆሻሻ ነው በሚል ሕጻናቱ እንዳይጠቡት  ልቦ እንዲፈስ የመደረጉ ሁኔ  ትልቅ ስሕተት ነው፡፡ ይህ ወተት የመጀመሪያው ተፈጥሮአው ክትባት መሆኑን ሁሉም ሊያውቅ ይገባል፡፡ እንዲያውም ወርቅ ወተት ተብሎ ነው የሚ ወቀው፡፡
የጡት ወተት ለህጻናቱ ያለጊዜ ገደብ መሰጠት አለበት፡፡ አንዳንድ ጊዜ ለህጻናቱ የሚጠቡበትን ሰአት መድቦ በየሁለት ወይንም ሶስት ሰአት በማለት ለመመገብ መሞከር  በጣም ስህተት ነው፡፡ ሕጻናቱ በፈለጉበት ሰአት መጥባት አለባቸው፡፡
እናቶች ጡት ማጥባት በሚጀምሩበት ወቅት አንዱን ጡት ለሕጻኑ ሲሰጡት ሌላኛወ ጡት ሊፈስ ይችላል፡፡ ያ የሚፈሰው ጡት ወተት እንዳይፈስ በሚል ቶሎ ወደዚያኛወ ጡት ሕጻኑን የማዞር ሁኔ  ይኖራል፡፡ ነገር ግን ምን ጊዜም ጡት በመጀመሪያው ዙር የሚፈሰው ወተት ሳይሆን ውሀ ነው፡፡ ስለዚህ ሕጻኑ በመጀመሪያው ጡት ውሀውን ከጠጣ በሁዋላ እንደገና ወደሁለተኛው ጡት ሲዞር አሁንም የሚያገኘው ውሀ ነው፡፡ ስለዚህ ሆዱ ይሞላና መጥባቱን ያቋርጣል፡፡ነገር ግን ሕጻኑ መጥባት ያለበት ውሀውን ጨርሶ ወተቱን በደንብ እስኪያገኝ እና ጡቱ ሙልጭ ብሎ ባዶ እስኪሆን እንጂ ሌላኛው ጡት ፈሰሰ ተብሎ አቋርጦ ጡቱን መለወጥ ትክክለኛው የአጠባብ ስልት አይደለም፡፡
እናቶች ጡት በሚያጠቡበት ጊዜ አሰጣጡ የጡቱን ጫፍና የጡቱን ዙሪያ ጥቁሩን ክብ የጡት አ ል ማለት ነው አንድ ላይ በአፉ እንዲጎርስ በማድረግ መሆን አለበት፡፡ በዚህ መልክ ጡቱን እንዲይዝ ከተደረገ የጡት ወተት በደንብ ይመነጫል፡፡ ከዚህ ውጭ ግን የጡቱን ጫፍ ብቻ በመያዝ የሚመጠምጥ ከሆነ ወተትም በደንብ አያገኝም እንደገናም እናትየው ጡቷን ሊያማት ስለሚችል ማጥባትዋን ል ቋርጥ ትችላለች፡፡
ሕጻናት ለስድስት ወር ውሀን ጨምሮ ያለምንም ተጨማሪ ምግብ የእና ቸውን ጡት ብቻ ነው መመገብ ያለባቸው፡፡ የእናት ጡት በቂ ውሀ ስላለው በበረሀ ያሉም እንኩዋን ቢሆኑ በዚህ ምንም ስጋት ሊኖራቸው አይገባም፡፡ እናቶች በስራ ምክንያት እንኩዋን ቀኑን ሙሉ ማጥባት ባይችሉ ጡ ቸውን እያለቡ በንጽህና ይዘው ልጆቻቸውን ሊያጠጡ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን አልበወ በጡጡ የሚያስቀምጡ ከሆነ ትክክል አይደለም፡፡ ጡጦ በምንም ምክንያት ለልጆች መሰጠት የለበትም፡፡ የጡት አጠባብና የጡጦ አጠባብ  የተለያዩ ነገሮች ናቸው፡፡ ሕጻኑ ጡጦን በቀጥ  በመሳብ ወተት የሚያገኝ ሲሆን ጡትን ግን በምላሱ ላንቃው ላይ በመጨመቅ ጭምር ነው ወተት የሚያገኘው፡፡ ሕጻኑ ጡጦን አንዴ ከጀመረ በምንም አይነት ወደጡት መመለስ አይፈልግም፡፡ ምክንያቱም ጡጦን በቀላሉ በመሳብ ወተት እንዲያገኝ ስለሚያስችለው ነው፡፡ ጡጦ በምንም ምክንያት በጊዜያዊነት እንኩዋን መጀመር የለበትም፡፡
ሕጻናት ከስድስት ወር በሁዋላ በአ ባቢው ያለውን ወላጆች የሚመገቡትን መመገብ ይችላል፡፡ ነገር ግን ምግቡ ሕጻናት ሊበሉ በሚችሉበት ሁኔ  ተስተ ክሎ ተዘጋጅቶ መሰጠት ለበት፡፡ ለምሳሌ ላላ ያለ ገንፎ ለማዘጋጀት የተለያዩ ምግቦችን በማደባለቅ ...አተር ፣ሽንብራ፣ ስንዱ፣ ጤፍ ፣በቆሎ የመሳሰሉትን በማደባለቅ ከአንዱ የሌለውን በሌላው በማሟላት የተሟላ ነገር በማዘጋጀት ሕጻኑ እንዲመገብ ማድረግ ጠቃሚ ነው፡፡ነገር ግን የጡት ወተቱን የማጥባት ሁኔ ው መቀጠል አለበት፡፡ ሕጻኑ 50% ሀምሳ በመቶ የሚሆነውን ሓይል ሊያገኝ የሚችለው ከጡት ወተት ስለሆነ ቢቻል እስከሁለት አመት ድረስ ማጥባት ይመከራል፡፡ ያ ካልተቻለ ደግሞ ከስድስት ወር በሁዋላ በከብት ወተት በመሳሰለው በመተ ት ወተት እንዳያጡ ማድረግ ይገባል፡፡

ይቀጥላል

***************************

ውፍረት በአብዛኛው ከሕጻንነት ይጀምራል፡፡
                                                                ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ

ሕጻናትና አመጋገባቸውን በተመለከተ በዛሬው እትም እንግዳችን የሁለት ልጆች እናት ነች፡፡ ልምዱዋ እንዴት እንደነበር እንደሚከተለው ገልጻለች፡፡
     *        *            *
፵ እኔ እድሜዬ ሰላሳ ሶስት አመት ነው፡፡ ስራ አለኝ ፡፡ የትምህርት ደረጃዬ በነርሲንግ ዲፕሎማ በሶሲዮሎጂ ቢኤ ዲግሪ ያለኝ ሲሆን በዴቨሎፕመንት ማናጅመንት ሁለተኛ ዲግሪዬን እየሰራሁ ነው፡፡ ልጆቼ ሁለት ሲሆኑ የመጀመሪያዋ የሰባት አመት ሁለተኛው ልጄ ደግሞ ሶስት አመቱ ነው፡፡
ጡት ማጥባት ለእኔ የምኮራበት ወይንም በትክክል ሰርቸዋለሁ የምለው አይደለም፡፡ ምክንያቱም ሁለቱንም ልጆቼን ከአራት ወር በላይ አላጠባሁዋቸውም፡፡ የመጀመሪያዋን ልጄን ጡት ላለማጥባ  ዋነኛው ምክንያት የስራዬ ሁኔ  ነበር፡፡ ከወለድኩኝ ከአራት ወር በሁዋላ ወደስራዬ መመለስ ነበረብኝ፡፡ መስሪያ ቤ ና ቤ  በጣም የተራራቀ ስለነበር በምሳ ሰአት ተመልሶ ማጥባት ጠዋት ረፈድ አድርጎ መውጣት ማ  በግዜ መግባት አልችልም ነበር፡፡ በሁለተኛወ ልጄ ላይ ግን የእራሴ ጥፋት እንጂ ከስራዬ ጋር በተያያዘ ጡት ማጥባት የማያስችል ምንም ችግር አልነበረብኝም፡፡ ሁል ጊዜ የሚገርመኝ ነገር እውቀ ን በተግባር ላይ ማዋል አለመቻሌ ነው፡፡ ጡት ለማጥባት ወይንም የጡት ወተቱን ለማምረት ብዙ መብላት ምንም ፋይዳ እንደሌለው እያወቅሁ ነገር ግን እወፍራለሁ ብዙ አልበላም የሚሉ ምክንያቶች ለራሴ እየሰጠሁ ልጆቼን አላጠባሁዋቸውም፡፡ ልክ እኔ ማጥባ ን ስቀንስ ጡቱም ወተቱን ይቀንሳል፡፡ ስለዚህ ቶሎ ጡጦ ወደመስጠት አዘነብላለሁ፡፡ በእርግጥ በመጀመሪያው ትምህር  የነርሲንግ ባለሙያ ስለሆንኩኝ የመጀመሪያውን እንገር የሚባለውን ወተት እንደተለመደው እንገር ነው ብዬ አላፈሰስኩትም፡፡ ሁለቱንም ልጆቼን አጥብቻለሁ፡፡ በአጠባብ ደረጃ ጡቱ በመጀመሪያው ደረጃ ሲጠባ የሚገኘው ውሀ እንደሆነም ስለማውቅ ለልጁ በመጀመሪ የሰጠሁትን ጡት ጥንፍፍ አድርጎ እስኪጠቀም ድረስ ጡቱን አልነጥቅም ፡፡ በዚህ በኩል ለዚያቹ አራት ወር እድሜም ቢሆን ልጆቼን አልጎዳሁዋቸውም፡፡
ጡት በማጥባበት ወቅት አንዱ የእኔ ችግር የነበረውና የማልረሳው ነገር የጡቱ ቁስለት ነው፡፡ እኔ እንዲያውም ጡት ለልጁ በማጉረስ ረገድ በተለይም በመጀመሪያው ወር ላይ ጡት በመስጠቱ ረገድ የእኔ ተሳትፎ የለም ማለት ይቻላል፡፡ ቤተሰብ በተለይም እና  ጡቱን ለልጁ ስትሰጥ እኔ የአልጋዬን እራስጌ ይዤ መጮህ ነበር ስራዬ ፡፡ ለዚህ የሚረዳ ብለው ዶክተሩ የሰጡት ማብራሪያ የጡቱን ጫፍ እስከ ጥቁር ክቡ ወይንም ዙሪያው ጭምር አብሮ መስጠትን እኔ ስለማላውቅም ተግባራዊ አላደረግሁም፡፡ እና ወደፊት ለሚወልዱ ሴቶች ይህንን ተግባራዊ ቢያደርጉ በእኔ የደረሰው ያ የሚያስመርር የጡት ቁስለት ይቀርላቸዋል፡፡
ጡት ወተት ለሕጻናት በጣም ወሳኝ ነገር ነው፡፡ ምንም እንኩዋን አኔ ባልፈጽመውም ለሚወልዱ ሁሉ የምመክረው ልጆቻቸውን ጡት እንዲያጠቡ ነው፡፡ ምክንያቱም ምንም ውጣ ውረድ የሌለው ወፈረ ቀጠነ የማይባል በተፈጥሮ ተመጣጥኖ የተሰራ ጽዳት ይጎድለዋል በሽ  ያመጣል የማይባል ነገር ስለሆነና የተማሩም ሆኑ ያልተማሩ ሴቶች ሁሉም እኩል ለልጆቻቸወ ሊመግቡት የሚችሉት ተፈጥሮአዊ ነገር በመሆኑ ጡትን ማጥባት ለማንኛዋም እናት ቀላሉና ጠቃሚው ዘዴ ነው፡፡ ልጆቹ ደግሞ ጡት በመጥባ ቸው ምክንያት ለተለያዩ በሽ ዎች ያልተጋለጡ እንደሚሆኑ አረጋግጫለሁ፡፡
እኔ ዛሬ ልጆቼ በተለያዩ ምክንያቶች ጉንፋን ለመሳሰሉት በሽ ዎች በጣም የተጋለጡ ናቸው፡፡ ስለዚህ ልጆቹን ከበሽ  ለመከላከል ስል የተለያዩ ምግቦችን መስጠት በተቻለ መጠን ጽዳትን መጠበቅ ጉንፋን ካለበት አ ባቢ ማራቅ የመሳሰሉት የእለት ተእለት ስራዎቼ ሆነዋል፡፡ ጡት ቢጠቡ ኖሮ ግን በቀላሉ ለእነዚህ በሽ ዎች ስለማይጋለጡ ብዙም አድ ሚ ነገር አይከሰትብኝም ነበር፡፡ በየጊዜው ከህጻናት ክሊኒክ ደጅ አልጠፋም፡፡ በሽ ውን ለመከላከል የሚረዱ ምግቦችንና የተለያዩ ደጋፊ ነገሮችን ለማሟላት ስል ወጪዬም ከፍተኛ ነው፡፡ ምንጊዜም የማዝንበት ነገር በመጀመሪያው ትምህር  በመጠኑም ቢሆን ወደ ሕክምናወ ያዘነበልኩ ቢሆንም ልቼን ጡት ለማጥባት ስላልተጠቀምኩበት ልክ አይደለሁም በማለት እራሴን እወቅሳለሁ፡፡፶
    *          *            *
ባለፈው ሳምንት በጡት ማጥባት ዙሪያ የተለያዩ ማብራሪያዎች የሰጡን ዶክተር መንግስቱ  ፈሰ በዚህ እትም ጡት ስለመጥባት ብቻ ሳይሆን የህጻናትን አመጋገብ በሚመለከትም መሰረ ዊ የሆኑ ነጥቦችን ለአምዱ አ ፍለዋል፡፡  *      *            *
ሕጻናት እስከ ስድስት ወር ድረስ ከጡት ወተት በስተቀር ውሀን ጨምሮ ሌላ ምንም ሊሰጣቸው አይገባም ፡፡ከስድስት ወር በሁዋላ ግን እንደአ ባቢያቸወ ማለትም ወላጆቻቸው ለምግብነት የሚጠቀሙበትን ማንኛውንም ምግብ በተጨማሪነት መውሰድ ይኖርባቸዋል፡፡ ለምሳሌ ጤፍ ፣በቆሎ ፣ስንዴ ፣ገብስ ...፺ወዘተ፻እንዲሁም ቅጠላቅጠሎችን ፍራፍሬዎችን እንደ ካሮት፣ ድንች፣ የመሳሰሉትን ሁሉ ጨምሮ መመገብ ተገቢ ነው፡፡ ትልቁ ነገር ግን አሰራሩ ለልጆች በሚመች መንገድ መሆን አለበት፡፡ ሳይንሱ ካርቦሀይድሬት ፣ፕሮቲን ፣ሚኒራል ፣ቫይ ሚን በሚል የከፋፈላቸውን ጠቃሚ ነገሮች በሙሉ ሊያገኙ በሚችሉበት መንገድ የምግብ አይነቶቹን አቀላቅሎ በመስራት ላላ ባለ የገንፎ መልክ ወይንም ለአጥሚት በሚሆን መንገድ አዘጋጅቶ ለሕጻናቱ መስጠት ይገባል፡፡
ሌላው ለሕጻናቱ በጣም አስፈላጊ የሆነው ንጥረ ነገር አዮዲን ነው፡፡ አዮዲን ለአእምሮ እድገት ወሳኝ የሆነ ንጥረ ነገር ነው፡፡በአመጋገብ ውስጥ የአዮዲን እጥረት ካጋጠመ የእንቅርት በሽ  የሚከሰት ሲሆን ከዚህም በላይ በተለይም ሕጻናትን ለአእምሮ ዝግመት እና ለነርቭ በሽ  ያጋልጣቸዋል፡፡ አዮዲን  ብዙ ጊዜ ተፈጥሮአዊ ከሆኑ ምግቦች የሚገኝ ቢሆንም ነገር ግን በቂ አይሆንም፡፡ ስለዚህም አዮዲንን በተጨማሪነት ማግኘት ያስፈልጋል፡፡ አዮዲንን በጨው ውስጥ በቀላሉ ማግኘት ይቻላል፡፡ በእርግጥ አዮዲን የሌለው ጨውም ይኖራል፡፡ አዮዲን ያለውን ጨው በመጠቀሙ ረገድ በሚበስለወ ምግብ ውስጥ ጨውን አስቀድሞ በመጨመር ምግቡ ሲበስል አብሮ ሲንተከተክ ከዋለ አዮዲኑ ስለሚጠፋ ይህ ትክክለኛወ ዘዴ አይደለም፡፡ ቢቻል ምግቡ ተሰርቶ ሲቀርብ ካልሆነም ከእሳት ላይ ሲወጣ ጨው ቢጨመር አዮዲኑ ሳይጠፋ መመገብ ያስችላል ፡፡ ባጠቃላይም ሕጻናቱ አዮዲን ከምግባቸው ጋር እንዲያገኙ ማድረግ ጤነኛነትን ያላብሳቸዋል ፡፡
ሰዎች በሕይወ ቸው ዘመናቸው የሚቸገሩበት የመወፈር ሁኔ  የሚጀምረው  በአብዛኛው ከሕጻንነት እድሜያቸው ነው፡፡ ጥናቶች እንደሚያስረዱት በሕጻንነት እድሜ የሚኖረው የአመጋገብ ሁኔ  ለውፍረት ያጋልጣል፡፡ ለምሳሌ የጡት ወተት የሚመገቡ ልጆች ጡቱ ሲሰጣቸው የተመረተውን ወተት ጨርሰው ስለሚጠቡ ጡቱ ባዶ ስለሚሆን መጥባ ቸውን ያቆማሉ፡፡ ነገር ግን በጡጦ የሚመገቡ ከሆነ ወተቱ ሲያልቅ ወዲያው ተጨማሪ ወተት ሊሞላ ስለሚችል ያለምንም ገደብ መጠጣት ስለሚችሉ የምግብ ፍላጎ ቸውን በእጥፍ እየጨመረው ይሄዳል፡፡ ስለዚህ ሌላም ምግብ ሲሰጣቸው መጠኑ በዚያው ልክ እያደገ ስለሚሄድ የመወፈር እድላቸው ከፍተኛ ይሆናል፡፡ ሕጻናቱ በሰባት እና ስምንት ወር እድሜያቸው ከአንድ አመት በላይ በሚሆን እድሜ ክብደ ቸው ይለ ል ፡፡ በሕጻንነት እድሜ በተለይም ለተለያዩ በርገር፣ ጣፋጭ፣ ስብነት ያለቸውን ምግቦችን የመሳሰሉትን ከልክ በላይ መውሰድ  ወደፊት በሚኖረወ ሕይወት ለውፍረትና ለተለያዩ ሕመሞች ሊያጋልጥ ስለሚችል መወገድ የሚገባው ልምድ ነው፡፡

አንዲት እናት ጡት በም ጠባበት ወቅት ለእራስዋ ተጨማሪ ምግቦችን መመገብ ይኖርባ ል፡፡ ያ ማለት ግን የወተት ምርቱ እንዲጨምር ሳይሆን የእርስዋ ሰውነት እንዳይጎዳ ነው፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ጊዜ የሚሰማወ ነገር ምግብ ስለማልመገብ ወተት የለኝም የሚል ነገር አለ፡፡ መ ወቅ ያለበት ነገር ግን ወተቱ ሊኖር የሚችለው ሕጻኑ ስለሚጠባው እንጂ እናትየው ምግብ ስለበላች አለመሆኑን ነው፡፡ የጡት ወተት እንዲመረት እናትየው ዘና ያለች መሆን አለባት ፡፡ እናትየው የምትጨነቅ ከሆነ የጡት ወተቱ እየደረቀ ነው የሚሄደው፡፡ በአገራችን ባህል አንዲት እናት ወተት እንዲኖራት ቆሎ መብላት በዚያ ላይ ጠላ የመሳሰሉትን መጠጦች መጠጣት የመሳሰለው ልምድ አለ፡፡ ያ በእርግጥ ጥሩ ጎን አለው፡፡ በልማዱ እንደሚ መነው ግን ወተቱ በሚወሰደው ምግብ ምክንያት ባይመረትም ነገር ግን እናትየው ቆሎ በመብላቷ አንድ የምግብ አይነት ወስዳለች ስለዚህ ለእራስዋ አትጎዳም ማለት ነው ፡፡ ጠላ የመሳሰሉትን መጠጦች በመውሰዱዋ ደግሞ ከጭንቀት ትገላገላለች፡፡ ስለዚህም ዘና ስለምትል ጡትዋ ወተት እንደልብ ሊያመርት ይችላል፡፡

ጡትን የማጥባት ሁኔ  ከጤና ጋር በተያያዘ አንዳንድ ሊተኮርባቸወ የሚገባቸወ ነገሮች አሉ፡፡ እናትየው ለምሳሌ የሳንባ በሽ  ወይንም ቲቪ ቢይዛት ልጁዋን በም ጠባ ጊዜ ልትተነፍስበት ስለምትችል በሽ ው እንዳይተላለፍበት መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ እንደ ጡት ካንሰር የመሳሰሉት ሕመሞች በእናትየው ላይ ቢከሰቱ ቁስለት የመሳሰሉት ነገሮች ስለሚኖሩ ወደ ሐኪም ዘንድ መሄድና መመ ከር ተገቢ ይሆናል፡፡ ከኤችአይቪ ኤይድስ ጋር በተያያዘ ግን እናቶች የሐኪም ምክር ሳይለያቸው ጡ ቸውን ማጥባት እንደሚችሉ ተረጋግጦአል፡፡ከዚህ ውጭ ግን ብዙሀኑ እናቶች ጤነኞች ስለሆኑ በተገቢው መንገድ ልጆቻቸውን ጡት በማጥባት ጤነኛ የሆኑ ልጆችን ማሳደግ ይጠበቅባቸዋል ፡፡ እናትየው የጡት ወተት ማጥባት እንደማትችል በሕክምና ባለሙያ ከተረጋገጠ ግን በከፍተኛ ጥንቃቄና ዝግጁነት በፋብሪካ የተዘጋጀ ወይንም የከብት ወተትን ለልጆች መመገብ ግድ ይላል፡፡

 ****************************************************

  ... ወሲብ በመፈጸሙ ረገድ ...የሚጎድላት ነገር የለም፡፡
                                                ፀሐይ ተፈረደኝ... ከኢሶግ

በዚህ እትም ለንባብ ያልነው ከማህጸን ጋር በተያያዘ የሚከሰቱትን የተለያዩ እጢዎች አፈጣጠርና አወጋገዳቸውን ነው፡፡ እነዚህን ነጥቦች በሚመለከት ወደ ባለሙያ ያመራነውም ሁለት የተለያዩ ጥያቁዎችን መሰረት በማድረግ ነው፡፡ የመጀመሪያው ጥያቄ የሚከተለው ነው፡፡
፵ለማህጽንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር እንደምን ሰነበ ችሁ እኔ አንድ የማዝንበት ገጠመኝ ስላለኝ ይህንን ደብዳቤ ላደርሳችሁ ተገደድኩ፡፡ ባለቤ  እኔን ለማግባት በነበረወ ፍላጎት በቤተሰብ ውስጥ ከፍተኛ አለመግባባት ተፈጥሮ የነበረ ቢሆንም እሱዋን ካላገባሁ ሞቼ እገኛለሁ በማለቱ ምክንያት ተዳርኩለት፡፡ እኔ በእርግጥ ልጅነት ስለነበረኝ ብዙም ፍቅር ወይንም ጥላቻ አልነበረኝም፡፡ ከተጋባን በሁዋላ ግን ልጅ መውለድ ቀጣዩ የሚናፈቅ ነገር ቢሆንም ቢጠበቅ ቢጠበቅ ግን እውን ሊሆን አልቻለም፡፡ አገባለሁ አ ገባም የሚለው ነገር አበቃና አሁን ደግሞ ሌላ  ሪክ ቀጠለ፡፡ የእርሱ ቤተሰቦች ልጅ የማትወልድ ሴት ናት እንዴ ያገባሀት እያሉ ጥያቄ ማንሳት ጀመሩ፡፡ እሱም ይህንኑ ጥያቄአቸውን ያስተጋባ ጀመር፡፡ እግዚአብሄር ካልሰጠን እኔ  ድያ ምን ማድረግ እችላለሁ የሚል ሆነ መልሴ፡፡ በሁዋልም የተለያዩ የጤና መጉዋደል ስሜቶች ስለነበሩኝ ወደሐኪም ቤት ስሄድ ከማህጸኔ ውስጥ እጢ እንዳለና ካልወጣም ልጅ ማርገዝ እንደማልችል ተነገረኝ፡፡ እኔና ባለቤ  ከተጋባን ገና ሶስት አመት ገደማ ሲሆነን በስምምነት እጢው ከማህጸኔ ውስጥ እንዲወጣ እና ልጅ ማግኘት እንድንችል በመናፈቅ ከሆስፒ ል ገባሁ፡፡ ከዚያም  ክሜ ስወጣ ባለቤ  የወሰደኝ ወደ እና  ቤት ነበር፡፡ ለምንድነው ወደቤ ችን የማልሄደው ስለው ስለው እንድ ርፊ... በደንብ እንዲያስ ምሙሽ ነው የሚል ነበር መልሱ፡፡ ወደ አስራ አምስት ቀን ገደማ መለስ ቀለስ አለና ከዚያ በሁዋላ ግንኙነቱ በስልክ ሆነ፡፡ ከአንድ ወር በሁዋላ የስልኩ ግንኙነትም ቀረ፡፡ እና  ቤት ወደ ሶስት ወር እንደሆነኝ በቃኝ አሁን ወደበ  እሄዳለሁ ስል ቤተሰቦቼም ተከላከሉኝ፡፡ ምንድነው ምክንያቱ ብዬ ብጠይቅ ማህጸንሽ ተከፍቶ ሲ ይ ከእጢው ባሸገርም ሌላ ችግር ስለተገኘ ማህጸንሻን በጠቅላላው ነው ሐኪሞቹ ያወጡት የሚል መልስ ተሰጠኝ፡፡ ለጊዜው ብደነግጥና በጣም ባዝንም ወደሐኪም ቤቱ ተመልሼ ስለሚቀጥለው ሁኔ ዬ ስጠይቅ ...በቃ ልጅ አትወልጅም እንጂ ሌላ ምንም ችግር የለም ብለው አስረዱኝ፡፡ ባለበ ን የአንተ ፍላጎት ልጅ ማግኘት ብቻ ነውን ብዬ ብጠይቀው አይ...አይደለም ...ነገር  ግን ከእንግዲህ በሁዋላ በቃ ...ሴት ስላይደለሽ አልፈልግሽም ብሎ ትዳሩን በቃኝ አለ፡፡ ይህ ግን ለብዙዎች ግልጽ መሆን ስለሚገባወ እባ ችሁ ባለሙያ አነጋግሩ፡፡ ፶
                                                       እስከዳር ተፈራ፺ከቦሌ፻
*        *            *            *

ሁለተኛውን ጥያቄ በአ ል ያቀረበችልን እንግዳ ጠየም ያለች ቁመናዋ የሚያምር ቦርጭ የሚባል ነገር ጨርሶውኑ የሌላት ባጠቃላይም ጥሩ ቁመና ያላት ነች፡፡ ፵አሁን እንዲህ የም ምሪ ነሽ የሚለውን አስተያየት ስሰማ በጣም ነወ የሚገርመኝ፶ አለች፡፡ ለምን?...የኛ ጥያቄ ነበር፡፡፵ እኔ ከአንድ አመት በፊት እጅግ የማስጠላ እንዲያውም ድርስ ማለትም የዘጠኝ ወር እርጉዝ የምመስል ሴት ነበርኩ፡፡ እየዋለ እያደረ እንዲያውም ሕመም ይሰማኝ ጀመር፡፡ በሁዋላም ወደሐኪም ቤት ስሄድ በከፍተኛ ደረጃ ያደገ እጢ በማህጸኔ ውስጥ እንዳለና በኦፕራሲዮን መወገድ እንዳለበት ተነገረኝ፡፡ እኔም በጣም ነበር ያዘንኩት፡፡ ተመልሼ ሰው ሆኜ ቆሜ እሄዳለሁ የሚል እምነት አልነበረኝም፡፡ ኦፕራሲዮን ስደረግ ግን ወደ አስራ አምስት ኪሎ የሚደርስ እጢ ነበር የተወገደልኝ፡፡ ያንን ያደረጉልኝን ሐኪም እንደገና እንደፈጠሩኝ ነው የምቆጥራቸው፡፡ለመሆኑ ሴቶቹ እንደዚህ የሰውን ሰውነት ቅርጽ እስከማበላሸት የሚደርስ እጢ በማህጸናቸው ውስጥ ሊፈጠርባቸው እንደሚችል ያውቁ ይሆን? በተለይም በገጠር አ ባቢ ወይንም የህክምና ተቋም በሌለበት አ ባቢ ያሉ ሴቶች የማይወለድ ልጅ አርግዘዋል እየተባሉ ስንቶቹ ይሆኑ እጢውን እንደተሸከሙት ለህልፈት የሚዳረጉ? እባ ችሁ ይህንን ሴቶቹ እንዲያውቁት ብ ደርጉት ጥሩ ነው የሚል ጥቆማ ልሰጣችሁ እወዳለሁ፡፡፶
                                          አልማዝ  ይሌ ፺ከ ዛንቺስ፻
*        *            *            *
                    
ቀደም ሲል ያነበባችሁዋቸውን መልእክቶች መሰረት በማድረግ በማህጽን አ ባቢ ስለሚፈጠሩ እጢዎችና ስለሚያደርሱት ጉዳት እንዲሁም በምን መልክ ሊወገዱ እንደሚችሉ የሚነግሩን ባለሙያ ዶክተር መብራቱ ጀምበር ይባላሉ፡፡ ዶ/ር መብራቱ ጀምበር በከዲስኮ ሆስ  ል የማህጸንና ጽንስ ሕክምና እስፔሻሊስት ናቸው ፡፡
*        *            *            *
ኢሶግ/ የማህጸን እጢ አፈጣጠር ምን ይመስላል?
ዶ/ር    የእጢ አይነቶች ብዙ ናቸው፡፡ ነገር ግን በአብዛኛው        ,        ፋብሮይድ ወይንም ማዮማ የሚባለው ነው የሚከሰተው፡፡ የማህጸን እጢ ሲባል ፺            )ኦቫሪያን ሲስት ማለትም የእንቁላል እጢ የሚባልም አለ፡፡ ባጠቃላይም ጠጣር እጢና ውሀ የቋጠረ እጢ ተብሎ ሊለይ ይቻላል፡፡  የማህጸን እጢ የሚባሉት የሚበቅሉበት ቦ  እንቁላሉ ላይ አለበለዚያም ዋናው ማህጸን ውስጥ ወይንም ከውጭ እንዲሁም ከማህጸን በሩ አ ባቢ ሊሆን ይችላል፡፡ በማህጸን ውስጥም ሆነ ውጭ የሚበቅሉት እጢዎች በኪሎ ከበድ ሊሉ ይችላሉ፡፡ ለምሳሌ ፋይብሮይድ ወይንም ማዮማ ፺9-15፻ከዘጠኝ እስከ አስራ አምስት ኪሎ ግራም ገደማ እስኪመዝን ሊያድግ ሲችል የእንቁላል እጢ ግን እስከ ፺30፻ሰላሳ ኪሎ ግራም ድረስ ሊያድግ ይችላል፡፡ እነዚህ የእጢ አይነቶች እርግዝናን የሚከለክሉም የማይከለክሉም አሉ፡፡ እርግዝና የሚከለክሉት በማህጸኑ ግድግዳ ውስጥ የሚፈጠሩት ሲሆኑ እነዚህም ተግባራቸው የሴቷ እንቁላልና የወንዱ ዘር እንዳይገናኝ ወይንም ተፈጥሮ ትክክለኛው እድገቱ እንዳይከናወን ማገድ ነው፡፡ እነዚህ እጢዎች ኪሎአቸው እያደገ በሄደ ቁጥር እጢው ያለባት ሴት ጤና በእጅጉ እየ ወከ ይመጣል፡፡  
ኢሶግ/የማህጸን እጢ ማህጸኑ እስኪወጣ የሚያደርሰው በምን ሁኔ  ላይ ሲገኝ ነው?
ዶ/ር    ማህጸን በኦፕራሲዮን እንዲወገድ ወይንም እንዲወጣ ከሚያደርጉት የእጢ አይነቶች ለምሳሌ አንዱ ፋብሮይድ ወይንም ማዮማ የሚባለው ነው፡፡ ፋብሮይድ ወይንም ማዮማ በአፈጣጠሩ ያያዘው ቦ  ፣ስፋቱ፣ ትልቅነቱ ወይንም መጠኑ ሁሉ ይወስነዋል፡፡ የሚበቅልበት ቦ ም ከማህጸን ከውስጠኛወ ግድግዳ ላይ ሊሆን ይችላል፡፡ ፋብሮይድ ዋና አ ሉ ወይንም ከውጭ አ ሉ ሆድ ውስጥም ሊበቅል ይችላል፡፡ በእርግጥ ከማህጸን ውጭ ሆኖ በሆድ ውስጥ ያለው ብዙም ጉዳት አያመጣም፡፡ ከማህጸን ውስጥ ግድግዳወ ላይ ያለው እጢ ግን የወር አበባ ያበዛል፡፡ የደም ማነስም ያስከትላል፡፡ የደም አፈሳሰሱና ሕመሙ ሁሉ ከበድ ይላል፡፡ ከማህጸን ውስጥ ግድግዳ ላይ ያለው እጢ ልክ ሉፕ እንደሚባለው የወሊድ መከላከያ እርግዝናውንም ይከላከላል፡፡ስለዚህ ማህጸኑ እንዲወጣ ወይንም እንዲቆይ የሚለውን ለመወሰን የዚህ እጢ ያለበት ሁኔ  ይወስነዋል፡፡
ኢሶግ/ እጢው በኦፕራሲዮን ከወጣ በሁዋላ እራሱን ይተ ል?
ዶ/ር    እጢው እራሱን ይተ ል አይተ ም የሚባለውን ነገር ለማስረዳት ከሚኖረው አስቸጋሪ ሁኔ  የሚመጣ ነው፡፡ ለምሳሌ ፋብሮይድ ወይንም ማዮማን ስንመለከት በኦፕራሲዮን ወቅት ያሉት እጢዎች በሙሉ ከማህጸን ተለቅመው ከወጡ በሁዋላ ሌሎች ለጊዜው የማይ ዩ ነገር ግን ቀድሞውኑም ያቆጠቆጡት ያድጋሉ እንጂ በኦፕራሲዮን የተወገደው  እጢ እራሱ ተመልሶ አያድግም ፡፡
ኢሶግ/ የማህጸን እጢ የተፈጠረባት ሴት የማርገዝ እድሉዋ እስከምን ድረስ ነው ?
ዶ/ር  አንዲት ሴት እርግዝናን ከማቀዱዋ በፊት ማድረግ ያለባት የጤና ምርመራዋን ማ ሄድ ነው፡፡ለእጢም ብቻ ሳይሆን ለማንኛውም የውስጥ ደዌ ሕመም ጭምር ከእርግዝና በፊት ቅድመ ምርመራ ማ ሄድ እርግዝናውን ጤናማ በሆነ ሁኔ  ለመቀጠል ያስችላል፡፡ የማህጸን እጢንም በተመለከተ ሴትየዋ ከማርገዝዋ አስቀድሞ ምርመራ አድርጋ ከሆነ እጢው ያለበት ሁኔ  እንዲ ይ ይረዳል፡፡ ፋብሮይድ ወይንም ማዮማ በማህጸንዋ ውስጥ ያለባት ሴት በተቻለ መጠን ያደጉት እጢዎች ተለቅመው ወጥተው እርግዝናዋን እንድትቀጥል ይደረጋል፡፡ ምክንያቱም የተፈጠሩት እጢዎች ከወጡ በሁዋላ ሌሎቹ ማለትም ያቆጠቆጡት እጢዎች እስኪያድጉ ድረስ ጊዜ ስለሚሰጥ ያለ ችግር ልጅን ለማግኘት ያስችላል፡፡ በእርግጥ ሁሉም እጢ ያለባቸው ሴቶች እጢው ተወግዶ ልጅ ለመውለድ ይችላሉ ማለት አይደለም፡፡ ነገር ግን እጢው እና የማህጸኑ የጤነኛነት ሁኔ  ያለበት ደረጃ ሁኔ ውን ይወስነዋል፡፡ ለማንኛውም ማንኛዋም ሴት ልጅ ለመውለድ ስትፈልግ ከማርገዝዋ አስkÉV ÖpLL U`S^ ”ɁÅ`Ó ÃSŸ^M::

›=fÓ/ TIç” uÖ=ኢሶግ/ ማህጸን በእጢም ሆነ በሌላ ሕመም ምክንያት ሲወገድ ከሴትነት ተፈጥሮ ጋር ያለው
ግንኙነት ምንድነው?
ዶ/ር  በዚህ ጉዳይ ላይ አንድ የማዝንበትና ሁልግዜ የማስ ውሰው ነገር አለ፡፡ በአንድ አጋጣሚ
ማህጸኑዋ የተጎዳ ሴትን ኦፕራሲዮን አድርጌ ነበር፡፡ ይህች ሴት ኦፕራሲዮን ፺ቀዶ ሕክምና ባይደረግላት ኖሮ ምናልባትም ልትሞት ትችል ስለነበር ሴትየዋን ለማትረፍ ሲባል ነው  እርምጃው የተወሰደው፡፡ ነገር ግን ከሕክምናው በሁዋላ ባልየው የወሰደው እርምጃ ትዳሩን ማቋረጥ ነበር፡፡ በጣም ነው ያዘንኩት፡፡ ሁሉም ሰው ይሔንን ሊረዳውና ሊያውቀው ይገባል፡፡ የማህጸን ዋና አ ል ወይንም ውስጡ በኦፕረሲዮን፺ቀዶ ሕክምና፻ ተወገደ ማለት የውጭው አ ል ወይንም የወንድና የሴት ግንኙነት እንዲኖር የሚፈቅደው ክፍል አብሮ ተወገደ ማለት አይደለም ፡፡ በእርግጥ ሴትየዋ ልጅ መውለድ አትችልም ፡፡ ከዚህ ሌላ ግን ሴት በመሆኑ ረገድ ወይንም ወሲብ በመፈጸሙ ረገድ ምንም የሚጎድላት ነገር የለም፡፡

*********************************

ትዳር ለመመስረት... መጠናናት...እስከምን ድረስ?
                                          
ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ
ትዳር ለመመስረት መጠናናት ተገቢ ቢሆንም ደረጃው ግን እስከምንድረስ ነው ለሚለው  ሪክዋን ል  ፍለን የወደደችው በቅጽል ስሟ ሳቂ  ከኮተቤ ነች፡፡ ሳቂ  ከልጅነት አሁን እስከአለችበት ድረስ ትዳርን በመመስረቱ ረገድ ያሳለፈችውን ልምዱዋን ለአንባቢ ይድረስልኝ በማለት በጽሁፍ አድርሳናለች፡፡


*        *            *            *
እኔ ተወልጄ ያደግሁት በአዲስ አበባ ቡራዩ አ ባቢ ነው፡፡ እናም እኔ ብዙም የከተማ ብዙም የገጠር ልጅ አይደለሁም ማለት እችላለሁ፡፡ ከሁለቱም ትንሽ ትንሽ በመያዝ መሀል ላይ ሆኜ ነው ያደግሁት፡፡ በእድሜዬ ገና ከፍ ማለት ስጀምርም ለትዳር የሚፈልጉኝ ሰዎች ጥያቄያቸውን ለቤተሰብ ያቀርቡ እንደነበርም አስ ውሳለሁ፡፡ ትዳርን በሚመለከት አንድ የማልረሳው ገጠመኝ አለኝ፡፡ ገና የሰባተኝ ክፍል ተማሪ ሆኜ አንድ በእድሜያቸው ትልቅ የሆኑ  በሙያቸው ዳኛ ይሁኑ ጠበቃ ብቻ ከሁለቱ በአንዱ ሙያ የተሰማሩ ሰው ለትዳር እንደሚፈልጉኝ ገልጸው ሽማግሌ ይል ሉ፡፡ አባ ም በጣም ተናድዶ ምንስ ቢሆን እንዴት ከእኔ ከአባቷ በእድሜ ለሚበልጡ ሰው ልጄን እድራለሁ በማለት እምቢ ይላል፡፡ አባ  ለትዳር የሚፈልጉኝ ሰዎች ጥያቄ ሲያቀርቡ እንደአመጣጣቸው እየመለሰ ትምህር ን እንድማር ያበረ  ኝ ነበር፡፡ እና  ደግሞ በበኩሏ እምነቷና ስጋቷ ከአባ  የተለየ ነበር፡፡ ይህች ልጅ የደረሰች ነች... በሁዋላ ችግር እንዳይከሰት...ስትል አባ ም በበኩሉ ምንድነው የሚከሰተው ችግር ...?ልጅ እንዳትወልድ ማለትሽ ነው ...?እሱዋ ደህና ትሁን ትማር እንጂ የምትወልደውን ልጅ ለማሳደግ አ ንስም የሚል ነበር የአባ  መልስ፡፡ በዚህ በዚህ አባ ን በጣም እወደዋለሁ አከብረዋለሁ፡፡
የዚህ  ሪክ ባለቤት እኔ ሳቂ   ድያ የአባ ን ፍላጎት ጠንቅቄ በመረዳ  በትምህር  ጎበዝ እየሆንኩ ከደረጃ ደረጃ መሸጋገሬን ቀጠልኩ፡፡ ብዙ ጉዋደኞቼ አንዳንዶቹም በፈተና ሲወድቁ ሌሎቹ ደግሞ ሲዳሩ ... ብቻ በተለያዩ ምክንያቶች ከትምህር ቸወ ሲፈናቀሉ እኔ ግን የብሄራዊ ፈተናዬን በሚገባ አልፌ ወደ ዩኒቨርሲቲ ገባሁ፡፡ በጊዜው ይሰጥ የነበረውን የሶሻል ሳይንስ ትምህርትም ለመማር ቻልኩ፡፡ ዛሬ ከአንድ ዲግሪም አልፌ ሁለተኛ ዲግሪዬን ይዣለሁ፡፡ ሶስት ልጆችም አፍርቻለሁ፡፡ እራሴን ለማስተዳደር ተገቢውን አቅም አጎልብቻለሁ፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በመማር ላይ ሳለሁ ለጉዋደኝነት ይፈልጉኝ የነበሩ ሰዎች  በር   ነበሩ፡፡ ከተማሪው ጀምሮ እስከ አስተማሪው ድረስ ማለት ይቻላል በተለያዩ መንገዶች ፍላጎ ቸውን የሚገልጹ ነበሩ፡፡ እኔም ያ... ከግማሽ ገጠሬነት እና ግማሽ ከተሜነት ይዤው የወጣሁት ተደብቆ የነበረ ውበት አሁን ወደለየለት የከተማ አኑዋኑዋር ሲለወጥ ውበ  ቀላል እንደአልሆነ ነበር ከሴት ጉዋደኞቼም ይነገረኝ የነበረው፡፡ስለዚህ የወንዶቹን ጥያቄ በቀላሉ መመለስ አስቸግሮኝ ነበር፡፡ እኔ ግን ትዳርን በመመስረቱ ረገድ አባ  ይናገር የነበረውን ነገር ሙሉ ለሙሉ ተቀብዬ ልክ በዩኒቨርሲቲው የአንደኛ አመት ትምህር ን እንዳጠናቀቅሁ ነበር ከትምህር  ጎን ለጎን ለትዳር የሚሆነኝን ሰው ማጥናት የጀመርኩት፡፡ ለትዳር የሚሆንን ሰው ማጥናት ተገቢና ጠቃሚ መሆኑን ከአባ  ብቻ ሳይሆን እኔም በትምህርቱ አለም እያለሁ ካገላበጥኩዋቸው ሰነዶች እና ከተለያዩ ምንጮች ለመረዳት ችያለሁ፡፡
ትዳርን ከመመስረት በፊት የትዳር ተጉዋዳኙን ማንነት ማወቅና የሰመረ ኑሮን መመስረት በተመሰረተው ቤት ውeØ ŸT>•\ u?}cx‹ ËUa uÒ^ ¾T>Áð\ª†¨< MЋ ”Ç=G<U uG<K~U ¾ƒÇ` Ñ<ªÅ—V‹ uŸ<M LK< u?}cx‹ ”Ç=G<U Iw[}cw Ÿ²=ÁU c=ÁMõ K›Ñ` ßU` ÖnT> ¾J’< KMTƒU }Ñu=¨<” ›e}ªê* K=Áu[¡~ ¾T>‹K< ¾Iw[}cw ¡õKA‹” KTÓ–ƒ ¾T>[Ç u?}cv© }sU” ”ÅSõÖ` ÃqÖ^M:: eKJ’U Ÿ›Ç=e ›uv ¿’>y`c=+ uÑvG< Ÿ›”É ›Sƒ ËUa KƒÇ` ¾T>J’˜” c¨< uTØ“~ [ÑÉ ›e` ›Sƒ ÁIM ðωKG<::
’@ dm ³_ uÉT@ ¨Å cLd eU”ƒ ›Sƒ ¾Å[eŸ< eJ” ƒÇ` ¾Á´Ÿ<ƒ Ó” uGÁ ²Ö˜ ›S}? ’¨<:: MЋ” uS¨<KÆ [ÑÉU ”Ç=G< T^^p ¾T>vK¨<” ’Ñ` dMÖkU „KA „KA ’¨< ¾¨KÉŸ<ª†¨<:: U¡”Á~U uÉT@ Ÿõ MŸ< uG<ªL MЋ” KS¨<KÉ vew U“Mvƒ ¾Ö?“ ‹Ó` ÁKv†¨< MЋ ”ÇM¨MÉ eKcÒG< ’¨<::
KƒÇ` ¾T>J’˜” c¨< uTØ“~ [ÑÉ ¾‰MŸ<ƒ” ›É`Ñ@›KG< w LÑv¨< ¾¨c”Ÿ<ƒ”“ ÁÑvG<ƒ” ¾feƒ MЊ” ›vƒ KG<Kƒ ›Sƒ ÁIM ¾õp` Ñ<ªÅ—¨< J–@ ›dMôÁKG<:: Ÿõp[— Ò` u×U }Óvw}“M:: }ªÅ“MU:: u²=I [ÑÉ ÔÅK ¾UK¨< U”U ’Ñ` ›M’u[U:: ¾kÉV¨< õp[— G<ªLU ¾ƒÇ` Ñ<ªÅ— uƒUI`~ ›KU Ÿ’@ G<Kƒ ›Sƒ kÉV ’¨< ¿’>y`c=+¨<” ¾Kkk¨<:: uÉT@U ¨Å ›^ƒ ›መት ያህል ይበልጠኛል፡፡ ባለቤ  በጣም ቆንጆ ነው፡፡ በዚያ ላይ በጉዋደኝነ ችን ጊዜ ባህርይው በጣም የሚገርም ነበር፡፡ በቃ ...ሁሉም ነገር አንቺ እንዳልሽ የሚለኝ ሰው ነበር፡፡ እንዲያውም ከእርሱ በፊት የነበረኝን ጉዋደኛዬን ሳስበው አንዳንድ ጊዜ ፈጣሪ ሰዎችን በስንት አይነት መንገድ እንደሚፈጥር እስከሚገርመኝ ድረስ ነው የማነጻጽረው፡፡ የቀድሞው ጉዋደኛዬን ጥያቄዎች ለመመለስ እጅግ ነበር የምቸገረው፡፡ የት ነበርሽ? ከነማንጋር ዋልሽ ?ለምን ይሄንን ለበስሽ? እውሸትሽን ነው አትወጂኝም ...ሌላም ሌላም የማይሆኑ ጥያቄዎችን የሚያነሳና ሁልጊዜ የሚያስጨንቀኝ ሰው ነበር፡፡ ይኼኛወ ግን ምንም አይነት አስቸጋሪ ጥያቄ የማያነሳ ሁሉም ነገር በኔ ፈቃድ እንዲሆን የሚፈልግ በቀጠሮአችን ወቅት ያለምንም ችግር የሚገኝ ለእኔም የሚያስፈልገኝን ነገር በብቃት የሚያሟላ ሰው ነበር፡፡ ስለሆነም አሁን በትክክል የማገባውን ሰው ስላገኘሁ ትዳር መመስረት እችላለለሁ የሚለውን ሀሳቤን ለአባ  አቅርቤ ባለበ ም ባህሉ በሚፈቅደው መሰረት ሽማግሌውን ልኮ ለጋብቻው ሁኔ ዎች ተመቻቹ፡፡
...እናስ ...ሳቂ ...ትዳር እንዴት ነው? ብትሉኝ... አገር ጉድ ይለኛል ባልል በሰርጌ ማግስት ነበር ጣጣ ሳላበዛ ወደአባ  ቤት የምመለሰው፡፡ ምን ሆንሽ? ብትሉኝ...ያ ለሁለት አመት ያህል ከመሬት ተነጥፌ ተረማመጅብኝ ይለኝ የነበረ ሰው ልክ ከቀለበቱ ጀምሮ ትክክለኛውን ባህርይውን ማሳየት ስለጀመረ ነው ይሆናል መልሴ ...፡፡ መጠሪያ ስሜ በተጨማሪ ሳቂ  መባሉ ከልጅነ  ጀምሮ መሳቅ ስለምወድ ነው እንጂ ዋናው ስሜ ሌላ ነው፡፡  ዲያ ባለቤ  የቀለበቱ እለት ምን አለ መሰላችሁ ?

  • ምን ለሚያልፈው ለሚያገድመው ሁሉ ትገለፍጪያለሽ... እራስሽን አ ስከብሪም እንዴ?
  • እንዴ ለሁለት አመት ያህል ስስቅ አ ውቀኝም ነበር እንዴ?
  • እና ለሁለት አመት ስቃጠል የኖርኩት አንሶ አሁንም እንድበግንልሽ ትፈልጊያለሽ ?የእኔ እመቤት... ክብርሽን መጠበቅ ያስፈልግሻል፡፡ አንቺን ተከትዬ መዋረድ አልፈልግም ፡፡

     
...ምልልሳችን ይህንን ይመስል ነበር፡፡ ሰርጋችን ገና ሁለት ቀን እየቀረው ነበር ይህ ነገር የተጀመረው፡፡ ይህ ሰው እንዳያገባኝ ማድረግ ከማልችልበት ሁኔ  ላይ ነው የነበርኩት፡፡ የሰርጉ ሁኔ  እስኪጠናቀቅ እሱም ትከሻውን እንደነፋና እንደኮራብኝ እኔም እየተገረምኩኝ ኑሮውን ጀመርን፡፡ በሕይወትሽ ያዘንሽበት ቀን መቼ ነው ቢባል የቀለበ  እለት ነው የሚል ነው መልሴ፡፡
ሰርጉም መልሱም ቅልቅሉም ሁሉም ነገር ከተጠናቀቀ በሁዋላ ሁኔ ውን ለአባ  ባጫውተው ...አ.አ.ይ... እንዲህ ያለ ነገርማ መስማት አልፈልግም፡፡ እወደዋለሁ አውቀዋለሁ ብለሽ ያመጣሽውን ሰው እንደአመሉ እዛው ያዢ አለኝ፡፡ ለእና ም ባማክራት ... እኔ ለስንቱ መኩዋንንት ትዳር እያልኩ ሳማክር እምቢ ተብሎ ...እኔ እንግዲህ ምን ማድረግ እችላለሁ፡፡ የሚል ሆነ መልሱዋ፡፡እኔም እንግዲህ ምን ላድርግ የባለቤ ን ባህርይ ማስተ ከል አለብኝ ብዬ የቻልኩትን ሁሉ ሞከርኩ፡፡ ትዳር ስመሰርት  ባለቤ  ባለብዙ ጉዋደኛ፣ መጠጣት የሚፈልግ፣ ለእራሱና ለእራሱ ቤተሰብ ቅድሚያ የሚሰጥ ፣ለባለቤቱም ሆነ ለልጆቹ ምንም ግድ የሌለው ሰው ሆኖ ነው ያገኘሁት ፡፡ አልፎ አልፎም ሳነጋግረው ...በቃ... ከእኔ ጋር ጭቅጭቅ አያስፈልግም... አርፈሽ መኖር ብቻ ነው የሚል ሆነ መልሱ፡፡ ስለዚህ የእራሴን እርምጃ መውሰድ አለብኝ ብዬ ዛሬ በጋራ ያፈራናቸውን ሶስት ልጆቼን ይዤ ቤት ተከራይቼ መኖር ጀምሬአለሁ፡፡ ቢያንስ ለልጆቹ ቅርብ እንዲሆንና እንዲረዳቸው ለማድረግ እንኩዋን ደረግሁት ሙከራ በእምቢተኛነቱ ስላልተሳካ እነሆ ዛሬ ከፍርድቤት ቆመናል፡፡

ይህንን  ሪ ን ለሚያነቡ ሁሉ ትምህርት ይሆናቸወ ዘንድ ግን አንድ ማለት የምፈልገው ነገር አለ፡፡ ትዳር በመጠናናት ነው መመስረት ያለበት ሲባል እስከምንድረስ ነው? የሚለውን ሁሉም ሊያውቅ ይገባል ባይ ነኝ፡፡ ባለቤ  ስለእኔ ማንነትና ምንነት አንድም ነገር ሳይቀረው በሚገባ ያጠና ሲሆን እኔ ግን እንድንገናኝ ከሚቀጥረኝ ቦ  ከመሄድ በስተቀርና ከእርሱ ሌላ ስለእሱ የሚነግረኝ ምንም ሰው አለማግኘ  ትልቁ የጎደለኝ ነገር ነበር፡፡ ምክንያቱም ስለትክክለኛው ማንነቱ ምንም መረጃ አልነበረኝም፡፡ እርሱ እኔን በእጁ እስኪያስገባ ድረስ በአገኘኝ ጊዜ ሁሉ ጥሩ ባህርይ ሲያሳየኝ ስለነበር ከመልክና ቁመናው ጋር ተዳምሮ እንደመልአክ ነበር የቆጠርኩት፡፡ ነገር ግን እውነ ው ሲገለጥ ይኼው ዛሬ የአባት ፍቅርና እንክብ ቤ የማያገኙ ሶስት ሕጻናትን ብቻዬን ይዤ እንድቀመጥ አድርጎኛል፡፡ ስለዚህ ሴቶችም ሆኑ ወንዶች ትዳርን ሲያስቡ ከበስተጀርባ ያሉ የተለያዩ ነገሮችን ሁሉ በደንብ መመልከት መቻል ጥሩ ነው፡፡ አንዳንዴ በቤተሰብ የሚመጣ ትዳር የእርስ በእርስ መፋቀርን ባያከትትም ማንነትን በማጥናት በኩል ግን ጥሩ የሚሆንበት አጋጣሚ ይኖረዋል ብዬ አስባለሁ፡፡ በእርግጥ ጋብቻን እርስ በእርስ ተፋቅሮ መመስረቱ ጥሩ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ለትዳር የሚሆነውን ሰው ለኑሮ የሚመች ወይንም የማይመች መሆኑን አስቀድሞ በሚገባ መመርመር ጥሩ ነው  እላለሁ፡፡

 ***************************************     

ማግኔዥየም ሰልፌት(Magnesium Sul)
                                                      ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ

በእርግዝና ጊዜ           -              ኢክላምፕሲያ እና ፕሪኢክላምፕሲያ የሚልስያሜ ያለው ሕመም አንዳንድሴቶችላይይከሰል፡፡ሕመሙ ከደምግፊትጋርየተያያዘ ሲሆን በጊዜው ሕክምና ካልተደረገለት እስከሞት ሊያደርስ የሚችልና አደገኛ ሁኔ ን የሚያስከትል ነው፡፡ እርጉዝ የሆኑ ሴቶች ከመጠን ያለፈ ውፍረት ሲያጋጥማቸው እንዲሁም ሰውነ ቸው ከመጠን ያለፈ ፈሳሽ የሚይዝ ሲሆን እና ከፍተኛ የደም ግፊት ሲኖራቸው በተጨማሪም በሽን ቸው ውስጥ ፕሮቲን ሲገኝ በኢክላምፕሲያና ፕሪኢክላምፕሲያ ሕመም መያዝና አለመያዛቸውን ወደ ሐኪማቸው በመሄድ ማረጋገጥ ይጠበቅባቸዋል ፡፡ እንዲሁም የአይን ብዥ  እና ከፍተኛ የራስ ሕመም ሲሰማቸውም ወደሕክምናው ፈጥነው መሄድ አለባቸው፡፡ ፺ማይክሮሶፍት ኢን ር  2009፻ ይህ  ሕመም ለእናቶች ሞት ምክንያት ከሚባሉት ውስጥ የሚመደብ ሲሆን በህክምና መከላከል ከተቻለ ደግሞ የእናቶችን ሞት ለመቀነስ ትልቅ እርምጃ ተወሰደ ለማለት ያስችላል ፡፡ በዚህ ዙሪያ ለመፍትሔነት የተመረጠው ማግኔዥየም ሰልፌት የተባለው መድሐኒት ሲሆን በዚህም ላይ ውይይት ለማድረግ የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ባለሙያዎች በኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር የስብሰባ አዳራሽ ሚያዝያ 14/2002 ዓ/ም ስብሰባ አድርገው ነበር፡፡ማግኔዥየም ሰልፌት የተሰኘውን መድሀኒት ጠቀሜ  እና አፈጻጸሙን በሚመለከት በኢሶግ የማግኔዥየም ሰልፌት ፕሮጀክት አስተባባሪ የሆኑት አቶ ሳሙኤል ሐደራ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡  
እንደአቶ ሳሙኤል ማብራሪያ ኢክላምፕሲያ እና ፕሪክላምፕሲያ የተባለው በእርግዝና ጊዜ የሚከሰተው የደም ግፊት ሕመም ለእናቶች ሞት በምክንያትነት ከሚጠቀሱት ከፍተኛ ደረጃ ካላቸው ሕመሞች የሚመደብ ሲሆን ከዚህ ቀደም  ማሚዎቹን በሌሎች መድሀኒቶች ለማከም ጥረት ይደረግ ነበር፡፡ ማግኔዥየም ሰልፌት የተሰኘው መድሀኒት ግን በህክምናው  መሰጠት ተጀምሮ የነበረ ሲሆን ነገር ግን በቀጣይነት በአገር አቀፍ ደረጃ ስራ ላይ ሳይውል የተቋረጠ ነው፡፡ ለኢክላምፕሲያ እና ፕሪክላምፕሲያ ሕመሞች በከፍተኛ ደረጃ መፍትሔ ይሰጣል ተብሎ የሚ መንት ማግኔዥየም ሰልፌት የተሰኘው መድሀኒት በአለም ላይ ለብዙ አመ ት በስራ ላይ የዋለ ሲሆን እኛ አገር ግን የነበረው የህክምና ልምድ የተወረሰው ከእንግሊዝ በመሆኑና የህክምና አሰጣጡም የእነሱን ስርአት የያዘ ስለሆነ እሳከዛሬ ድረስ ከጥቅም ላይ ሳይውል ቀርቶአል፡፡
የእናቶች ጤና ችግር ከፍተኛ ትኩረት የተሰጠው ነው፡፡ ምክንያቱም

  • በአብዛኛው በእናቶች ላይ የሚደርስ የጤና ችግር በእርግዝና ወቅት የሚከሰት ሲሆን የእናቶችን ሕመምና ሞትን በማስከተል በተዘዋዋሪ የህጻናትን ሞት ስለሚጨምር፣
  • እናቶች የቤተሰብ መሰረት በመሆናቸውና ለእናቶች ጤንነት መጠበቅ የሚደረግ ርብርብ ለአገራዊ ብልጽግና መሰረት ስለሆነ ፣
  • መሰረ ዊ የጤና አገልግሎትችን በማስፋፋትና ህብረተሰቡም ተጠቃሚ እንዲሆን በማድረግ የእናቶች ሞት ምክንያቶች በቀላሉ ሊቀረፉ የሚችሉ በመሆናቸው ነው፡፡  

ከዚህም በመነሳት የእናቶችን ሞት በመቀነሱ ረገድ ከሚወሰዱ እርምጃዎች አንዱ ማግኔዥየም ሰልፌት የተሰኘውን መድሀኒት በእርግዝና ወቅት የደም ግፊት ለሚከሰትባቸወ ሴቶች መስጠት ጠቃሚ መሆኑን አለም ሁሉ ያመነበት ስለሆነ በአሁኑ ወቅት በሰፊው በኢትዮጵያ ውስጥ ለማስረጽ  ስቦአል፡ እስከአሁን ከምንጠቀምባቸው መድሀኒቶች ይኼኛው መድሀኒት ተመራጭ የሚሆንበት ምክንያት ከሌሎቹ ተመሳሳይ ስርአት ካላቸው መድሀኒቶች በእርግዝና ጊዜ የሚመጣውን የመንቀጠቀጥ ችግር በከፍተኛ ደረጃ የመቀነስ  ይል ስለአለው ነው፡፡ በእርግጥ የደም ግፊቱ በተለያዩ መድሀኒቶች ሊ ከምና በወሊድ ወቅትም ይሁን ከወሊድ በሁዋላ እንዲቀንስ ማድረግ ይቻላል፡፡ እርጉዝ የሆኑ ሴቶችን በሚመለከት ግን ማግኔዝየም ሰልፔት ከደም ግፊቱ ጋር በተያያዘ ለሞት የሚዳርገውን በተለምዶ የሚጥል በሽ  እንደሚባለው እሚያንቀጠቅጠውን በሻ  ለመቆጣጠር የሚያስችል መድሀኒት ነው ማግኔዥየም ሰልፌት ፕሮጀክት አስተባባሪ አቶ ሳሜኤል ገለጻ፡፡
      የማግኔዥየም ሰልፌትን አወሳሰድ በሚመለከት አቶ ሳሙኤል እንደገለጹት መድሀኒቱ በመርፌ መልክ የተዘጋጀ ሲሆን በአሰጣጡም በ ፋ ወይንም በደም ስር ሊሰጥ የሚችል ነው፡፡ ነገር ግን በአገራችን በየትኛው መንገድ መጠቀም አመቺ ይሆናል  የሚለውን ለመወሰን ግን የባለሙያዎችን ምክክር የሚሻ ይሆናል፡፡ ማግኔዥየም ሰልፌት የተባለውን ይህንን መድሀኒት በተገቢው መንገድ በሁሉም የአገሪቱ የህክምና ተቋማት በተመሳሳይ መንገድ ከጥቅም ላይ ለማዋል እንዲቻል የህክምና መመሪያ           እንዲወጣለት ዝግጅት በመደረግ ላይ ነው፡፡ ይህ የህክምና መመሪያም ከአሁን ቀደም ከወጣው  ከማህጽንና ጽንስ ሕክምና መመሪያ ጋር እንዲጣጣም ተደርጎ ይዘጋጃል፡፡

የማግኔዥየም ሰልፌትን አቅርቦት በሚመለከት መንግስት በአሁኑ ሰአት ከዩኒሴፍ ጋር በመተባበር ለስድስት ወር የሚበቃ መድሀኒት እንደአስገባ እና ከዚያም በሁዋላ መንግስት የመድሀኒቱ አቅርቦት እንዲቀጥል ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን የሚያሳ እቅድ መኖሩን የማግኔዥየም ሰልፌት ፕሮጀክት አስተባባሪ አቶ ሳሙኤል ገልጸዋል፡፡ መንግስት ማግኔዥየም ሰልፌት የተሰኘውን የእናቶችን ሞት ለመቀነስ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለውን ይህንን መድሀኒት ወደሀገር ከሚገቡ በጣም አስፈላጊ ከሆኑ መድሀኒቶች ዝርዝር ውስጥ ያስገባው ሲሆን ይህም መንግስት ከወሰዳቸው ቁርጥ ውሳኔዎችአንዱ መሆኑን ያሳያል ፡፡ ስለሆነም መድሀኒቱ እንደከአሁን ቀደሙ ተጀምሮ የሚቋረጥ ወይንም በተወሰኑ አንባቢዎች ብቻ የሚገኝ ሳይሆን እንደፍላጎቱ መጨመር ወደሐገር ይገባል የሚል እምነት አለ፡፡
አንድ አዲስ መድሀኒት ተግባር ላይ ለመዋል የሚያስችለውን ዝግጅት በሙሉ የማግኔዥየም ሰልፌት ፕሮጀክት አቅፎአል፡፡ መድሀኒቱ በእርግዝና ወቅት ለሚከሰቱት የደም ግፊት በሽ ዎች በምን መልክ ይሰጥ የሚለው ተቀዳሚ በመሆን ተገቢውን ስልጠናና ምክክር ማድረግን ይጠይቃል፡፡ በመቀጠልም በየደረጃው ለሁሉም የህክምና ተቋማት አገልግሎቱን ማዳረስ የሚያስችል እቅድ የተነደፈ ሲሆን በቅድሚያ ግን በተመረጡ በ115 የመንግስት ሆስፒ ሎች ማለትም ለእናቶችና ሕጻናት በቂ ግልጋሎት በሚሰጡት የህክምና ተቋማት እንዲጀመር ዝግጅት በመደረግ ላይ ነው፡፡  
የኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር በፕሮጀክቱ ያለው ድርሻ መድሀኒቱ በእያንዳንዱ ሆስፒ ል እንዲዳረስና እንዳይቋረጥ ክትትል ማድረግ እንዲሁም አንዳንድ የአሰራር እገዛዎች ማድረግ ነው፡፡ የህክምና ባለሙያዎቹን የማሰልጠን ስራውም የኢሶግ ድርሻ ነው ፡፡ ስራውን ለመጀመር ከተመረጡት አንድ መቶ አስራ አምስት ፺115፻ የመንግስት ሆስፒ ሎችም ሀያ ሶስቱ ፺23፻ ተመርጠው በአሰራሩ ላይ ጥናት የይደረጋል፡፡ መድሀኒቱን በመስጠቱ ረገድ የነበረው በጎ ጎንና ችግሩስ ምን እንደሚመስል እንዲሁም ማግኔዥየም ሰልፌት የተሰኘው መድሀኒት ከመሰጠቱ በፊት የነበረውን ችግርና መድሀኒቱ መሰጠት ከተጀመረ በሁዋላ ያለውን ለውጥ መመርመርም ከስራው የተ ተተ ነው፡፡ የህክምና ተቋማቱ ሕክምናውን በሚሰጡበት ጊዜ አጋዥ ወይንም ምክርና ሀሳብ ቢፈልጉም ኢሶግ ከሚሰራባቸው ስድስት አ ባቢያዊ የጤና ተቋማት ማለትም ሐዋሳ፣ ድሬደዋ ፣ሐረር ፣ጎንደር ...ወዘተ በነዚህ ቦ ዎች ያሉት የኢሶግ ወኪሎች እንዲከ ተሉ ወይንም እንዲወያዩና ችግሩን ወደኢሶግ በማቅረብ መፍትሔ እንዲያገኙ ለማድረግና ስራውን በተቀናጀ መልክ ለመምራት ዝግጅት መደረጉን ነው የፕሮጀክቱ አስተባባሪ አቶ ሳሙኤል ሐደራ የገለጹት፡፡
ዋናው ፍላጎት ከእናቶች ጤና ጋር በተያያዘ ሞትን መቀነስ ነው፡፡ ይህንን  እውን ለማድረግ ደግሞ ፖሊሲ ከመቅረጽና  የህክምና መመሪያ ከማውጣት ጀምሮ ብዙ ሂደቶች አሉ፡፡ ማግኔዥየም ሰልፌት የተሰኘውን መድሀኒት መስጠት ግን በእርግዝና ወቅት የመከሰተውን በደም ግፊት ምክንያት የሚመጣውን የእናቶችን ሞት ለመቀነስ ወሳኝ የሆነ መድሀኒት በመሆኑ ይህንን ተግባራዊ ማድረግ መቻል ምናልባትም ትልቁ ግብ ሊሰኝ የሚችል ነው፡፡ ምክንያቱም የእናቶችን ሞት በመቀነሱ ረገድ አንዱን ጫፍ የሚቋጭ ነው ብለዋል አቶ ሳሙኤል ሐደራ፡፡
የኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር በየአመቱ የሚያደርገው አመ ዊው  ጠቅላላ ጉባኤ እንደውጭው አቆጣጠር ሜይ 3 እና 4 /2010/በእኛ በኢትዮጵያ አቆጣጠር ደግሞ ሚያዝያ 25 እና 26 /2002/ 18ኛውን ጉባኤ እንደሚያደርግ ከወጣው ፕሮግራም ለማወቅ ተችሎአል ፡፡  ማህበሩ በየአመቱም በጠቅላላ ጉባኤው ወቅት ትኩረት የሚያሻቸውን የጤና ጉዳዮች እያነሳ ተገቢውን እርምጃ ለመውሰድ እንዲያመች ለስብሰባው ያቀርባል ፡፡ የዘንድሮው አመ ዊ ጉባኤ መሪ ቃልም ማግኔዥየም ሰልፌት ሲሆን ቀኑም የማግኔዥየም ሰልፌት ቀን በሚል እንዲሰየም ተወስኖአል፡፡

 **************************************

የኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር (ESOG)
   18 ጠቅላላ ጉባኤ /ሜይ 3-4 /21010 ሚያዝያ 25-26/2002
                                                      
ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ

የኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር ( ESOG ) 18ኛውን አመ ዊ ጠቅላላ ጉባኤውን እንደውጭው አቆጣጠር፺ሜይ 3-4 /21010፻ ሚያዝያ 25-26/2002 በአዲስ አበባ አ ሄዶአል፡፡ማህበሩ በየአመቱ በስነተዋልዶ ጤና ዙሪያ ተገቢውን ትኩረት ሊያገኙ ይገባቸዋል የሚላቸውን ለውይይት የሚያቀርብ ሲሆን  በዘንድሮው ጠቅላላ ጉባኤም ስለማግኔዥየም ሰልፌት አስፈላጊነት ውይይት ደርጎአል፡፡ የጠቅላላ ጉባኤው መሪ ቃልም በእርግዝና ወቅት የሚከሰተውን           -              )ኢክላምፕሲያ እና ፕሪኢክላምፕሲያ የተባለ ሕመም ለመከላከል ማግኔዥየም ሰልፌት የተሰኘውን መድሀኒት የመጠቀም አስፈላጊነትን የሚገልጽ ነው፡፡
የማግኔዥየም ሰልፌትን ምንነት በሚመለከት ፕሮፌሰር እያሱ መኮንን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ-ሲኒየር ፋርማኮሎጂስት እንዲሁም የማግኔዥየም ሰልፔት መድሀኒትን ጥቅም ላይ እንዲውል ለማስቻል የኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስ ርን እንቅስቃሴ በሚመለከት ደግሞ ዶክተር መንግስቱ  ይለማርያም ከጤና ጥበቃ ሚኒስተር የጤና ማበልጸግና በሽ  መከላከል ዳይሬክቶሬት ቢሮ የእናቶች ጤና አማ ሪ ለዚህ አምድ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
እንደዶክተር መንግስቱ  ይለማርያም ማብራሪያ ማግኔዥየም ሰልፌት በኢትዮጵያ በተለያየ ምክንያት  አይ ወቅም ነበር ማለት ይቻላል፡፡ አሁን ግን በተለይም ኢክላምፕሲያና ፐሪኤክላምፕሲያ ለተሰኘው በእርጉዞች ላይ ለሚከሰተው ሕመም መድሀኒት መሆኑ ስለተረጋገጠና በአለም ላይ ከፍተኛ ግምት የተሰጠው መድሀኒት ስለሆነ ወደአገር እንዲገባ ተደርጎአል፡፡

ይህ መድሀኒት ወደ አገር እንዲገባና ከፍተኛ ግምት ከተሰጣቸው መድሀኒቶች መ ከል እንዲመዘገብ መደረጉ ጤናማ እናትነት በሚል ለአንድ ወር ያህል በመላው ኢትዮጵያ የተለያዩ እንቅስቃሴዎች ከተደረጉ ጀምሮ በመንግስት በመደረግ ላይ ያለውን ከፍተኛ እርምጃ የሚያሳይ ነው እንደ ዶ/ር መንግስቱ ፡፡ በውጭው አቆጣጠር በ2005 የተደረገ አንድ ጥናት እንደሚያስረዳው በእናቶች ጤና ላይ የሚሰሩ ስራዎች ባለፉት ጊዜያቶች ጥራ ቸው ዝቅ ያለ እንደነበር የሚያሳይ ሲሆን በአሁኑ ወቅት ግን በእናቶች ጤና ዙሪያ ያሉ የህክምና አገልግሎቶችን ጥራ ቸውን ከፍ ለማድረግ እና ተገቢውን ሕክምና ለመስጠት መንግስት እንደ የኢትዮጵያ የማህጸንና ጽንስ ሐኪሞች ማህበር ካሉ አጋር ድርጅቶች ጋር በመተባበር ከፍተኛ እንቅስቃሴ እያደረገ ነው ፡፡
ዶ/ር መንግስቱ  ይለማርያም እንደገለጹት መድሀኒቱን ወደሀገር የማስገባትና የማሰራጨት እንዲሁም ተግባራዊነቱን የመከ ተሉ ስራ ይቀጥላል፡፡ የምእተአመቱ ግብ እንደውጭው አቆጣጠር በ1919 ዓ/ም የተፈረመ ሲሆን ተግባራዊነቱ የሚጠበቀው በሀያ አምስት አመት ጊዜ ውስጥ በ2015 ዓ/ም ነው፡፡ ስምምነቱ በተፈረመበት ጊዜ በኢትዮጵያ ከመቶ ሺህ እናቶች ውስጥ ከአንድሺህ በላይ ይሞቱ የነበረ ሲሆን አሁን ግን በ2005 የተደረገ ጥናት እንደሚያሳየው ከአንድ ሺህ ወደስ ድስት መቶ ሰባ ሶስት ዝቅ ብሎአል፡፡ ወደፊት አስከ 2015 ደግሞ በኢትዮጵያ የእናቶች ሞት ወደ ሁለት መቶ ስድሳ ሰባት ቢቻልም ከዚያ በ ች እንዲሆን ጥረቱ ይቀጥላል፡፡
ፕሮፌሰር እያሱ መኮንን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እንደሚገልጹት ማግኔዥየም ጨው ነው ፡፡ ማግኔዥየም ሰውነ ችን ውስጥ የሚገኝ ንጥረ ነገር ሲሆን ንጥረ ነገሩ ሊገኝ የሚችለው በምግብ አማ ኝነት ነው፡፡ ማግኔዥየም በተወሰነ መጠን በሰውነ ችን ውስጥ መገኘት ያለበት ንጥረ ነገር ሲሆን ይህ ንጥረ ነገር በበቂ ደረጃ በሰውነ ችን ውስጥ ካልተገኘ ሰውነ ችን ሊሰራው የሚገባው ነገር ሊስተጉዋጉልበት እንደሚችል ነው ያብራሩት ፡፡
እንደፕሮፌሰሩ መግለጫ ማግኔዥየም ጨው ነው ቢባልም ከምግብ ጨው ጋር ግን አይመሳሰልም፡፡ ጨው ሲባል ብዙ አይነት ጨው አለ፡፡ ለምሳሌም የገበ  ጨው የሚባለው ሶድየም የሚባለውን ንጥረ ነገር የያዘ ሲሆን ጨው ማለት ደግሞ ሶድየምን የያዘ ብቻ ሳይሆን ማንኛውም የተለያዩ ንጥረ ነገሮችን ያዘሉ በጨው መልክ የሚዘጋጁትን ያ ት ል ፡፡  
ማግኔዥየም ሲባል ንጥረ ነገር ነው፡፡ ንጥረ ነገሩን ግን እንዳለ ወደሰውነት ማስገባት ስለማይቻል ያንን ንጥረ ነገር አመቺ በሆነ መንገድ ለምሳሌ በመድሀኒትነት መልክ ጥቅም ለሰይ እንዲውል ሲፈለግ በጨው መልክ ከ ሚ ሉ ጋር አንድ ላይ በማዋሃድ ስለሚዘጋጅ ማግኔዥየም ሰልፔትን ያስገኛል ፡፡ ዋናውን የህክምና ስራውን የሚሰራው ማግኔዥየም ሲሆን ሰልፔት ደግሞ ከጥቅም ላይ እንዲውል ሲባል የሚ ተት  ነው፡፡
ማግኔዥየም ከምግብ ማለትም ከፍራፍሬ፣ አትክልት፣ የእንስሳ ውጤት ከመሳሰሉት በአጠቃላይም ከሚወሰዱ ከተለያዩ ምግቦች ይገኛል፡፡ ብዙ ምግቦች ማግኔዥየም ስለአላቸውና በበቂ መጠን ከየምግቦቹ ስለሚገኝም የማግኔዥየም እጥረት ብዙ ጊዜ በሰውነት ውስጥ አይከሰትም እንደፕሮፌሰር እያሱ ማብረሪያ፡፡
እርጉዝ ሴቶች ላይ ከደምግፊት ጋር በተያዘ ለሚከሰተው አክላምፕሲያና ፕሪክላምፕስያ ለተሰኘው ሕመም የማግኔዥየም ፈዋሽነት የተረጋገጠ ሲሆን በእርግዝና ጊዜ ስለሚከሰተው የማግኔዥየም እጥረትግን በጥናት የተደገፈ ብዙ ማረጋገጫ የለም፡፡ ነገር ግን እንደአጠቃላይ ሊወሰድ የሚችለው ይህ በሽ  የሚያጠቃው በኢኮኖሚያቸው ዝቅተኛ ደረጃ ላይ ያሉ ሰዎችን መሆኑን ነው፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ ምናልባት እርግዝናው ሲከሰት እርጉዝዋ እናት ንጥረ ነገሩን ልጅዋ ሊሻማት ስለሚችል የማግኔዥየም እጥረት ሊያጋጥማት ይችላል ወደሚለው መደምደሚያ ሊያደርስ ይችላል፡፡
ማግኔዥየም ሰውነት የተለያዩ ስራዎችን እንዲሰራ የሚያግዝ ንጥረ ነገር ነው ፡፡ በተለያየ ምክንያት የማግኔዥየም ጉድለት በሰውነት ውስጥ ከተከሰተ ግን ሰውነት ሊሰራው የሚገባው ነገር እንዲስተጉዋጎል ያደርጋል፡፡ የማግኔዥየም እጥረት በሰውነት ውስጥ ሲከሰት የተለያዩ የነርቭ ችግሮችን፣ የማሰብ ፣የጡንቻ ፣ መንቀጥቀጥ የመሳሰሉትን ችግሮች የሚያስከትል ሲሆን ባጠቃይም የመሀከለኛው የነርብ አ ል እንዲጎዳ ያደርጋል፡፡
የማግኔዥየም እጥረት ጾ ና እድሜን አይለይም፡፡ በእርግጥ በእርግዝና ወቅት ሊከሰት የሚችለው የማግኔዥየም እጥረት ለከፋ የጤና ችግር ስለሚያጋልጥ ከፍተኛትኩረት የሚያሻው ነው፡፡ነገር ግን በእጥረቱ ምክንያት የሚከሰተው ሕመም የሚያጠቃው ሴቶችን ብቻ ሳይሆን ወንዶችንም ጭምር ነው፡፡
ፕሮፌሰር እያሱ መኮንን በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሲኒየር ፋርማኮሎጂስት እንደሚሉት መድሀኒት ማለት መርዝ ነው፡፡ ከመርዝ ጋር መጫወቱ አማራጭ በሌለበት ሁኔ  ብቻ ነው መሆን ያለበት ፡፡ ስለሆነም የማግኔዥየም እጥረትን ለመከላከል ሌላ አማራጭ ቢኖር ጥሩ ነው፡፡ በተለይም በእርግዝና ወቅት የተመጣጠነ ምግብ መመገብ አንዱ ችግሩን ለማስወገድ አስፈላጊ ነገር ነው ፡፡ማግኔዥየም ሰልፔት የሚባለው መድሀኒት ኢክላምፕሲያና ፕሪኤክላምፕላሲያ ላለባቸው እርጉዝ ሴቶች የሚሰጥ ነው፡፡ ሌላ መድሀኒት ለምን አይሰጥም ብለው የሚያስቡ ሰዎች ቢኖሩ መልሱ እንደማግኔዥየም  ችግሩን ሊቆጣጠር የሚችል የሌለ መሆኑን ነው ጥናቶች የሚያስረዱት፡፡
እንደፕሮፌሰር እያሱ እምነት ይህ መድሀኒት ሙሉ ለሙሉ ውጤ ም ነው፡፡ ነገር ግን መድሀኒቱ ያለምንም ችግር ውጤት ያመጣል ማለት እንዳልሆነ መ ወቅ አለበት፡፡ ስለሆነም የህክምና ባለሙያዎች ስልጠና መውሰዳቸው  ተገቢ ነው፡፡ መድሀኒቱ በተለይም የመተንፈሻ አ ላትን ክፉኛ ሊጎዳ ስለሚችል ጥንቃቄ መደረግ አለበት፡፡ የህክምናው ዘርፍ በሚያውቀው የክትትል ዘዴ በጥንቃቄ ለ  ሚዎች ሊሰጥ የሚገባው መድሀኒት ነው ፡፡ ይህ ማለት ግን መድሀኒቱን ጥቅም ላይ ለማዋል የሚያሰጋ ነገር አለ ማለት አይደለም ብለዋል ፕሮፌሰር እያሱ መኮንን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፡፡

***********************

ዓለም አቀፍና አገር አቀፍ የኤችአይቪ ገጽ  በህጻናት ...
                                                   ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ

  • በኢትዮጵያ 72.945 ሰባ ሁለት ሺህ ዘጠኝ መቶ አርባ አምስት የሚሆኑ ከአስራ አምስት አመት እድሜ በ ች ያሉ ሕጻናት ከኤችአይቪ ቫይረስ ጋር ይኖራሉ፡፡  
  • በኢትዮጵያ ስምንት መቶ ሀምሳ አምስት ሺህ ሰባትመቶ ሀያ ፺855.720፻የሚሆኑ ሕጻናት በኤይድስ ምክንያት ወላጆቻቸውን ያጡ መሆናቸው ይገመ ል፡፡
  • ከእናት ወደ ልጅ በሚተላለፍ የኤች አይ ቪ ኢንፌክሽን አማ ኝነት የተጠቁ ሕጻናት ምንም አይነት ሕክምና ካልተደረገላቸው 50% ሀምሳ በመቶ የሚሆኑት የሁለት አመት እድሜ ሳይሞላቸው የሚሞቱ ሲሆን ሌሎች ማለትም 75% ሰባ አምስት ከመቶ የሚሆኑት ደግሞ አምስት አመት እድሜ ሳይሞላቸው ሕይወ ቸው እንደሚያልፍ ጥናቶች ያሳያሉ፡፡
  • የኤችአይቪ ተጠቂ የሆኑ ህጻናት የእድገት ዝግመት፣ ክብደት መቀነስ ፣ተቅማጥና በቆዳ ላይ የሚከሰቱ ችግሮች ፣ተደጋጋሚ የአየር መተንፈሻ ቧንቧ ኢንፌክሽን የመሳሰሉት ሕመሞች ይ ዩባቸዋል፡፡

**          **              **     

ባለፈው ሳምንት እትም ፺                              )  ወርልድ ዋይድ ኦርፋንስ ፋውንዴሽን ከተሰኘ ግብረሰናይ ድርጅት ሕጻናትንና ኤችአይቪ ኤይድስን በተመለከተ አንዳንድ መረጃዎችን ላንባቢ ማቅረባችን ይ ወሳል፡፡ በድርጅቱ የኢትዮጵያ ቢሮ ዳይሬክተር የሆኑት ዶክተር ሶፍያ መንግስቱ የህጻናትን ሁኔ  ከኤችአይቪ አኩዋያ የሰጡንን ቀሪ ማብራሪያ እነሆ ለንባብ ብለናል፡፡

ህጻናት በጤንነ ቸው ሁኔ  እንዲወስኑና እንዲሳተፉ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡
                                                   ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ

  • በኢትዮጵያ 72.945 ሰባ ሁለት ሺህ ዘጠኝ መቶ አርባ አምስት የሚሆኑ ከአስራ አምስት አመት እድሜ በ ች ያሉ ሕጻናት ከኤችአይቪ ቫይረስ ጋር ይኖራሉ፡፡  
  • በኢትዮጵያ ስምንት መቶ ሀምሳ አምስት ሺህ ሰባትመቶ ሀያ ፺855.720፻የሚሆኑ ሕጻናት በኤይድስ ምክንያት ወላጆቻቸውን ያጡ መሆናቸው ይገመ ል፡፡
  • የኤችአይቪ ተጠቂ የሆኑ ህጻናት የእድገት ዝግመት፣ ክብደት መቀነስ ፣ተቅማጥና በቆዳ ላይ የሚከሰቱ ችግሮች ፣ተደጋጋሚ የአየር መተንፈሻ ቧንቧ ኢንፌክሽን የመሳሰሉት ሕመሞች ይ ዩባቸዋል፡፡

**          **              **     
ባለፈው ሳምንት እትም ፺                              )  ወርልድ ዋይድ ኦርፋንስ ፋውንዴሽን ከተሰኘ ግብረሰናይ ድርጅት ሕጻናትንና ኤችአይቪ ኤይድስን በተመለከተ አንዳንድ መረጃዎችን ላንባቢ ማቅረባችን ይ ወሳል፡፡ በድርጅቱ የኢትዮጵያ ቢሮ ዳይሬክተር የሆኑት ዶክተር ሶፍያ መንግስቱ የህጻናትን ሁኔ  ከኤችአይቪ አኩዋያ የሰጡንን ቀሪ ማብራሪያ እነሆ ለንባብ ብለናል፡፡
ኢሶግ/ በኤችአይቪ ቫይረስ ለተያዙ ሕጻናት ፀረ ኤችአይቪ በመስጠቱ ረገድ ወላጆች ሊያውቁት የሚገባው ነገር ምንድነው?
ዶ/ር    ከፀረ ኤችአይቪ መድሀኒቶች የሚጠበቀውን ውጤት ለማግኘት የሚቻለው የመድሀኒቱን ባህሪይና አጠቃቀም በመገንዘብ በትክክል በመውሰድና የጤና ባለሙያዎችን ምክር ተግባራዊ በማድረግ ብቻ ነው፡፡ አንድ ህጻን ኤችአይ ቪ በደሙ ውስጥ ስለተገኘ ብቻ ያለሀኪም ትእዛዝና ክትትል የፀረ ኤችአይቪ መድሀኒት ቢወስድ ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ የሚያመዝን በመሆኑ ባለሙያ በማማከር አገልግሎቱን በሚሰጡ ሕጋዊ የህክምና ተቋማት ብቻ መጠቀም ያስፈልጋል፡፡ በመሆኑም ወላጆች የሚከተሉትን ማወቅ ይጠበቅባቸዋል፡፡  

  • የፀረ ኤችአይቪ መድሀኒት ህክምና መከ ተል እድሜ ልክ የሚወሰድ በመሆኑ መድሀኒቱን ለማስጀመር ቁርጠኛ መሆን ያስፈልጋል፡፡
  • መድሀኒቱ አንዴ መወሰድ ከተጀመረ እድሜ ሙሉ ሳይቋረጥ መቀጠል ይኖርበ ል፡፡
  • በምንም አይነት ሁኔ  ቢሆን መድሀኒቱ እንዲወሰድ በ ዘዘበት ሰአት ሁሉ መውሰድ አስፈላጊ ነው፡፡
  • ፀረኤችአይቪ መድሀኒት ህክምና የጀመረ ህጻን በየጊዜው ተከ  ይ የጤና ምርመራ ማድረግ ይኖርበ ል፡፡
  • ማንኛውም መድሀኒት ለአንድ ህመም መድሀኒትነት ሲያገለግል ሌሎች የማያስፈልጉ የጎንዮሽ ውጤቶች ሊያስከትል ይችላል፡፡ በተመሳሳይ ሁኔ  የፀረ ኤችአይቪ መድሀኒቶችም በአይነ ቸውና በመጠናቸው ከሰው ሰው ይለያዩ እንጂ መወሰድ በጀመሩ በመጀመሪያዎቹ ጥቂት ሳምን ት ጊዜ ውስጥ ወይንም በተወሰነ ደረጃ ቀጣይነት ባለው መልኩ የተለያየ የጤንነት መ ወክ ሁኔ  ሊያጋጥም ይችላል፡፡ የጤና መ ወኩ ከመጠን ባለፈ ሁኔ  ከተከሰተ ወላጆች የህጻናቱን ሐኪም ማማከር ያስፈልጋቸዋል፡፡

ኢሶግ/ ህጻናት የፀረ ኤችአይቪ መድሀኒት በትክክል እንዲወስዱ ለማድረግ ወላጆች ምን ማድረግ
ይጠበቅባቸዋል?
ዶ/ር    የፀረ ኤችአይቪ መድሀኒት አወሳሰድ አጠቃላይ መመሪያ አለው፡፡

  • ለህጻናቱ የመድሀኒቱን አስፈላጊነት በየጊዜው ማስረዳት ያስፈልጋል፡፡
  • መድሀኒቱ የሚወሰድበትን ሰአት መወሰን ያስፈልጋል፡፡
  •  የሚወስደውን መድሀኒት አይነትና መጠን ለይቶ ማወቅ ማዘጋጀት፡፡
  • መድሀኒቱ ተመሳሳይ ቢሆንም ከሌላ ሰው ጋር መጋራት ክልክል ነው፡፡
  • የመድሀኒት መስጫ/መለኪያ እቃዎችን መድሀኒት ከመስጠት በፊትና በሁዋላ በሚገባ ማጽዳት ያስፈልጋል፡፡
  • ለአንድ ጊዜ መድሀኒት መውሰድ ቢረሳ በሚቀጥለው ጊዜ እጥፍ መጠን ያለው መድሀኒት መውሰድ የተከለከለ ነው፡፡ ነገር ግን መድሀኒት መወሰድ ናለበት ሰአት በአራት ሰአ ት ጊዜ ውስጥ ማስ ወስ ከተቻለ የተወሰነውን የአንድ ጊዜ መጠን ብቻ መውሰድ ይቻላል፡፡

ህጻናቱ መድሀኒቱን በክኒን መልክ የሚወስዱ ከሆነ መድሀኒቱ በአፋቸው ውስጥ እንዳልቀረና በትክክል እንደዋጡት ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡

  • መድሀኒቱን በእንክብል መልክ ሲወስዱ የሚቸገሩ ከሆነ መድሀኒቱን በወረቀት በመጠቅለል በጠርሙስ መፍጨትና በውሀ በጥብጦ መስጠት እንደ አማራጭ መውሰድ ይቻላል፡፡
  • በፈሳሽ መልክ የተዘጋጀ መድሀኒት ከተወሰደ በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ ከባድ ትውከት ካስከተለና መድሀኒቱ መውጣቱ ከተረጋገጠ በድጋሚ መውሰድ ያስፈልጋል፡፡
  • በ ብሌት/እንክብል መልክ የተዘጋጀ መድሀኒት ከተወሰደ በሁዋላ ትውከት ካስከተለና መድሀኒቱ ሳይሟሟ ከወጣ ደግሞ መውሰድ ይቻላል፡፡ ይህ ባልሆነበት ሁኔ  በድጋሚ መስጠት አያስፈልግም ፡፡
  • መድሀኒቱን ከወሰዱ በሁዋላ ህጻናቱን ማመስገንና ማበረ  ት ሁልጊዜም መድሀኒቱን ያለችግር እንዲወስዱ ያስችላል፡፡
  • ወላጆች መድሀኒቶቹን ህጻናት በማይደርሱበት ቦ  እንዲሁም ቀዝቃዛ እና ደረቅ በሆነ የፀሐይ ብርሀን በማይደርስበት እና ሙቀት በማይኖርበት ሁኔ  ማስቀመጥ ይኖርባቸዋል፡፡

ኢሶግ/ ኤችአይቪ ከአንዱ ህጻን ወደሌላው እንዳይተላለፍ ሊደረግ የሚገባወ ጥንቃቄ ምን
ይመስላል?
ዶ/ር    ኤችአይቪ ኤይድስ ከደም ጋር ንክኪ በሌለበት ሁኔ  በሌሎች ማህበራዊ ግንኙነቶች ማለትም አብሮ በመመገብ፣ በመተኛት ፣በመጫወት በመሳሰሉት አይተላለፍም፡፡ በመሆኑም ኤችአይቪ ያለባቸውን ህጻናት በየትኛውም ስፍራ ከሌሎች ህጻናት እንዲለዩ ማድረግ ተገቢ አይደለም፡፡ ባጠቃላይም ሌሎች ተላላፊ በሽ ዎችን ለመከላከል ከምናደርገው የተለየ ጥንቃቄ አያስፈልግም፡፡
ነገር ግን ባጠቃላይ ህጻናቱ ከማንኛውም ሰው ጋር ስለ ማ ነገሮችን ማለትም እንደ የጥርስ ብሩሽ ፣መርፌ ፣ምላጭ ፣የጆሮ ጉትቻና ሌሎች ስለ ም ጌጣጌጦችን እና የውበት መጠበቂያዎችን የመሳሰሉትን በጋራ እንዳይጠቀሙ ማስተማር ያስፈልጋል፡፡ ማንኛውም ህጻን ቢደማ ወይንም በጨዋ  ጊዜ ግጭት ቢፈጠር ከደም ጋር ንክኪ እንዳይኖር በጓንት መጠቀም አስፈላጊ ነው፡፡
ኢሶግ/ የህጻናት የኤችአይቪ ምርመራና ህክምና በማድረግ ረገድ ያጋጠሙ ችግሮች አሉ?
ዶ/ር    በእርግጥ በአሁኑ ሰአት ብዙ የተሸሻሉ አገልግሎት አሰጣጦች አሉ፡፡ ነገር ግን አሁንም የቀረ ወይንም ሊስተ ከል የሚገባው ከሚባሉት መ ከል፣

    • የእናቶች የእርግዝና ምርመራና ክትትል ሽፋን አናሳ መሆን፣
    • የማዋለጃ አገልግሎት መስጫ ተቋማት አናሳ መሆን፣
    • ከእናት ወደልጅ መከላከል፺     ፻አገልግሎት በበቂ ሁኔ  አለመኖር፡፡እንዲሁም ስለ አገልግሎቱ ህብረተሰቡ ያለው ግንዛቤ ዝቅተኛ መሆን፣
    • ከእናት ወደልጅ መከላከል፺     ፻አገልግሎትና ሌሎች ተመሳሳይ አገልግሎት አሰጣጥ የቅንጅት ማነስ፣
    • በቂ የሰለጠነ የሰው  ይል አለመኖር የመሳሰሉት ቢስተ ከሉ ለሚሰጠው አገልግሎት አስተዋጽኦው ከፍተኛ ነው፡፡

ኢሶግ/ ወላጆች ኤችአይቪ ላለባቸው ህጻናት ልጆቻቸው ስለበሽ ው መንገር ይኖርባቸዋል?
ዶ/ር    ኤችአይቪ ያለባቸው ህጻናት በየትኛውም እድሜ ላይ ውጤ ቸውን እንዲያውቁ ማድረግ እንዳለብን ግልጽ የሆነ መመሪያ ባይኖርም የህጻኑ እድሜ የጤንነት ሁኔ ና ሌሎች ማህበራዊ ጉዳዮችን ግንዛቤ ውስጥ በማስገባት ህጻናቱ እንዲያውቁት ቢደረግ ጠቀሜ  ይኖረዋል፡፡ በአብዛኛው ህጻኑ ትምህርት ቤት በሚገባበት እድሜ፺ከ8፻ስምንት አመት ጀምሮ እንዲያውቅ ቢደረግ ጠቀሜ  እንዳለው ይመከራል፡፡ ባጠቃላይ ግን በየትኛው እድሜ ለሚገኘው ልጅ በምን ሁኔ  መረጃውን መስጠት እንደሚገባ ከባለሙያ ምክር መጠየቅ ተገቢ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ወላጆች...

      • ህጻናቱ የሚጠይቁትን ጥያቄ በትክክል መመለስ፣
      • የህጻናቱን እድሜ የሚመጥን መረጃ እንዲያገኙ ማድረግ፣ የህጻናቱ እድሜ በጨመረ ቁጥር ለእድሜያቸው የሚመጥን ተጨማሪ መረጃዎችን መስጠት፣
      • ህጻናት በጤንነ ቸው ሁኔ  እንዲወስኑና እንዲሳተፉ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ሕጻናት ተከ  ይ የምክር አገልግሎት እንዲያገኙ ማስቻልም ከወላጆች ይጠበቃል፡፡  

********************************************

   ከጥሩው ትዳር ቸር ይግጠመን ...ብሎ መጸለይ...                                
ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ

፵ሰላምና ጤናን ለላንቺና ላንተ አምድ አዘጋጆች እንዲሁም ለ ዳሚዎቹ እላለሁ፡፡ ከጥቂት ሳምን ት በፊት በእናንተ አምድ አንድ ጽሁፍ አንብቤ ነበር፡፡ ትዳር ለመመስረት... መጠናናት...እስከምን ድረስ? በሚል የኮተቤዋ ሳቂ  ለአንባቢ ይድረስልኝ ያለችው ነበር፡፡ ምንም እንኩዋን የእራስዋ  ሪክ ቢሆንም ለሌሎች ጉዳዩ ለሚመለከ ቸው ሁሉ የሚጠቅም እጅግ በጣም ጥሩ ትዝብት ነበር ያቀረበችው፡፡ከዚያም በመነሳት በእኔ በኩል ደግሞ ያጋጠመኝን እንድ ስነብቡልኝ እነሆ ብያለሁ፡፡፶
       ከላይ ያነበባችሁትን ጽሁፍ ጋዜጣው ላይ በሚገኘው የዘጋቢዋ ኢሜይል አድራሻ የላከልን ወንድምኩን ተሰማ ከናዝሬት ነው፡፡ ወንድምኩን እነሆ ያለንን የህይወት እማኝነት እኛም እነሆ ለአንባቢ ብለናል፡፡
            *         *           *           *      

     እኔና የአሁኑዋ ባለቤ  የቀድሞዋ የልጅነት ጉዋደኛዬ የተገናኘነው በናዝሬት ፺አዳማ፻ ከተማ በአብሮ አደግነት ነው፡፡ በእርግጥ እኔ በእድሜ ሶስት አመት ያህል እበልጣ ለሁ፡፡  ድያ እኔና አብሮ አደጌ አፈር በምንፈጭበት ዘመን ከጉዋደኞቻችን ጋር በመሆን አንዳንድ ጨዋ  ስንጫወት ባልና ሚስት የሚለው ምድብ ብዙ ጊዜ ይደርሰን ነበር፡፡ የሁዋላ ሁዋላ ተለማመድንና ነው መሰል እኔም ሆንኩ እሱዋ በአጋጣሚ እንኩዋን ከሌሎች ልጆች ጋር ባልና ሚስት የሚለው ጭውውት ሲደርሰን ያለእፍረት እምቢ አልፈልግም ...እምቢ አልፈልግም እያልን ስንወራጭ ይሳቅብን ነበር፡፡ እንዲህ እንዲህ እያልን ስናድግ በእድሜያችንም ከፍ እያልን ትምህርቱም እየዘለቀ በመሄዱ በሁዋላ ላይ የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና ለመፈተን በቃን፡፡ ግን ውጤቱ ምን ሆነ መሰላችሁ?...እሱዋ ውጤት ሲመጣላት እኔ ግን አልመጣልኝም፡፡ ጎበዝ ወንድም ስለነበራት ጥናትዋን እየተከ ተለ ለውጤት አንዳበቃት እርግጠኛ ነበርኩ፡፡ እኔ ግን ለቤተሰቤም ትልቁ ልጅ ስለነበርኩና ወላጆቼም በትምህርቱ ረገድ ምንም የሚያውቁት ነገር ስላልነበረ እንደልቤ  ስቦዝን ያው ...ዘጭ ማለት አልቀረልኝም፡፡የልጅነት ጉዋደኛዬ የአሁንዋ ባለቤ  በጊዜው በነበረው ምድብ አስመራ ዩኒቨርሲቲ ስለደረሳት ሻንጣዋን ጠርፋ ጉዞዋን ስ መቻች እጅግ ተላቅሰን ነበር የተለያየነው፡፡

በቃ...ወደ አስመራ ሄደች፡፡ በዛን ጊዜ እንደአሁኑ የሞባይል ስልክ የለ...መደበኛውም ስልክ ቢሆን ያውም አስመራ ድረስ እንዴት ይደወላል... ብቻ ምንም ገንዘብ ለሌለው ሰው ሁሉ ነገር ጨለማ ነበር፡፡ ትንሽ ወራት በልቤ ሐዘኔን ተሸክሜ እንደተቀመጥኩ ድሬደዋ ይኖር የነበረ አጎ  ሁኔ ዬ ስላላማረው ...እዚህ ተቀምጠህ ምን ትሰራለህ ? ና ...እኔጋ ...እግዜር ያውቃል...አንዳንድ ነገር ትጀምራለህ ... አለና አስከትሎኝ ሄደ፡፡
      በድሬደዋ ከተማ ደቻቱ የምትባል እጅግ ሞቅ ያለች ሁሉም አይነት ሰው ፺ሀብ ም... ደሀ... አገሬውም... ሌላውም...፻የሚኖርባት መንደር ነች፡፡ አጎ  የመረጠልኝ ይህችን ስፍራ ሲሆን ትንሽ ገንዘብ ሰጥቶ... ትንሽ ቤት ተከራይቶ ...ያውልህ ...እንደሳምቡሳ...ሻይ...ቀሽር...የመሳሰሉትን እየሰራህ ሽጥ ...ብሎ አያያዘኝ፡፡ እነሆ ዛሬ ያ ንግድ መልኩን ለውጦ ባለ ካፊ ሪያና ትላልቅ  ክ ቤት ለመሆን  ስላስቻለኝ ...ይህንን ሀሳብ አምጥቶ ለዚህ ላበቃኝ አጎ ም እዚህ አገር ያልተነዳች ቶዮ  ዲኤክስ መኪና ለመሸለም በቅቻለሁ፡፡ ስራውም ከድሬደዋም ወጥቶ ናዝሬትም አዲስአበባም ድረስ የተስፋፋ ሲሆን ያ ስራም በኔ አቅም በርካ  የምለው ሰራተኛም ያስተዳድራል፡፡
      ወደ አስመራ ዩኒቨርሲቲ ተመድባ የሄደችው የልጅነት ጉዋደኛዬ የአሁኑዋ ባለቤ  ትምህርትዋን ጨርሳ ተመርቃ ስትመጣ ስራ ያገኘችው በሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስ ር ነበር፡፡በጊዜው እኔም የጦፈ ስራ ላይ ስለነበርኩ እሱዋም በራስዋ ምክንያት ልንገናኝ አልቻልንም ነበር፡፡ በእርግጥ በዚህ ጊዜ ውስጥ እኔም የሴት ጉዋደኛ ለመያዝ እሱዋም የወንድ ጉዋደኛ ለመያዝ ወዲያ ወዲህ አላልንም ባንልም የእሱዋን ባላውቅም ከእኔ መንፈስ ውስጥ ግን እሱዋን የም ስወጣ ሴት አላገኘሁም ነበር፡፡ስለሆነም ከተለያየን ከሰባት አመት በሁዋላ እንደገና እንድንገኛኝ ሁኔ ዎችን ማመቻቸት ጀመርኩ፡፡ ጥያቄዬም ተቀባይነትን አገኘ፡፡
      እኔ የማውቃት የልጅነት ጉዋደኛዬ ተፈጥሮ ከለገሰቻት ውጫዊ አካልዋ ቁንጅና በላይ ውስጣዊ ስሜትዋ እጅግ ለሰው የሚመች ፣ደግ፣ ግልጽና  ማኝ ነበረች፡፡ ለተቸገረ አሳቢ እና የፍቅር ሰው ስለነበረችም የአስራ አንደኛ ክፍል ተማሪ ሆነን ነበር ፍቅራችን እየጠነከረ በመሄዱ ሳናስበው እሱዋም የእኔን እኔም የእሱዋን ክብረንጽሕና የተዳፈርነው፡፡ በቃ...እኔ ከዚያ በሁዋላ በፍቅሩዋ ነሆለልኩ ፡፡ ትምህር ን መከ ተል ቀርቶ እርስዋን ከማሰብ ውጭ ምንም ነገር ማሰብ አቅቶኝ እንደነበር ዛሬ ላይ ሆኜ ሳስበው ...አወይ ፍቅር እውር ...እላለሁ፡፡ እሱዋ ግን ምንም እንኩዋን በፍቅሬ ብትወድቅም የምትፈራው  ላቅ ወንድሙዋ የግድ ወደትምህርትዋ እንድ ዘነብል ትልቅ እገዛ ያደርግላት ስለነበር ውጤ ማ ሆናለች፡፡ ደግነቱ እርግዝና አልተከሰተም ነበር፡፡ ከዚያ በሁዋላ ግን ከእስዋ ጋር ፍቅርን ለመጋራት ብዙም ምቹ ሁኔ ዎች ሳይኖሩ ነበር የተለያየነው፡፡  ድያ ከሰባት አመት በሁዋላ እንደገና የፍቅር ጉዋደኛ እንድንሆን ስጠይቃት ምንም ሳ ንገራግር ነበር በእሺ  የተቀበለችኝ፡፡ እኔም በጣም እወዳት ስለነበር በእጅጉ ተደስቼ የጋብቻውን ሂደት ቀጠልኩ፡፡
      ከዚያስ በሉኛ... አሁን እንግዲህ እኔንና የኮተቤዋን ሳቂ  የሚያመሳስለን ነገር ተፈጠረ ማለት ይቻላል፡፡ የሚለየው የተፈጠረው ነገር ሁኔ ው እንጂ ውጤቱ ዞሮ ዞሮ በፍቅር ያጠመዱትን ሰው እንደነበር ያለማግኘት ነው፡፡ በሰርጉ ሰሞን አንዳንድ ምልልሶች ነበሩን፡፡
እኔ/     እኔ የእምልሽ?
እሷ/     እ...ህ...
እኔ/      ሰርግ ያስፈልጋል እንዴ?
እሷ/     እኛ ከተግባባን ሰርጉ ቢቀርም ግድየለም፡፡
       የመጀመሪያው ንግግራችን ይህንን ይመስል ነበር፡፡ለማንኛውም በጣም ትንሽ ሰዎች እስከ ሀያ የሚደርስ ማለት ነው ልንጠራና ...የፊርማ ስነስርአትን ማድረግ አላማ አድርገን የምንጋባበት ቀን አንድ ወር ሲቀረው ሌላ ነገር ተከሰተ፡፡
እሷ/     እኔ የምልህ?
እኔ/      እ...ህ...
እሷ/     በትንሹ እንኩዋን ሰርግ አናደርግም እንዴ?
እኔ/      አያስፈልግም አላልሽም እንዴ?
እሳ     አ...አ...ይ  ቢሆንም አሁን ሳስበው ትክክል አልነበርኩም፡፡
      እንግዲህ ልብ በሉልኛ... ይህንን ጅማሬ የት እንደሚደርስ መገመት አስቸጋሪ አይመስለኝም ፡፡ አረ ምኑ ቅጡ...ያሰኛል፡፡ የእስዋ የልብስና የጌጣጌጥ አይነት...የወርቅ ጥያቄ...እሱን እንደምንም ተወጣሁት ስል ደግሞ ሌላ ነገር መጣ፡፡ እንዲህ አለችኝ፡፡
 ሳ/        እኔ የምልህ?
እኔ/    እ...ህ...
 ሳ/        የእኔን ቤተሰቦች አቅም ያው  ውቀዋለህ
እኔ/      አዎን አውቀዋለሁ...እናስ...
 ሳ/        እናማ...
       እናማ ...ወገኖቼ... የእነሱን ቤት ድግስ መደገስ ነበረብኛ...፡፡ ለምን እንደአቅማቸው አድርገው አያወጡሽም ብላት ምን አቅም አላቸውና ሆነ መልሱ፡፡ እኔ አንቺን እንጂ ድግሱን እኮ አልፈልግም ብልም ...ካልፈለግህ ተወው እንጂ እኔ ደግሞ ሕይወ  ነው ...ነበር መልሱዋ፡፡ የኮተቤዋ ሳቂ  እንዳለችው ...ጠላ ተደፍድፎ...ስንት ነገር ተዘጋጅቶ ሆነና ነው እንጂ እኔም የፍቺ ደብዳቤዬን ባቀርብ ደስ ይለኝ ነበር፡፡ አልቀረም ተጋባን፡፡ ለማንኛውም ያቺ ለሰው በእጅጉ  ስብ የነበረች የልጅነት ጉዋደኛዬ ድሮ እንደማውቃት አላገኘሁዋትም፡፡በልጅነት አቅሜ... ላይ  ች ብዬ...ወንድ ነኝ ...አላውቅበትም ሳልል እራሴ ሳምቡሳና ፓስ  ጠብሼ...ሻይ ቀቅዬ ያፈራሁትን ገንዘብ ያለርህራሄ ነበር በሰርግ ሽፋን የተጫወተችበት፡፡
      ...ኑሮው እንዴት ሆነ? ይመስለኛል ቀጣዩ ጥያቄ፡፡ ትክክል ነው፡፡ ኑሮውማ እንደእኔ መሰረተ ደሀ የሆነ ሰው ኑሮ ሳይሆን ቅብርር ያለ ሀብ ም ሰው ኑሮ ነው እንዲሆን የ ሰበው፡፡ ለማስረዳትም ብሞክር ልትቀበለኝ አልቻለችም፡፡ አረ ስለፍቅር ብዬ ልመናዬን ቀጠልኩ፡፡ አልሆነልኝም ፡፡ በዚህ መሀል አንድ ልጅ ተወልዶአል፡፡
አንድ ቀን ...ከእሁዶች መሀል የማልረሳት እሁድ መጣች፡፡ የባለቤ  ወንድም ...አጎት...እና የማላውቃቸው ትልቅ ሰው ወደቤ ችን መጡ፡፡ እኔ ደግሞ እሁድ ከሌላ ቀን ይበልጥ የስራ ቀኔ ነውና በጠዋት ተዘገጃጅቼ ልወጣ መኪና እያሞቅሁ ነበር፡፡ እንግዶቹን ከበር ላይ ይዤ ወደሳሎን አመራሁ፡፡ እሱዋንም ጠራሁ፡፡ ምነው በደህና ነው? አልኩዋቸው፡፡ ወንድምዬው ቀጠለ፡፡
፵አአይ... በደህና ነው ፡፡ ግን ...መቼም ከተጋባችሁ ይኸው ሁለተኛ አመ ችሁ ነው፡፡እናም ልጅቷ ...ሲሉ...ልጅቷ ማለት ህጻኑዋ? አልኩዋቸው...አይደለም...አይደለም...ሚስትህ እንጂ...እሺ...አልኩ፡፡ ያለህን ንብረትና ገንዘብ በትክክል አውቃ ቢቻል በስምዋ...ባይቻል ደግሞ በሁለ ችሁም ስም እንዲሆን ለማድረግ ጠይቁልኝ ስላለችን ነው ማልደን የመጣነው፶ አሉኝ፡፡

እኔም በነገሩ እጅግ ተገርሜ ...ወደአላሰብኩት ነገር ስለከተቱኝ ተበሳጭቼ...በቃ እስዋ ከገባች ጀምሮ ያፈራነውን ገንዘብና ንብረት ትንገረኝና አካፍላ ለሁ፡፡ ከዚያ ውጪ ግን ልጄን አሳድጋለሁ፡፡ ከእርስዋ ጋር ግን የባልና ሚስትነት ሁኔ  እዚህ ላይ ያበቃል... ብዬ እነሆ ዛሬ ከልጅነት ጉዋደኛዬ ...ከዛሬዋ ባለቤ  ጋር በፍቺ ሂደት ላይ እንገኛለን፡፡
      እዚህ ላይ እኔ ሳስብ የነበረው በስማችን መሬት ገዝተን ፣ቤት ሰርተን ፣ለእስዋ መኪና ገዝቼ እያልኩ ሲሆን እሱዋ ግን ባላሰብኩት መንገድ ያውም እኔን ሳ ናግረኝ በጠዋት በሽማግሌ ስ ስጠይቀኝ...አሀ...ለካስ ገንዘቤን እንጂ እኔን ፈልጋ አልነበረም እንጋባ ስላት እሺ ያለችኝ... ወደሚለው ነጥብ ነው እንዳመራ ያደረገችኝ፡፡ ወደሁዋላ ተመልሼ በጋብቻው ወቅትም የሆነውን ሳስበው ... እጅግ በጣም እበሳጨኝ ጀመር፡፡ እና የኮተቤዋ ሳቂ  ጋብቻ ለመመስረት መጠናናት እስከምን ያለችው ነገር ...እኔም እስከምን እንደሆነ አላውቅም፡፡ ምክንያቱም ከማጥናትም በላይ በጣም የማውቃት እንደእራሴ የማምናት ልጅ እንዲህ ሆና በመገኘቱዋ በጣም ነው ያዘንኩት፡፡ ለማንኛውም የትዳር ነገር ቢሳካ እጅግ ጠቃሚ ቤተሰባዊ ተቋም በመሆኑ ከማጥናትም በላይ  ከጥሩው ትዳር ቸር ይግጠመን ብሎ መጸለይ እንደሚያስፈልግ አምኛለሁ ፡፡  
       *********

          Cord Blood---ከእትብት የሚገኝ ደም
                                                                                                            ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ

           ---ኮርድ ብለድ ማለት ልጅንና የእንግዴ ልጅን ከሚያገናኘው መስመር ማለትም  ከእትብት የሚገኝ ደም ለማለት ነው፡፡ ይህም ማለት ሕጻኑ በእትብቱ አማካኝነት ከእንግዴ ልጅ ጋር ይገናኛል--እንግዴ ልጁ ደግሞ ከእናትየው አስፈላጊውን ደም የሚወስድ ሲሆን እትብቱ ይህንን ከእናትየው የሚመጣውን ደም እንደቲዩብ በማገልገል ወደሕጻኑ እንዲገባ ያደርጋል፡፡ ወደጽንሱ የደረሰው ደም በተጣራ መልኩ ልጁ ከተጠቀመበት በሁዋላ ደሙ በድጋሚ እንዲጣራ ወደ እንግዴ ልጅ በዚሁ በእትብቱ አማካኝነት ይመለሳል፡፡ እንግዴ ልጅ በልጅና በእናት መካከል ምግብና ኦክስጂን መለዋወጥ እንዲኖር የሚያገለግል አካል ወይንም ክፍል ነው፡፡ ሕጻኑ በሚወለድበት ጊዜ እትብት ከህጻኑ እንብርት ጥቂት እንዲቀር ተደርጎ ሲቆረጥ ከእንግዴ ልጅ ጋር በሚቀረው እትብት ውስጥ ተጠራቅሞ የሚቀረው ደም ነው            --- ከእትብት የሚገኝ ደም የሚባለው፡፡ የዚህን ደም ምንነትና ጥቅም የሚያብራሩልን  ዶ/ር ዳዊት ደሳለኝ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ህክምና ፋክልቲ የቅድመ ምረቃ ተባባሪ ዲንና ረዳት ፕሮፌሰር እንዲሁም የማህጸንና ጽንስ ሕክምና ባለሙያ ናቸው፡፡
* * *                * * *
አንድ ልጅ ሲወለድ ከእትብት ውስጥ የሚገኘው ደም ከአንድ ስኒ ማለትም ሰላሳ ወይንም ከሀምሳ ሚሊ ሊትር እስከ መቶ ሚሊ ሊትር የሚበልጥ አይደለም፡፡ በእርግጥ የሚገኘው ደም መጠን ልጁ ከተወለደ በሁዋላ እትብቱ እስኪቆረጥና እስኪቋጠር ድረስ እና ደሙ እስኪወሰድ ድረስ በሚወስደው ጊዜ ከፍና ዝቅ ሊል ይችላል ፡፡
ከእትብት የሚገኘው ይህ ደም ለደም ማነስ ብቻ የሚሰጥ ሳይሆን የተለያዩ የጤና ሁኔ ዎችን ለመሟላት የሚያገለግል ነው ፡፡ ኮርድ ብለድ መጠኑ ትንሽ ቢሆንም የሴሎቹ ጥቅም ግን በጣም ብዙ ነው፡፡ ምክንያቱም ከህጻን የሚገኘው ሴል የሚያድግ ሴል ሲሆን ከአዋቂ ግን የሚገኘው ሴል እድገቱን የጨረሰ ነው፡፡ ከህጻን ደም የሚገኘው ሴል ስቲም ሴል ይባላል፡፡
ስቲም ሴል ከአንድ ሴል ወደተለያየ የደም ሴል ወይንም ወደተለያየ የሰውነት አካል መቀየር የመቻል አቅም ያለው ሴል ነው፡፡ ይህ ሴል ግን ከአዋቂ ደም አይገኝም፡፡ ከእትብት የሚገኝ ደም አወሳሰዱ በስራ ላይ ባለው ዘዴ ከአዋቂዎች እንደሚለገሰው ደም በጎ ፈቃደኝነትን ወይንም ልገሳን የሚጠይቅ እሺ እሰጣለሁ ወይንም አልሰጥም የሚባልበት አይደለም፡፡ ከእትብት የሚገኝ ደም የሚጣል ነው፡፡ ደሙ በመወሰዱ እናትየውንም ሆነ ህጻኑን የሚጎዳ ምንም ነገር የለውም፡፡ የእትብት ደም በመወሰዱ የሚያጋጥም ምንም ህመም የለም፡፡ ደሙ በመወሰዱ የእናትየውም ሆነ የህጻኑ ደም ምንም አይቀንስም፡፡ ከእትብት የሚገኝ ደም የእናትየውንም ሆነ የህጻኑን መብት ምንም የሚነካ ነገር የለውም፡፡ የእትብት ደም ተወስዶ በምርምር እንደአስፈላጊነቱ ከስራ ላይ ቢውል ግን ደሙ የጎደለ የሰውን አካል ለማሟላትና በህመም ስቃይ ላይ የሚገኝን ህይወት ለመ ደግ የሚያስችል ነው፡፡ የስቲም ሴል ምርምር በውጭው አለም በከፍተኛ ሁኔ  ትኩረት የተሰጠው ነው፡፡ ለምሳሌ አሜሪካ በዚህ ሴል ላይ ለሚደረገው ምርምር በፕሬዝዳንት ቡሽ ጊዜ ትኩረት ተነፍጎት የቆየ ቢሆንም አሁን በፕሬዝዳንት ኦባማ ጊዜ ግን በጀት ተመድቦለት በተገቢው ሁኔ  እየተሰራ ነው፡፡ ስለሆነም             ከእትብት ከሚገኘው ደም ስቲም ሴሎችን ማግኘት ቀላሉ መንገድ ሆኖአል፡፡

ስቲም ሴል ብዙ ጊዜ የሚገኘው የወንድ የዘር ፍሬና የሴት እንቁላል  በሚገናኝበት ጊዜ መጀመሪያ በሚፈጠረው        ኤምብሮዮ ነው፡፡ የሰው አካል የሚሰራው ከዛ ከ        ውስጥ ነው፡፡ መጀመሪያ ላይ ሁሉም ሴሎች አንድ አይነት ሲሆኑ ከዛ በሁዋላ ግን እራሳቸውን እየለዩ አንዱ ጉበት ሌላው ልብ እንዲሁም እግር፣ እጅ የመሳሰለወ ሁሉ በተለያየ ሁኔ  ይፈጠራል፡፡ ያንን የሚለየው እውስጡ ያለው ጂን ነው፡፡ እንደዚህ የመሆን አቅም ያላቸው ሴሎች በተገቢው ሁኔ  የሚገኙት ደግሞ ከህጻን ልጅ እትብት ከሚገኘው ደም ውስጥ ነው፡፡ እናም በኮርድ ብለድ የሚገኘው ደም ለደም ማነስም የሚያገለግል ቢሆንም ከዚያ በላይ ግን ለሌሎች የጤና አገልግሎቶች ሊጠቅም የሚችል ነው፡፡ በእርግጥ ከደም ማነስ ጋር በተያያዘ ለምሳሌ በወባ ምክንያት ለሚፈጠረው የደም ማነስ ሲወሰድ የህጻን የደም ሴል አይነቱ ለወባ መከላከል የሚያገለግል በመሆኑ የተለየ ጥቅም አለው፡፡ የቀይ ደም ሴልና የውሀው መጠንም በፐርሰንት ምን ያህል ነው ሲባልም ከአዋቂዎች ጋር ሲነጻጸር ከእትብት የሚገኘው ደም ብዙ የቀይ የደም ሴል ያለው ነው፡፡ ስለዚህ ከአዋቂ በአንድ ጊዜ የሚወሰደው ደም ከአራት መቶ ሲሲ በላይ ቢሆንም ከእትብት የሚገኘው ደም ግን ግማሹ ሊበቃ ይችላል፡፡

ከእትብት ከሚወሰደው ደም የሚገኘው ስቲም ሴል ጥቅምን በዝርዝር መመልከት ይቻላል፡፡

  • ስቲም ሴል የተለያዩ በሽ ዎችን ማለትም እንደካንሰር፣ በቫይረስ ምክንያት የሚመጡ እና ሌሎችንም የውስጥ ደዌ አይነት ሕመሞችን ለመ ደግ የሚያስችሉ ናቸው፡፡  ለምሳሌ አንድ ሰው የስኩዋር በሽ  ህመምተኛ የሚሆነው ጣፊያ የተሰኘው የሰውነት አካል ኢንሱሊን የተሰኘውን ንጥረ ነገር ማምረት ሲያቆም ነው፡፡ በስቲም ሴል  ፺ስኩዋር በያዘው ጂን ማለት ነው፻ አማካይነት ግን ወደጣፊያው በበቂ መጠን ሴሎቹ እንዲገቡ ቢደረጉ ይህንን ጣፊያ ሊያመርተው ያልቻለውን ኢንሱሊን እንደገና እንዲያመርት ማድረግ ስለሚያስችል ለስኩዋር በሽ  በየጊዜው ኢንሱሊን መወጋት ይቀርና ሰውነት በሚያመርተው ኢንሱሊን ይተካል ማለት ነው፡፡
  • በስቲም ሴል አማካኝነት የአእምሮ ሕመምንም ማስወገድ ቻላል፡፡ ፺በአንድ ወቅት አንዲት ሴት በደረሰባት አደጋ ከፍተኛ የአእምሮ መጎዳት ስለደረሰባትና ጭንቅላትዋ ውስጥ ብዙ ደም በመፍሰሱ ምክንያት ለሶስት ወር ያህል በሆስፒ ል ውስጥ እራስዋን ሳ ውቅ ፺ኮማ፻ ውስጥ የቆየች ስትሆን ስቲም ሴል ወደ አእምሮዋ ሲገባላት ግን በአንድ ወር ውስጥ መነጋገር መንቀሳቀስ ችላለች፡፡
  • አጥንትን በስቲም ሴል መስራት ተችሎአል፡፡ እስከአሁን በተለመደው የህክምና ዘዴ በተለያየ ምክንያት አጥንት ቢጎዳ የሚደረገው ህክምና ከአንዱ ቦ  ማለትም በወገብ አካባቢ ከሚገኙ የአጥንት ክፍሎች ወስዶ ወደሌላው የመተካት ስራ ነው፡፡ ነገር ግን በስቲም ሴል ወይንም በጀነቲክ ሴል አማካኝነት አጥንትን መስራት ተችሎአል፡፡
  • አንድ ሰው ቆዳው ተቃጥሎ ወደህክምናው ቢመጣ በተለመደው የህክምና አሰራር ሊደረግለት የሚችለው ከሌላ የሰውነት ክፍል ቆዳ ወስዶ የተጎዳውን ቆዳ መተካት ሳሆን በስቲም ሴል አማካኝነት ግን ከሌላ ሰውነቱ ላይ ቆዳ መቅፈፍ ሳያስፈልግ እንደ አዲስ መስራት ይቻላል፡፡
  • የሚበላ ስጋ የሚገኘው ከከብት ሲሆን በስቲም ሴል አማካኝነት ግን በላቦራቶሪ ውስጥ ለምግብነት የሚውል ስጋን መስራት ተችሎአል፡፡ ተመራማሪዎች ለዚህ እንደምክንያት ያቀረቡትም ከከብት የሚወጣው ትንፋሽ የአየር ጸባይን ለመበከል አስተዋጽኦ የሚያደርግ ስለሆነ ከብትን ማርባት እንዲቀንስ ከሚል አስተሳሰብ ነው፡፡ 1/3ኛው የአለም ከርቦንዳይ ኦክሳይድ ከከብት ትንፋሽ የሚወጣ ነው፡፡
  • ኤችአይቪ ኤይድስን በሚመለከት በተለይ ነጭ የደም ሴሎች ስራቸውን እንዲጀምሩ ለማድረግ በስቲም ሴል የተለየ ጂን ተሰጥቶአቸው ኤችአይቪ ቫይረስ ያለባቸውን ሴሎች የመግደል አቅም እንዲኖራቸው ተደርጎ እየተሰራ ነው፡፡ ስለዚህ ይሄ በወደፊቱ አካሄድ ቫይረሱን ለማጥፋት ይረዳል ተብሎ ይ ሰባል፡፡
  • ከማህጸንና ጽንስ ጋር በተገናኘ በተለይም በመውለድ ሁኔ  የሴት ልጅ እንቁላል ቢቋረጥ ወይንም የወንድ ዘር ልጅ ለማምረት ባይችል እስቲም ሴሎች ሆርሞንን እያስተካከሉ እንቁላሉም እንዲመረት የወንድ የዘር ፍሬውም ዘር ለመፍጠር እንዲችል ስለሚያደርጉ ልጅ መውለድን ሊያስገኙ ይችላል፡፡ ይህ ግን እስከአሁን በጥናት ላይ ያለ ነው፡፡
  • ሌላው የማረጥ ሁኔ  ነው፡፡ በእድሜ ወይንም በአንዳንድ ሁኔ ዎች ከሚከሰተው የወር አበባ መቆም ጋር በተያያዘ በሆርሞን መቀነስ ምክንያት የሚከሰቱ የተለያዩ ሕመሞች ሲኖሩ  ፺የአጥንት መሳሳት፣ የልብ ሕመም፣ የሰውነት ሙቀት ...ወዘተ ፻ ይህንን ለማስ ገስ የሚደረገው የህክምና እርዳ  ሆርሞን መስጠት ነው፡፡ በስቲም ሴል የሚሰጠው አገልግሎት ግን ሰውነት እራሱ ሆርሞንን እንዲፈጥር ማድረግ  ስለሆነ እጅግ ጠቃሚ የምርምር ውጤት ነው፡፡
ስቲም ሴሎች የተለያዩ ናቸው፡፡ ከደም ሴሎች ጋር የተገናኘና፣እንደ ኢንሱሊን መስሪያ የሚሆኑ እንዲሁም የሰውነት አካልን የሚተኩ የመሳሰሉ ናቸው፡፡ ይህ ሕጻናት ሲወለዱ ከእትብት ከሚገኘው ደም የሚገኘው ሴል ምርምሩም ሆነ የደሙ አወሳሰድ በሌላው የአለም ክፍል የተለመደ ቢሆንም እስከአሁን በእኛ አገር ግን በስራ ላይ አልዋለም፡፡በሙያው ከተሰማሩ የውጭ ባለሙያዎች እንደምንረዳው ግን ጠቀሜ ው የጎላ ከመሆኑ አንጻር ወደፊት በአገራችንም ወደተግባሩ ቢገባ ብዙ የጤና መጉዋደሎችን ለማስተካከል እንደሚረዳ እሙን ነው፡፡  

*****************

ዛሬም አለ እንዴ..
                               ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ

 

      ሰላምና ጤናን ለላንቺና ላንተ አምድ ዝግጅት ክፍል  እላለሁ፡፡ እኔ ይመኙሻል ለ ሪክ እባላለሁ፡፡ ትውልዴ ወደ ሰሜንሸዋ ተጉለትና ቡልጋ ሲሆን እድገ  ግን አዲስ አበባ ወደ ኮተቤ አካባቢ ነው፡፡ ዛሬ የእኔ እድሜ ወደ አምሳዎቹ መጨረሻ አካባቢ ደርሶአል፡፡ አስተያየት ልልክላችሁ ካሰብኩ ቆይቻለሁ፡፡ ነገር ግን ስፈራ ስቸር ከዛሬ ነገ ስል እስከዛሬ ቆየሁ፡፡ አሁን ግን የተለያዩ አስተያየቶች በጋዜጣው ሲቀርቡ በማየ  ተደፋፍሬ እነሆ ለአንባቢ በሉልኝ  ብያለሁ፡፡
      ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ እኔና ጉዋደኞቼ በእድሜአችን ገና ወደ አስራ ስድስትና አስራ ሰባት አመት ሲሆነን ነው ከወንድ ጉዋደኞች ጋር መዋል የጀመርነው፡፡  ዲያ በዚያን ጊዜ እንዲህ እንደአሁኑ  ዘና ያለ አዋዋል አልነበረም፡፡ እንዲያው መቼም አዲስ አበባ እንዲህ እንደአሁኑ ፊልሙ፣  ክ ቤቱ እንደልብ ሳይመሰረትባት ነባሮቹ እነ ሲኒማ ኢትዮጵያ ነበሩ መደሰቻዎቻችን፡፡  ክ ቤቶቹም በውስን ደረጃ ነባር የሚባሉት ነበሩ፡፡  ዲያ አብረው ከዋሉ መቼም ነገር አይጠፋምና እየዋለ እያደረ አንዳንድ ችግር መከሰቱ አልቀረም፡፡ ለችግሩ ከተጋለጡት ውስጥ ቀዳሚዋ እኔ ነበርኩ፡፡ ከወንድ ጉዋደኛዬ ጋር ስዝናና ተሳሳትንና በአስራ ሰባት አመ  እርግዝና ተከሰተ፡፡ ለጉዋደኛዬ ሳማክረው ከጉዋደኞችሽ ተማከሪና መላ ፈልጊ አለኝ፡፡ መላ ተባለና ጽንሱን ለማስወረድ የወሰድነው እርምጃ ግን እጅግ ከባድ መከራ ውስጥ ነበር የከተተኝ፡፡ በዚያ ጊዜ ተፈጥሮ በነበረው ኢንፌክሽን ምክንያት ልጅ አልባ ሆኜ ቀርቻለሁ፡፡ የእኔውስ ደግ...እናንተ... የባሰው ደግሞ የጉዋደኛዬ ነው፡፡ አለም ተድላ የተባለችው አብሮ አደግ ጉዋደኛችን ከፍቅረኛዋ  ጋር በነበራቸው ስምምነት መሰረት ምናልባት እርግዝና ቢከሰት ሊያገባት ነበር የተስማሙት፡፡ የፈሩት አልቀረም እርግዝናው እውን ሲሆን ግን እኔ ምንም ማድረግ አልችልም የፈለግሽውን ማድረግ ትችያለሽ የሚል መልስ ነበር የሰጣት፡፡ ቤተሰብ ከሚያውቅብኝ የፈለገው ነገር ይምጣ በማለት ጽንሱን ለማስወጣት በወሰደችው እርምጃ ግን ሕይወቷ አለፈ፡፡ በእርሱዋ ሕይወት ማለፍ  የጉዋደኞ  የሁላችንም ሞራል ነበር የተጎዳው፡፡ በጣም አዘንን፡፡
      ከላይ የገለጽኩዋቸወ ችግሮች የመከሰ ቸው ምስጢር በዘመኑ በህጋዊ መንገድ ጽንስን ማቋረጥ የማይቻል ስለነበር ነው፡፡ በባህላዊውም ይሁን  በዘመናዊ መንገድ እየተጠቀሙ በድብቅ ይህንን ድርጊት በሚፈጽሙ ሕገወጥ ሰዎች እጅ የብዙ ሴት ልጆች ሕይወት አልፎአል፡፡
      አሁን ይህንን ጉዳይ ማንሳት ለምን አስፈለገሽ ትሉኝ ይሆናል፡፡ ትክክል ነው፡፡ ማስረዳት አለብኝ፡፡ ከአንድ አመት በፊት ወደአገር ቤት ሄጄ ሳለ ነበር አንዲትን እናት ያገኘሁት፡፡ እጅግ አዝናለች፡፡ ምነው ምን ሆነሻል ብዬ ብጠይቃት የነገረችኝ ነገር እጅግ ነበር ያሳዘነኝ፡፡ ልጅቷ ተገዶ መደፈር ይደርስባ ል፡፡  ዲያ በዚያው እርግዝና በመከሰቱ ምክንያት ለጉዋደኞ   ማክራለች፡፡ ምን ችግር አለ ... እከሌ የሚባል ሰው እኮ አለ፡፡ የእነ እከሌትን...የእነ እከሊትን... እኮ እሱ ነው ያስወጣላቸው ይሉ ይመክሩና ተያይዘው ይሄዳሉ፡፡ ምን አይነት ድርጊት እንደተፈጸመባት ለመናገር እንኩዋን ሳትችል ሰውነቷ እንደተነፋፋ...በትኩሳት አንደነደደች ...ሐኪም ቤት እንኩዋን ብንወስዳት ሊረዱዋት ስላልቻሉ ሕይወቷ አለፈ ... ብላ ሐዘኑዋን የሟች እናት ትገልጽልኛለች፡፡
እኔ ግን ወደሁዋላው ዘመን ተመልሼ እኛ ያሳለፍነውን እና አሁን ያለውን ማነጻጸር ነበር የያዝኩት፡፡ ዛሬም አለ እንዴ ይሄ ነገር ብዬ ነበር እራሴን የጠየቅሁት፡፡
      በአሁን ጊዜ በኢትዮጵያ ጽንስን ለማቋረጥ የሚያስችል ሕጋዊ ድንጋጌ መኖሩን ሰምቻለሁ፡፡ ከአንዳንድ መረጃዎችም እንደተረዳሁት እንዲያውም በኢትዮጵያ የወጣው ይሄ ድንጋጌ የብዙዎችን ሕይወት ለመ ደግ ያስቻለ መሆኑን ነው፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ሴቶች መብ ቸውን ያላወቁ ወይንም የት ፣መቼ፣ምን ማድረግ እንደሚገባቸው ግራ የተጋቡ አሉ የሚል ድምዳሜ ላይ አድርሶኛል ከገጠር ያገኘሁዋት እናት የሰጠችኝ መረጃ፡፡
      በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ያለው ችግር በከተሞች የለም ማለት አይቻልም፡፡ እውቀቱ አለን ሐኪሞች ነን በሚሉ አንዳንድ የተሳሳቱና ለገንዘብ ያደሩ ሰዎች ኣማካኝነት አንዳንድ ሴት ልጆች ተ ለው ህይወ ቸውን ከሚያጠፋ እንዲሁም ጤናቸውን ከሚያቃውስ ነገር እንዳይገቡ አስቀድመው እንዲጠነቀቁ እራሳቸውን ከአደጋ እንዲከላከሉ ማድረግ የሚገባ ይመስለኛል፡፡

                                    ይመኙሻል ለ ሪክ ፺ከኮተቤ፻
          *           *           *           *
           የውርጃን አለምአቀፋዊ ገጽ  ስንመለከት ሕገወጥ ውርጃ ከፍተኛውን የእናቶችን ሞት የሚያስከትል የህይወት ጠንቅ ሲሆን ሴቶች ከህልፈት እንኩዋን ቢድኑ ብዙዎቹ በዚህ ምክንያት ለተለያዩ የጤና እክሎች እንደሚዳረጉ ጥናቶች ያሳያሉ፡፡ በአለም አቀፍ ደረጃ ፺20፻ ሀያ ሚሊዮን ያህል ህገወጥ ውርጃዎች በየአመቱ ይፈጸማሉ፡፡ ይህም ማለት በየአስር እርግዝናዎች አንድ ህገወጥ ውርጃ ወይንም ከሰባት ወሊድ አንድ ህገወጥ ውርጃ እንደሚፈጸም ስሌቱ ያስረዳል፡፡ በአለምአቀፍ ደረጃ ከሚፈጸሙት ህገወጥ ውርጃዎች 90%  በ ዳጊ አገሮች የሚደረግ መሆኑን ጥናቱ ያስረዳል፡፡
      ህገወጥ ውርጃ ለእናቶች ሞት ምክንያት ናቸው ከሚባሉት መካከል ሲሆን በአለማችን በህገወጥ ውርጃ ምክንያት በየአመቱ ለህልፈት የሚዳረጉ ሴቶች ቁጥር ወደ 200.000 ሁለት መቶ ሺህ ይደርሳል ተብሎ ይገመ ል፡፡ ይህም ማለት በተለያዩ ምክንያቶች ከሚከሰተው የእናቶች ሞት ከ13 እና 20 በመቶ መካከል ያለው የሚከሰተወ በህገወጥ ውርጃ መሆነን ነው የሚያሳየው፡፡
      በየአመቱ ፺35 ፻ ሰላሳ አምስት ሚሊዮን የሚሆነው ህገወጥ ውርጃ የሚፈጸመው በ ዳጊ አገሮች ሲሆን በንጽጽር ሲ ይ በአደጉ አገሮች የሚከናወነው ህገወጥ ውርጃ ግን 7 ሚሊዮን ያህል ብቻ ነው፡፡
      አንዳንድ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት ደግሞ  ወደ ፺182፻ አንድ መቶ ሰማንያ ሁለት ሚሊዮን ከሚሆኑት በ ዳጊ አገሮች ከሚኖሩ እርግዝናዎች ውስጥ ከአንድ ሶስተኛው በላይ ያልተፈለገ እርግዝና በመሆኑ ምክንያት ህገወጥ ውርጃው የሚከናወንባቸው ሲሆኑ ወደ 11% የሚሆኑት ውርጃዎች ግን በህገወጥ መንገድ የሚካዱ ናቸው ፡፡
      ወደ ኢትዮጵያ ሁኔ  ስንመለስ አማካይ የጋብቻ እድሜ በኢትዮጵያ በሚል ባለፈው አመት የወጣ አንድ መረጃ እንደሚያሳየው በኢትዮጵያ አማካይ የጋብቻ እድሜ 16 አመት መሆኑንና ከጠቅላላው እርግዝና ከ50% በላይ የሚሆኑት እርጉዞች በእድሜያቸው ከ15 አመት በ ች ያሉ ሴት ሕጻናት መሆናቸውን ያስረዳል፡፡ ይህም ያልተፈለገ እርግዝና ከሚለው የሚካተት ነው፡፡ በእድሜያቸው ከ20-24 አመት የሚሆኑት ሴቶች 37 % የሚሆነውን ያልተፈለገ እርግዝና የሚሸፍኑ ሲሆኑ ያልተፈለገ እርግዝና መሆኑ ደግሞ ውርጃ እንዲያካሄዱ መንገድ የሚከፍት ነው፡፡ በኢትዮጵያ አንዳንድ ሆስፒ ሎች ውስጥ የተደረገ ጥናት እንደሚያሳየው  ከሚ ዩት ተገልጋዮች ወደ 60%  የሚሆኑት የማህጸንና ጽንስ  ካሚዎች ሲሆኑ ከእነዚህም አብዛኞቹ ከህገወጥ ውርጃና ተያያዥ ችግሮች ጋር በተያያዘ ጤናቸው የተጉዋደሉ ናቸው ይላል መረጃው፡፡ በኢትዮጵያ ከአንድ ሺህ ወላዶች ውስጥ ወደ 104 የሚሆኑት እድሜያቸው ከ15-19 አመት የሚሆኑ ሴት ህጻናት ናቸው፡፡ የሴት ህጻናቱ እርግዝና ከተለያዩ ምክንያቶች አኩዋያ ሲ ይ ህገወጥ እርግዝና ከሚል ይፈረጃል፡፡ ህገወጥ እርግዝናን ተከትሎ በአብዛኛው ህገወጥ ውርጃ ይፈጸማል፡፡ በኢትዮጵያ በተለያዩ ሆስፒ ሎች የተካሄደው ጥናት እንደሚያስረዳው ከእናቶች ሞት ወደ 40% የሚከሰተው በውርጃና ከውርጃ ጋር ተያያዞ በሚከሰት የጤና ችግር  ሳቢያ ነው፡፡
      እንደውጭው አቆጣጠር ሜይ 2005ዓ/ም የኢትዮጵያ መንግስት የሴቶችን ሕይወት የሚያጠፋውን ህገወጥ ውርጃ ለማስቀረት በተለያዩ አሳማኝ በሆኑና በመረጃ በተደገፉ ምክንያቶች ጽንስን በህጋዊ መንገድ ማቋረጥ እንደሚቻል የሚያሳይ ድንጋጌ አውጥቶአል፡፡ ረዘም ላሉ ጊዜያት በስራ ላይ የነበረው የወንጀለኛ መቅጫ ህግ ተሸሽሎ አዲሱ የወንጀል ህግ ሲጸድቅ መፍትሔ ከሰጠባቸው ጉዳዮች አንዱ ህገወጥ ውርጃን ለማስቀረት የትኛውም የህክምና ተቋም በህጉ ላይ በሰፈሩት ምክንያቶች ጽንሱን ማቋረጥ እንደሚቻል በመደንገጉም በተለይም በአስገድዶ መድፈር ምክንያት አለአግባብ ሳይ ቀድ የሚመጣውን እርግዝና በተገቢው መንገድ ህግ በሚፈቅደው መሰረት መፍትሔ እየተሰጠበት በመሆኑ የብዙዎችን ሕይወት ለመ ደግ ተችሎአል፡፡
      በኢትዮጵያ በወጣው ህግ መሰረት ጽንስን ማቋረጥ የሚቻልባቸው ምክንያቶች

  • ተገዶ በመደፈር ምክንያት የሚከሰት እርግዝና፣
  • ከጤና አኩዋያ እናትየው በህክምና ሊረዳ የማይችል ሕመም ሲኖራት፣
  • የጽንሱ መኖር ለእናትየው ጤናና በሕይወት ላይ አደጋ የሚያስከትል ሲሆን ፣
  • በአካልና በአእምሮ ሳይበስሉ ፺ልጅ በመሆን፻ የተረገዘውን ልጅ ወልዶም ለማሳደግ የማይቻል መሆኑ ሲረጋገጥ፣

ከዚህም ውጭ እንደአስፈላጊነቱ ከሚ ዩት ውስጥ የማበራዊና ኢኮኖሚያዊ ሁኔ ዎች ይጠቀሳሉ፡፡
ስለዚህ ተሳ ፊያችን እንደጠቀሱት ሴቶች ጽንስን ማቋረጥ ሲሹ በአቅራቢያቸው ወደሚገኘው የህክምና ተቋም በመሄድ ሁኔ ውን ማስረዳት እና ተገቢውንና ህጋዊውን  አገልግሎት ማግኘት ይገባቸዋል፡፡ ሴት ሕጻናቱ እራሳቸውን ከጥቃት እንዲከላከሉ የማስቻሉ ተግባር ከወላጆች ከትምህርት ማህበረሰብ እና ከሁሉም ማለትም ከሚመለከ ቸው አንላትና የህብረተሰብ ክፍሎች የሚጠበቅ  ይሆናል፡፡

 **************************         

...መኖር ይቻላል...
                                                      ፀሐይ ተፈረደኝ ከኢሶግ


የኤችአይቪ ኤይድስ መረጃ ማእከል ፵በጎ እናድርግ፡ ህይወትን እንለውጥ፶ በሚለው እትም ባወጣው መረጃ ሰዎች በኤችአይቪ ቢያዙም ጤናማ እና ምር ማ  ሆነው ኑሮአቸውን መምራት ይችላሉ፡፡ ይህንን ለማሳካት ግን ራሳቸውን መንከባከብ ይኖርባቸዋል ፡፡
      መረጃው በተጨማሪም እንደሚያስረዳው በሽ  የመከላከል አቅምን ማጠናከር ለኤችአይቪ ፖዘቲቭ ሰዎች በጣም ጠቃሚ ነው፡፡ ይህም በሰውነ ቸው ውስጥ የሚገኘውን የኤችአይ ቪ መጠን ቀንሶ እንዲቆይ ያደርገዋል፡፡ በሽ ን የመከላከል ስርአ ቸው ከተዳከመ ግን ለሕመም የመጋለጥ እድላቸው የሰፋ እና በሰውነ ቸው ውስጥ የሚኖረው የቫይረስ ቁጥርም የበዛ ይሆናል፡፡ ጠንካራ በሽ ን የመከላከል አቅም ያላቸው ከኤችአይቪ ጋር የሚኖሩ ሰዎች ሌሎች ተሀዋስያንና ቫይረሶች በቀላሉ አጥቅተው ለህመም አይዳርጓቸውም፡፡
      ከኤችአይቪ ጋር የሚኖሩ ሰዎች በጤናማነት መኖር ይችላሉ የሚለውን የሚያረጋግጡልን ኤችአይቪ ፖዘቲቭ እናቶች ለዚህ አምድ በእንግድነት ሀሳባቸውን ያጋራሉ፡፡ ኤች ጸሐይ የተሰኘ በአሜሪካ የሚገኘው የጆን ሆፕኪንስ ዩኒቨርሲቲ ኤችአይቪን ለመከላከል በኢትዮጵያ በሚያደርገው ድጋፍ       ኤችአይቪ ከእናት ወደልጅ እንዳይተላለፍ ለማድረግ ለሚሰሩ ስራዎች እገዛ ደርጋል፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘም        ’                 የእናቶች የድጋፍ ቡድን ማለትም ከኤችአይቪ ጋር የሚኖሩ እናቶች በተለያዩ ሁኔ ዎች ላይ ግልጽ የሆነ ውይይት የሚያደርጉበትን መድረክ በተለያዩ ሆስፒ ሎች ውስጥ ፈጥሮአል፡፡ በጋንዲ እና ጳውሎስ ሆስፒ ሎች የቡና ጠጡ ፕሮግራም ላይ ተሳ ፊ የሆኑት እናቶች ከኤችአይቪ ጋር በተያያዘ አንዳንድ ሀሳቦችን ሰንዝረዋል፡፡
( ( ( ( ፵አዲስአበባመርካቶአካባቢ ነው ተወልጄያደግሁት፡፡እናትነበረችኝ፡፡አባ ከሞተበሁዋላእናመደገፍስለነበረብኝብዙ ተንገላትቼነው የኖርኩት፡፡በሁዋላምቀደምሲልሌላትዳርነበረኝ፡፡ከሱ ጋርከተፋ በሁዋላሌላባልአግብቻለሁ፡፡ቀደምያለው ባለቤ ከአስራሁለትአመትበፊትሞቷል፡፡ከሁዋለኛው ባለቤ ጋርግንወደአስርአመትእንደኖርንእኔ ስመረመርኤችአይቪ ቫይረስእንደለብኝአወቅሁኝ፡፡እሱ ግንሲመረመርነጻስለሆነጥሎኝሄዶአል፡፡ከሁለተኛው ባለቤ ጋርአንድአስርአመትኖረናል፡፡አሁንብቻዬንነው የምኖረው፡፡ከሶስትአመትወዲህየምኖረው ማንኛውንምተራስራእየሰራሁ ነው፡፡ልብስአጠባንግድየመሳሰለውንሁሉ እሰራለሁ፡፡በጋንዲ ሆስፒየቡናጠጡ ፕሮግራምላይተሳመሆኔ በጣምጠቅሞኛል፡፡
አድሎናመገለልንበተመለከተከሌላው ሰው ማለትምከጎረቤትጉዋደኛምበላይየገዛቤተሰቤንሁኔሳየው ብዙምጥሩጥሩስሜትአይሰማኝም፡፡እንዲያውምአንዳንድጊዜ ለምንነገርኩዋቸው እስከማለትያደርሰኛል፡፡ሆኖምግንአንዳንድመሻሻሎችንእያየንመሆኑንመካድአይቻልም፡፡እራስንበማጠንከርግንመኖርይቻላልየሚለውንሁሉምየሚያምንበትነው፡፡
ቀደምሲልኤችአይቪ ኤይድሰንበሚመለከትየነበረው ሁኔማስፈራሪያተደርጎይገለጽስለነበርሁሉንሰው ያሸማቀቀናመጥፎነገርነበር፡፡አሁንግንመድሀኒትስለሚወሰድሰውነትተጎድቶአይይምእንደገናከቫይረስነጻየሆነልጅመውለድይቻላልየሚለው መረጃስላለአንዳንድየኤችአይቪ ቫይረስያለባቸው ሰዎችሌሎችንምእያሳሳቱያሉበትንሁኔስለምመለከትየቫይረሱ ስርጭትእንዳይቀንስምክንያትይሆናልብዬእሰጋለሁ፡፡፺ከጋንዲ ሆስፒል፻
   ( ( ( (
በኢትዮጵያ ከአንድ ሚሊዮን ሰዎች በላይ ከኤችአይቪ ቫይረስ ጋር ይኖራሉ፡፡ ከኤችአይቪ ጋር ከሚኖሩት ሰዎች 41% የሚሆኑት ወንዶች ሲሆኑ 59% ያህሉ ደግሞ ሴቶች ናቸው፡፡ እንደመረጃው እማኝነት ሴቶች ይበልጡኑ በኤችአይቪ ቫይረስ ተጎጂዎች ናቸው፡፡
( ( ( (
፵እኔ ከክፍለሀገርከእህ ጋርነው የመጣሁት፡፡አዲስአበባትምህርእየተከተልኩ ሳለሁ ነበርባለቤ ያገባኝ፡፡ከባለቤ ጋርአብረንስንኖርእርሱ ሁልጊዜ ማሚ ነው፡፡ሲመረመርደግሞሳንባበሽነው እየተባለመድሀኒትቢወስድምሊድንአልቻለም፡፡በእርግጥየመጀመሪያልጄከበሽ ነጻሆናነው የተወለደችው፡፡ሁለተኛልጄንአረገዝኩናስወልድልጁበጣምማሚ ሆነ፡፡በየሆስፒባስመረምረውምምንምመፍትሄ ሳያገኝሞተ፡፡እኔ ምንምአይነትሕመምስላልነበረብኝምንምአልጠረጠርኩም፡፡ከዚያበሁዋላግንእንደገናሳረግዝግንየኤችአይቪ ምርመራበፈቃደኝነትአደረግሁ፡፡ስመረመርግንኤችአይቪ ፖዘቲቭመሆኔ ተነገረኝ፡፡ባለቤብዙ ሳይቆይሞተ፡፡እኔምእራሴንእየተከተልኩ እኖራለሁ፡፡
      እኔ የምኖረው ከእህ ጋርነው፡፡በእርግጥኤችአይቪ ፖዘቲቭመሆኔንለእሱዋአልነገርኩዋትም፡፡ግንባለቤ የሞተበትንምክንያትስለምውቅመድሀኒትስወስድ፣ለምርመራወይንምለቡናጠጡ ፕሮግራምከቤትስወጣበጥሩሁኔአትመለከተኝም፡፡አድሎናመገለልንበሚመለከትበእኔ አስተያየትበእርግጥህብረተሰቡ በብዙ መልኩ ተለውጦአል፡፡ነገርግንአሁንምመሰራትያለበትይመስለኛል፡፡ አንዳንድሰዎችተመርምረው እራሳቸውንሳያውቁተመርምረንእራሳችንንያወቅነውንሲተቹወይንምመጠቋቆሚያሲያደርጉ ይስተዋላሉ፡፡እኔ ለእራሴ ሙሉ ጤነኛሆኜ ልጆቼንበማሳደግላይእገኛለሁ፡፡ይህምተመርምሬእራሴንበማወቄስለሆነበበኩሌ ተመርምረው እራሳቸውንካላወቁሰዎችእሻላለሁ ብዬአስባለሁ፡፡
      ስርጭቱንበመግረገድያየሁትአንድነገርአለ፡፡በአሁኑ ሰአትአንዳንዶችኮንዶምመጠቀምአይፈልጉም፡፡ከተለያዩሰዎችጋርልቅየወሲብድርጊትንሲፈጽሙ ይስተዋላሉ፡፡ይህበጣምአስጊ ነው፡፡ኤችአይቪ ቢይዘኝምጸረኤችአይቪ መውሰድእችላለሁ በሚልየተሳሳተአስተሳሰብችላየሚሉ ሰዎችስላሉ ይህረምተገቢ ነው እላለሁ፡፡
( ( ( (
የኤችአይቪ ቫይረስ ስርጭት በአለም ላይ እንደየሀገሮቹ የእድገትና ተያያዥ ሁኔ ዎችና እንደየህብረተሰቡ የባህርይ ለውጥ ይለያያል፡፡ በየጊዜው ከሚመዘገበው አዲስ በቫይረሱ የሚያዙ ሰዎች 91% የሚሆኑት በሰብሰሐራ አፍሪካ የሚገኙ ናቸው፡፡ ይህ ኢትዮጵያንም የሚጨምር አሀዝ ነው፡፡
 ( ( ( (
፵እኔ መናገርየምፈልገው በመጀመሪያይህንንፕሮግራምየሚያካሂዱትንበጣምአመሰግናለሁ፡፡ከዚያበመቀጠልግንህብረተሰቡንማስተማርእየፈለግሁ ግንመገለልንበመሸሽተግባራዊአላደርገውም፡፡ምክንያቱምየምኖረው በግለሰብቤትተከራይቼነው፡፡በእርግጥብዙ ጥሩመንፈስያላቸው ለሰው የሚያዝኑ የቤት&